የአሜሪካ ጥቃት ሰርግ ላይ የነበሩ አራት ሰዎችን መግደሉን ተከትሎ ኢራን የአጸፋ እርምጃ መውሰዷ ተገለጸ
የአሜሪካ ጦር ማክሰኞ ምሽት በድጋሚ ኢራንን መምታቱን ተከትሎ፣ ቴህራን ኢራቅ እና ዮርዳኖስ ውስጥ በሚገኙ የዋሽንግተን ጦር ሰፈሮች ላይ ጥቃት መክፈቷን የአገሪቱ መንግሥታዊ መገናኛ ብዙኃን እና የዮርዳኖስ ጦር አስታወቁ።
አሜሪካ ደቡባዊ ኢራን ውስጥ ሲሪክ ከተማ የፈጸመችው የሚሳዔል ጥቃት ስብርባሪ ሰርግ እየተካሄደ የነበረበት ቤት ላይ በማረፉ ሕጻን ልጅን ጨምሮ አራት ሰዎች መገደላቸውን የኢራን ቀይ ጨረቃ ማኅበር ገልጿል። ከ50 በላይ ሰዎች መጎዳታቸውንም ማኅበሩ ተናግሯል።
የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም)፣ ኢራን ላይ ጥቃት የተፈጸመው፣ እስላማዊው አብዮታዊ ዘብ በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚያልፉ የንግድ መርከቦች ላይ “በቅርቡ ያደረቸጋውን የጥቃት ሙከራዎች” ተከትሎ እንደሆነ ገልጿል።
የአሜሪካ ተተኳሾች በኢራን ቻባሃር እና ኮናራክ የተባሉ አካባቢዎችን እንዲሁም ጂሮፍት ውስጥ የሚገኝ አየር ማረፊያን መምታታቸውን የኢራን መንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል። ቃሽም ደሴት እና የወደብ ከተማው ባንዳር አባስ ውስጥም ፍንዳታ መሰማቱን በዘገባቸው ጠቅሰዋል።
የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ አሜሪካ ጥቃቶቹን በመፈጸሟ “ትጸጸታለች” ሲል ዝቷል። ዘቡ ዛሬ ረቡዕ ጠዋት ላይ ዮርዳኖስ ውስጥ በሚገኘው የአሜሪካ የባህር ኃይል ጦር ሰፈር ላይ በርካታ የባለስቲክ ሚሳዔሎችን ማስወንጨፉን ከፊል ይፋዊ የሆነው ታስኒም የዜና ወኪል ዘግቧል።
የዮርዳኖስ ጦር 13 ባለስቲክ ሚሳዔሎችን ማክሸፉን ገልጿል። ከእነዚህ ውስጥ 10 ያህሉ ሲወድሙ፣ ሦስቱ ገጠራማ አካባቢዎች ላይ መውደቃቸውን አስታውቋል። ኢራን በፈጸመችው ጥቃት የሞተም ሆነ የተጎዳ ሰው የለም።
የኩዌት ጦር ደግሞ የአገሪቱ አየር መከላከያ ስርዓት ዛሬ ረቡዕ ንጋት ላይ ከኢራን ለተወነጨፉ ሚሳዔሎች ምላሽ እየሰጠ መሆኑን ተናግሯል።
የኢራንን ጥቃት ተከትሎ ባህሬን ውስጥም በርካታ ፍንዳታዎች መሰማታቸውን የኢራኑ መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።
የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ማክሰኞ ምሽት አሜሪካ ጥቃት መፈጸሟ በተገለጸበት ሰዓት፣ ኢራን የአጸፋ እርምጃ ከወሰደች “እጅግ በጠነከረ እና ከፍተኛ ደረጃ” በድጋሚ እንደምትመታ አስጠንቅቀው ነበር።
ሁለቱ አገራት በድጋሚ ግጭት ውስጥ የገቡት፣ አሜሪካ ከሐምሌ ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ እሁድ ምሽት በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ በሚገኘው የኢራኑ ላራክ ደሴት ውስጥ ጥቃት ከፈጸመች በኋላ ነው።
ኢራንም በዮርዳኖስ የሚገኙ የአሜሪካ አየር ኃይል ጦር ሰፈሮች ላይ ሚሳዔሎችን በማስወንጨፍ እና ወደ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ድሮን በመላክ የአጸፋ እርምጃ ወስዳ ነበር።