አሜሪካ ስለ የኢራን የሳይበር ዘመቻዎች ከፍተኛ አዛዥ መረጃ ለሚሰጥ 10 ሚሊዮን ዶላር ልትከፍል ነው
አሜሪካ የኢራን አብዮታዊ ዘብ የሳይበር እና ኤሌክትሮኒክስ ዘመቻዎች ዕዝ ውስጥ ከፍተኛ አዛዥ የሆነው አሚር ያሪያብን ማንነት ወይም አድራሻውን የሚጠቁም መረጃ ለሚሰጥ ሰው እስከ 10 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ የገንዘብ ሽልማት እንደምትሰጥ አስታወቀች።
የአብዮታዊ ዘቡ ዕዝ ከፍተኛ አዛዥ ላይ የመረጃ ጥያቄ የቀረበው፣ “ሽልማት ለፍትህ” በሚባለው እና የአሜሪካ መንግሥት በወንጀል ስለሚፈልጋቸው ሰዎች ጥቆማ ለሚሰጡ የገንዘብ ሽልማት የሚያቀርብበት መርሃ ግብር አካኝነት ነው።
በዚህም “በውጭ መንግሥታት ቁጥጥር ወይም መመሪያ ሥር ሆነው በአሜሪካ ወሳኝ መሠረተ ልማቶች ላይ ጎጂ የሳይበር ጥቃቶችን የፈጸሙ ግለሰቦችን ለመለየት ወይም ለማግኘት የሚያስችል መረጃ ለሚያቀርብ ሰው እስከ 10 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ ሽልማት ይሰጣል” ብሏል።
የአሜሪካ መንግሥት አሁን ዝርዝር መረጃውን ለማግኘት ጥሪ ያቀረበበት አሚር ያሪያብ፣ በኢራን አብዮታዊ ዘብ ሥር የበይነ መረብ እና ኤሌክትሮኒክስ ወታደራዊ ጉዳዮችን በሚከታተለው ዕዝ ውስጥ "የበይነ መረብ ዘመቻዎች" ምክትል አዛዥ እንደሆነ ተገልጿል።
ዋሽንግተን እንደምትለው ያሪያብ በአሜሪካ፣ በአውሮፓ እና በመካከለኛው ምሥራቅ በመከላከያ፣ በመገናኛ ብዙኃን፣ በባሕር ትራንስፖርት፣ በጉዞ እና ቱሪዝም (ሆቴሎችና አየር መንገዶች)፣ በኃይል፣ በፋይናንስ እና በቴሌኮሙኒኬሽን ዘርፎች ላይ የተፈጸሙ አደገኛ የበይነ መረብ ጥቃቶችን ይመራ እንደነበር አሳውቃለች።
ከሁለት ዓመታት በፊትም የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤት ተፈላጊዎችን የሚመለከት መረጃ ለማግኘት የኢራን አብዮታዊ ዘብ የበይነ መረብ ጥቃት የዕዝ ማዕከል ስድስት ከፍተኛ ኃላፊዎችን በሚመለከት ጥቆማ እንዲሰጠው ጥያቄ አቅርቦ ነበር።
በዚህም የስድስቱን አዛዦች ፎቶግራፎች በማውጣት እነዚህ ግለሰቦች የት እንደሚገኙ ወይም ማንነታቸውን ለማጋለጥ የሚያስችል ዝርዝር መረጃ ለሚሰጥ ሰው 10 ሚሊዮን ዶላር ሽልማት ለማቅረብ ቃል ገብቶ ነበር።