በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ በወደብ ሳያርፍ 250
ቀናትን ባሕር ላይ ያሳለፈው ‘ዩኤስኤስ አብርሃም ሊንከን’ የተባለው የአሜሪካ በኒውክሌር ኃይል የሚንቀሳቀስ የጦር አውሮፕላን ተሸካሚ መርከብ በታይላንድ መልሕቁን ጣለ።
የጦር መርከቡ መቆም ለስምንት ወራት በላይ መሬት
ሳይረግጡ የከረሙት 5,000 ገደማ የባሕር ኃይል አባላቱ እጅግ ሲፈልጉ የነበረውን እረፍት የሰጠ ሆኗል።
መርከቡ ያረፈው በግርግር በተሞላ የምሽት ሕይወት እና በወሲብ ቱሪዝም በሚታወቀው የታይላንድ ፓታያ ከተማ
የሚገኝ የባሕር ዳርቻ ሪዞርት አቅራቢያ ነው።
የአሜሪካው የጦር መርከብ ለስድስት ወር ለሚቆይ
የፓስፊክ እና የደቡብ ቻይና ባሕር ግዳጅ ነበር ታኅሣሥ ላይ ከሳን ዲዬጎ የተነሳው።
ይሁን እንጂ የካቲት መጨረሻ ላይ አሜሪካ እና
እስራኤል ኢራን ላይ ወታደራዊ ዘመቻ መክፈታቸውን ተከትሎ መርከቡ ጉዞውን ወደ ባሕረ ሰላጤው አድርጓል።
የመርከቡ ስምሪት ከታሰበው የበለጠ ጊዜ በመውሰዱ
የምግብ እጥረት እንዲሁም በሠራተኞቹ ላይ የአእምሮ መወጠር እንዳጋጠመ የተወሰኑ አሜሪካ የኮንግረስ አባላት በቅርቡ ተናግረው ነበር።
አሜሪካ ባሕር ኃይል አባላቱ አስቸጋሪ የሥራ
ሁኔታ ውስጥ እንዳሉ ቢያምንም፣ በቂ አቅርቦት እንዳላቸው ገልጿል።
ከ286 ቀናት አጠቃላይ የባሕር ላይ ቆይታ በኋላ
ታይላንድ የደረሱት የመርከቡ አባላት ለአምስት ቀናት እረፍት እንደሚያደርጉ እና እንደሚያገግሙ የታይላንድ ባለሥልናት መናራቸው ሮይተርስ
ዘግቧል።
የአሜሪካ ሠራዊት አባላቱ የታይላንድ ፓታያ ማረፋቸው
በኢራን ጦርነት የተቀዛቀዘውን የከተማውን ኢኮኖሚያ ያነቃቃል የሚል ተስፋ ተጥሎበታል።
በአካባቢው የሚገኙ ባለሥልጣናት ከአሜሪካ ሠራዊት
አባላት መምጣት አስቀድሞ በተወሰኑት የከተማው የወሲብ ቱሪዝም መዳረሻዎች ላይ እርምጃ እንደወሰዱ ተዘግቧል።
ታይላንድ ውስጥ የወሲብ ንግድ የተከለከለ ነው።
ባለሥልጣናት አልፎ አልፎ እርምጃ የሚወስዱ ቢሆንም እንደ ፓታያ ያሉ ከተሞች በግልጽ በሚታይ ደረጃ ዋነኛ የወሲብ ቱሪዝም ማዕከል
ናቸው።
የአሜሪካ እና ታይላንድ ባለሥልጣናት ፓታያ ታዋቂ
የሆነችበት ወሲብ ነክ ጉዳይ የዜና ርዕስ ሳይሆን የሠራዊት አባላቱ ቆይታ እንዲጠናቀቅ እየሞከሩ ነው።
የአሜሪካ ወታደሮች መሄድ የማይችሉባቸው የተወሰኑ
ቦታዎች እንዳሉ የታይላንድ ባለሥልጣናት ተናግረዋል። ከእነዚህ ስፍራዎች አንዱ ወደ ዋናው የባሕር ዳርቻ የሚወስደው እና በርካታ
መጠጥ ቤቶች የሚገኙበት ‘ሶይ 6’ የተባለ አካባቢ ነው።
የታይላንድ ፖሊስ የወሲብ ንግድ በአገሪቱ ሕግ
የተከለከለ መሆኑን ለአሜሪካውያኑ ጎብኚዎች እየገለጸ ቢሆንም፣ ፓታያ ውስጥ 25,000 እስከ 50,000 የሚደርሱ በወሲብ ንግድ
ላይ የተሰማሩ ሰዎች እንዳሉ ይታመናል።
ብዙዎቹም የሚገኙት በመጠጥ ቤቶች ደጃፍ ላይ
ቆመው ወንዶችን ወደ ውስጥ ለማስገባት በሚሞክሩበት ሶይ 6 ነው።