ቀጥታ, የአሜሪካ ጥቃት ሰርግ ላይ የነበሩ አራት ሰዎችን መግደሉን ተከትሎ ኢራን የአጸፋ እርምጃ መውሰዷ ተገለጸ

የአሜሪካ ጦር ማክሰኞ ምሽት በድጋሚ ኢራንን መምታቱን ተከትሎ፣ ቴህራን ኢራቅ እና ዮርዳኖስ ውስጥ በሚገኙ የዋሽንግተን ጦር ሰፈሮች ላይ ጥቃት መክፈቷን የአገሪቱ መንግሥታዊ መገናኛ ብዙኃን እና የዮርዳኖስ ጦር አስታወቁ። አሜሪካ ደቡባዊ ኢራን ውስጥ ሲሪክ ከተማ የፈጸመችው የሚሳዔል ጥቃት ስብርባሪ ሰርግ እየተካሄደ የነበረበት ቤት ላይ በማረፉ ሕጻን ልጅን ጨምሮ አራት ሰዎች መገደላቸውን የኢራን ቀይ ጨረቃ ማኅበር ገልጿል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. አሜሪካ በኢራን ላይ በፈጸመችው ጥቃት የሞቱ ሰዎች ቁጥር 19 መድረሱ ተዘገበ

    መልሶ ባገረሻው የኢራን እና የአሜሪካ ጥቃትን ተከትሎ ማክሰኞ ምሽት አሜሪካ በደቡባዊ ኢራን ውስጥ በፈጸመችው ጥቃት የሞቱ ሰዎች ቁጥር ወደ 19 ከፍ ማለቱን የኢራን መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    በጥቃቱ ኮሁስታክ በተባለው የኢራን ግዛት ቢያንስ አራት ሰዎች፣ በኹዜስታን ግዛት ሰባት ሰዎች፣ በከርማንሻህ አራት የኢራን አብዮታዊ ዘብ ሠራዊት አባላት የተገደሉ ሲሆን፤ በላቫን ደሴት ሦስት የባሲጅ ሚሊሻ አባላት እንዲሁም በፋርስ ግዛት ውስጥ በሚገኘው ጃህሮም ውስጥ አንድ ሰው ተገድሏል።

    የኢራን ባለሥልጣናት በአሜሪካ ጥቃት በርካታ ሰላማዊ ሰዎች መገደላቸውን በመግለጽ የአሜሪካንን እርምጃ እያወገዙ ይገኛሉ።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል በሲሪክ ከተማ በነበረ የሰርግ ሥነ ሥርዓት ላይ በተፈጸመ የአሜሪካ ጥቃት ሁለት ሕፃናትን ጨምሮ ቢያንስ አራት ሰዎች መገደላቸውን ዘግቧል።

    ነገር ግን በኢራን ላይ የሚካሄደውን ወታደራዊ ዘመቻን የሚመራው የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) የተፈጸሙት ጥቃቶች ሰላማዊ ሰዎችን ዒላማ ደያረጉ አይደሉም ሲል አስተባብሏል።

    የኢራን ባለሥልጣናት እንደገለጹት፣ አሜሪካ በፈጸመችው ጥቃት ከሞቱት 19 ሰዎች በተጨማሪ ከ50 በላይ ሰዎች የመቁሰል ጉዳት ደርሶባቸዋል።

  2. ግብፅ ውስጥ በደረሰ የመኪና አደጋ የ22 ሰዎች ሕይወት አለፈ

    በግብፅ ምሥራቃዊ ክፍል በደረሰ የአውቶቡስ አደጋ ቢያንስ 22 ሰዎች መሞታቸውን የአገሪቱ የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ።

    በደቡብ ሲናይ ግዛት ውስጥ የሚገኙትን ዳሃብ እና ኑዌይባ የቀይ ባሕር ዳርቻ ከተሞችን በሚያገናኘው መንገድ ላይ ዛሬ ረቡዕ በደረሰው አደጋ ሌሎች 28 ሰዎች ቆስለዋል።

    የግብፅ እና የዮርዳኖስ መገናኛ ብዙኃን እንደዘገቡት፣ በአደጋው ከሞቱት መካከል እስከ 10 የሚደርሱ የዮርዳኖስ ዜጎች ሊኖሩ ይችላል።

    የበርካታ ሰዎች ሕይወት የጠፋበት የዚህ አደጋ መንስኤ ምን እንደሆነ እስካሁን አልታወቀም።

    አካባቢው ከዓለም ዙሪያ በርካታ ቱሪስቶች የሚጎበኙት ታዋቂ የቱሪስት መዳረሻ ነው።

    አደጋው በደረሰበት ጊዜ በአውቶቡሱ ውስጥ ምን ያህል ሰዎች እንደነበሩ አልታወቀም።

    የግብፅ ጤና ሚኒስቴር በሰጠው መግለጫ፣ የቆሰሉት ሁሉም ሰዎች በሦስት የተለያዩ ሆስፒታሎች ሕክምና እያገኙ ነው።

    በግብፅ አደገኛ የመንገድ አደጋዎች የተለመዱ ሲሆን፣ ባለሥልጣናት ባለፈው የአውሮፓውያን ዓመት ብቻ ወደ ስድስት ሺህ የሚጠጉ ሰዎች በመኪና አደጋ መሞታቸውን ሪፖርት አድርገዋል።

    እንደዚህ ያሉ አደጋዎች በአብዛኛው ጥንቃቄ በጎደለው ማሽከርከር እና በደካማ የመንገድ ጥገና ምክንያት እንደሚከሰቱ ይነገራል።

    ባለፈው ወር በሰሜን ምሥራቅ ግብፅ ኢስማኢሊያ ግዛት ውስጥ ሁለት ጭነት መኪኖች ተጋጭተው 18 ሰዎች ሲሞቱ 30 ሰዎች ቆስለው ነበር።

  3. በጊኒ ቢሳው የፕሬዝዳንቱን ሥልጣን የሚያሰፋ አዲስ ሕገ መንግሥት በሕዝበ ውሳኔ ጸደቀ

    ከወራት በኋላ አጠቃላይ ምርጫ በሚደረግባት ጊኒ ቢሳው በተካሄደ ሕዝበ ውሳኔ የፕሬዚዳንቱን ሥልጣን በከፍተኛ መጠን የሚያሰፋ አዲስ ሕገ መንግሥት ጸቀደ።

    ሕዝበ ውሳኔውን ያዘጋጀው ታኅሣሥ ላይ በተደረገው ምርጫ የተፈጠረውን ውዝግብ ተከትሎ የአገሪቱን ሥልጣን የተቆጣጠረው ወታደራዊ መንግሥት ነው።

    በሕዝበ ውሳኔው ድምፅ የሰጡ መራጮች ፕሬዝዳንቱ ጠቅላይ ሚኒስትሩን እና ካቢኔውን እንዲሾም እና እንዲሽር እንዲሁም ከባድ የፖለቲካዊ ቀውስ ከተፈጠረ ፓርላማውን እንዲበትን የማድረግ ሥልጣን የሚሰጠውን ማሻሻያ ደግፈዋል።

    የጊኒ ቢሳው ዋና ተቃዋሚ ፓርቲ በቂ ፖለቲካዊ እና ተቋማዊ ገለልተኝነት የሌለው እንዲሁም አገሪቱ ወደ ዴሞክራሲ የምታደርገውን ሽግግር አደጋ ላይ የሚጥል እንደሆነ በመግለጽ ራሱን ከሕዝበ ውሳኔው አግልሏል።

    በዓለም ላይ ከሚገኙ ደሃ አገራት አንዷ የሆነችው ጊኒ ቢሳው በአውሮፓውያኑ 1974 ከፖርቱጋል ነፃነቷን ካገኘች በኋላ ቢያንስ ዘጠኝ የተሳኩ እና የከሸፉ መፈንቅለ መንግሥቶችን አስተናግዳለች።

    አገሪቱ ሰዎች የማይኖሩባቸው በርካታ ደሴቶች ስላላት ለአደንዛዥ ዕፅ አዘዋዋሪዎች የተመቸች ሆናለች። የተባበሩት መንግሥታት “የናርኮ መንግሥት” የሚል ስያሜ ሰጥቷታል።

    በአገሪቱ የምርጫ ኮሚሽን ይፋ የተደረገው የሕዝበ ውሳኔው ጊዜያዊ ውጤት እንደሚያሳየው፣ እሁድ ዕለት በተሰጠው ድምጽ ከተሳታፊዎቹ መካከል 70 በመቶው ለውጡን ደግፈዋል፤ 30 በመቶዎቹ ደግሞ ተቃውመውታል።

    ከተመዘገቡ መራጮች ውስጥ 60 በመቶ ያህሉ ድምጻቸውን እንደሰጡ ተገልጿል።

    አዲሱ ሕገ መንግሥት የጠቅላይ ሚኒስትሩ ሥልጣን ተሸርሽሮ፣ የፕሬዝዳንቱ ኃይል እንዲጠናከር ያደርጋል። ጊኒ ቢሳው በምትከተለው ከፊል-ፕሬዝዳንታዊ ሥርዓት አማካነኝት የተዘረጋን የሥልጣን ክፍፍል ሚዛንንም ይቀይራል።

    ከዚህ ቀደም በነበረው አሠራር፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩን የሚሾመው ፓርላማው ሲሆን የሚመረጠውም በምክር ቤቱ አብላጫውን መቀመጫ ከያዘው ፓርቲ ነው።

    አሁን አገሪቱን የሚመሩት የወታደራዊው መንግሥት ባለሥልጣናት ይህ አሠራር በአገሪቱ ለተፈጠረው ፖለቲካዊ አለመረጋጋት አስተዋፅዖ እንዳለው በመግለጽ ይከራከራሉ።

    የአሁኑ ለውጥ ፕሬዝዳንቱ በመንግሥት ውስጥ ከፍ ያለ ሥልጣን እንዲኖረው ያደርጋል።

    በሕገ መንግሥቱ የተደነገገው ለአምስት ዓመት የሚቆይ የሁለት የሥልጣን ዘመን ገደብ ግን አልተነካም።

    የወታደራዊው አስተዳደር ባለሥልጣናት፣ እነዚህ ማሻሻያዎች መደረጋቸው በፕሬዝዳንቶች እና በጠቅላይ ሚኒስትሮች መካከል በተደጋጋሚ የሚነሱ አለመግባባቶችን ለማስቆም አስፈላጊ ናቸው የሚል መከራከሪያ ያቀርባሉ።

    ይሁን እንጂ ሕዝበ ውሳኔው በአገሪቱ ዋነኛ ተቃዋሚ ፓርቲ ከሆነው የጊኒ እና ኬፕ ቨርዴ የነፃነት አፍሪካዊ ፓርቲ ጠንካራ ተቃውሞ ገጥሞታል። ፓርቲው ደጋፊዎቹ ድምፅ እንዳይሰጡ አሳስቧል።

    የሚደረጉት ማሻሻያዎች በፕሬዝዳንቱ እጅ ከልክ ያለፈ ሥልጣን እንዲከማች ሊያደርግ ይችላል ሲልም አስጠንቅቋል።

  4. ግዙፉ የአሜሪካ የጦር መርከብ ለ250 ቀናት መልሕቁን የጣለበት በወሲብ ንግድ የምትታወቀው የታይላንድ ከተማ

    በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ በወደብ ሳያርፍ 250 ቀናትን ባሕር ላይ ያሳለፈው ‘ዩኤስኤስ አብርሃም ሊንከን’ የተባለው የአሜሪካ በኒውክሌር ኃይል የሚንቀሳቀስ የጦር አውሮፕላን ተሸካሚ መርከብ በታይላንድ መልሕቁን ጣለ።

    የጦር መርከቡ መቆም ለስምንት ወራት በላይ መሬት ሳይረግጡ የከረሙት 5,000 ገደማ የባሕር ኃይል አባላቱ እጅግ ሲፈልጉ የነበረውን እረፍት የሰጠ ሆኗል።

    መርከቡ ያረፈው በግርግር በተሞላ የምሽት ሕይወት እና በወሲብ ቱሪዝም በሚታወቀው የታይላንድ ፓታያ ከተማ የሚገኝ የባሕር ዳርቻ ሪዞርት አቅራቢያ ነው።

    የአሜሪካው የጦር መርከብ ለስድስት ወር ለሚቆይ የፓስፊክ እና የደቡብ ቻይና ባሕር ግዳጅ ነበር ታኅሣሥ ላይ ከሳን ዲዬጎ የተነሳው።

    ይሁን እንጂ የካቲት መጨረሻ ላይ አሜሪካ እና እስራኤል ኢራን ላይ ወታደራዊ ዘመቻ መክፈታቸውን ተከትሎ መርከቡ ጉዞውን ወደ ባሕረ ሰላጤው አድርጓል።

    የመርከቡ ስምሪት ከታሰበው የበለጠ ጊዜ በመውሰዱ የምግብ እጥረት እንዲሁም በሠራተኞቹ ላይ የአእምሮ መወጠር እንዳጋጠመ የተወሰኑ አሜሪካ የኮንግረስ አባላት በቅርቡ ተናግረው ነበር።

    አሜሪካ ባሕር ኃይል አባላቱ አስቸጋሪ የሥራ ሁኔታ ውስጥ እንዳሉ ቢያምንም፣ በቂ አቅርቦት እንዳላቸው ገልጿል።

    ከ286 ቀናት አጠቃላይ የባሕር ላይ ቆይታ በኋላ ታይላንድ የደረሱት የመርከቡ አባላት ለአምስት ቀናት እረፍት እንደሚያደርጉ እና እንደሚያገግሙ የታይላንድ ባለሥልናት መናራቸው ሮይተርስ ዘግቧል።

    የአሜሪካ ሠራዊት አባላቱ የታይላንድ ፓታያ ማረፋቸው በኢራን ጦርነት የተቀዛቀዘውን የከተማውን ኢኮኖሚያ ያነቃቃል የሚል ተስፋ ተጥሎበታል።

    በአካባቢው የሚገኙ ባለሥልጣናት ከአሜሪካ ሠራዊት አባላት መምጣት አስቀድሞ በተወሰኑት የከተማው የወሲብ ቱሪዝም መዳረሻዎች ላይ እርምጃ እንደወሰዱ ተዘግቧል።

    ታይላንድ ውስጥ የወሲብ ንግድ የተከለከለ ነው። ባለሥልጣናት አልፎ አልፎ እርምጃ የሚወስዱ ቢሆንም እንደ ፓታያ ያሉ ከተሞች በግልጽ በሚታይ ደረጃ ዋነኛ የወሲብ ቱሪዝም ማዕከል ናቸው።

    የአሜሪካ እና ታይላንድ ባለሥልጣናት ፓታያ ታዋቂ የሆነችበት ወሲብ ነክ ጉዳይ የዜና ርዕስ ሳይሆን የሠራዊት አባላቱ ቆይታ እንዲጠናቀቅ እየሞከሩ ነው።

    የአሜሪካ ወታደሮች መሄድ የማይችሉባቸው የተወሰኑ ቦታዎች እንዳሉ የታይላንድ ባለሥልጣናት ተናግረዋል። ከእነዚህ ስፍራዎች አንዱ ወደ ዋናው የባሕር ዳርቻ የሚወስደው እና በርካታ መጠጥ ቤቶች የሚገኙበት ‘ሶይ 6’ የተባለ አካባቢ ነው።

    የታይላንድ ፖሊስ የወሲብ ንግድ በአገሪቱ ሕግ የተከለከለ መሆኑን ለአሜሪካውያኑ ጎብኚዎች እየገለጸ ቢሆንም፣ ፓታያ ውስጥ 25,000 እስከ 50,000 የሚደርሱ በወሲብ ንግድ ላይ የተሰማሩ ሰዎች እንዳሉ ይታመናል።

    ብዙዎቹም የሚገኙት በመጠጥ ቤቶች ደጃፍ ላይ ቆመው ወንዶችን ወደ ውስጥ ለማስገባት በሚሞክሩበት ሶይ 6 ነው።

  5. ዩክሬን በሩሲያ አየር ክልል ላይ የሚበሩ አየር መንገዶችን አስጠነቀቀች

    የዩክሬን ፕሬዚዳንት ቭሎዲሚር ዜሌንስኪ አገራቸው በሩሲያ ላይ የምትፈጽመውን የድሮን ጥቃት በማጠናከሯ የሩሲያ የአየር ክልል “ይዘጋል” ሲሉ አየር መንገዶች አስጠነቀቁ።

    ዜሌንስኪ፤ “የሩሲያን የአየር ክልል የሚጠቀም ማንኛውንም አየር መንገድ፣ ኢንሹራንስ ሰጪዎች እና የሩሲያ ዋና ዋና አውሮፕላን ማረፊያዎችን የሚጠቀሙ ሁሉንም ማስጠንቀቅ እንፈልጋለን፤ የሩሲያ የአየር ክልል በእጅጉ አደገኛ እየሆነ ነው” ብለዋል።

    ሩሲያ በዩክሬን ላይ እያካሄደችው ባለው ወረራ ምክንያት አብዛኞቹ የምዕራብ አገራት የንግድ አየር መንገዶች በሩሲያ ሰማይ አይበሩም። እንደ ቻይና ያሉ አገራት አየር መንገዶች ግን አሁንም በሩሲያ ሰማይ ላይ ይጓዛሉ።

    ለዚህ የዩክሬን ፕሬዝዳንት ማስጠንቀቂያ የሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን በሰጡት ምላሽ፣ የዜሌንስኪን አስተያየት “መንግሥታዊ የሽብርተኝነት አዋጅ” ሲሉ ገልጸውታል። ሩሲያም በዩክሬን ላይ እያጠናከረች ያለውን ጥቃት እንደምትቀጥል ተናግረዋል።

    ፕሬዝዳንት ዜሌንስኪ የአየር ክልሉ ላይ ስለተደቀነው አደጋ ከፍተኛነት ሲያስረዱ፣ “ዩክሬን አንድም የሲቪል አየር ማረፊያ ላይ ስጋት አትደቅንም" ብለዋል።

    "ነገር ግን በሩሲያ ሰማይ ላይ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ድሮኖች ይኖራሉ፤ ይህም ግምት ውስጥ ሊገባ የሚገባ ጉዳይ ነው” በማለትም አሳስበዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ማክሰኞ ምሽት ባሠራጩት የቪዲዮ መልዕክት፣ “በሩሲያ የተጀመረው ጦርነት የራሷን የአየር ክልል እየዘጋ ነው” ሲሉ ተናግረዋል።

    የዜሌንስኪ ማስጠንቀቂያ በተለይ እንደ ሞስኮ እና ሴንት ፒተርስበርግ ባሉ ዋና ዋና ከተሞች ውስጥ ወደሚገኙ የሩሲያ አውሮፕላ ማረፊያዎች በረራዎችን ማካሄዳቸውን ለሚቀጥሉ የአየር መንገዶች የተሰጠ ነው።

    አራት ዓመታትን ያስቆጠረው የሩሲያን ወረራ ተከትሎ የቀሰቀሰው ጦርነት ከድንበር አካባቢዎች ባይሻገርም ሁለቱ አገራት በሚፈጽሟቸው የድሮን ጥቃቶች ታላላቅ ከተሞች ድረስ ዘልቋል።

    በዚህም ዩክሬን በተለያዩ ጊዜያት የሩሲያ ተቋማትን ዒላማ በማድረግ እስከ ሞስኮ የዘለቁ ጥቃቶችን ስትፈጽም፣ ሩሲያም በኪየቭ እና በሌሎችም ከተሞች ላይ ጥቃት እያደረሰች ነው።

    የአሁኑን የፕሬዝዳንት ዜሌንስኪ ማስጠንቀቂያ ተከትሎ ምላሽ የሰጡት የሩሲያው ፕሬዝዳንት ቭላድሚር ፑቲን፣ "ድርድር እንዲጀመር እየጠየቁ ነው... ነገር ግን ከሽብርተኞች ጋር አንደራደርም" ብለዋል።

  6. ከአሜሪካ ጋር የሚተባበሩ አገራት "አደገኛ ምላሽ" እንደሚጠብቃቸው ኢራን አስታወቀች

    አሜሪካ በኢራን ላይ ዳግም የከፈተችውን ጥቃት ተከትሎ ማክሰኞ ምሽት ሌላ ዙር ጥቃት ካደረሰች በኋላ ኢራን ጦር ኃይሎች ጠቅላይ ዕዝ የአሜሪካ ወዳጅ የሆኑትን የአካባቢው አገራት አስጠነቀቀ።

    ኻታም አል አንቢያ የተባለው ኢራን ከአሜሪካ ጋር የምታካሂደውን ጦርነት የሚመራ ዋና ማዘዣ፣ አሜሪካ በደቡባዊ ኢራን ጥቃት ከፈጸመች በኋላ ከአሜሪካ ጦር ጋር የሚተባበሩ የቀጣናው አገራት “አደገኛ ምላሽ ይጠብቃቸዋል” ሲሉ አስጠንቅቋል።

    ዕዙ ዛሬ ረቡዕ ጠዋት በወጣው መግለጫ፣ የኢራን አብዮታዊ ዘብ እና የአገሪቱ ጦር ኃይል ለአሜሪካ ጥቃት አጸፋ መስጠቱን ጠቅሶ፣ በአካባቢው ባሉ የአሜሪካ ተቋማት እና ጦር ሰፈሮች ላይ ከባድ ጉዳት መድረሱን አመልክቷል።

    ጨምሮም የአሜሪካ ኃይሎችን የሚያስተናግዱ የአካባቢው አገራት “ከጥቃት ፈጻሚው የአሜሪካ ጦር ጋር የሚያደርጉት ትብብር የሚያስከትለውን አደገኛ ውጤት መቀበል አለባቸው” ብሏል።

    አሜሪካ ማክሰኞ ምሽት በኢራን ደቡባዊ የባሕር ጠረፍ አካባቢዎች የአየር ጥቃት መፈጸም ከጀመረች ከአንድ ሰዓት በኋላ፣ የኢራን አብዮታዊ ዘብ እና ጦሩ በዮርዳኖስ፣ በባህሬን እና በኢራቅ የኤርቢል ከተማ የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን በሚሳዔል እና በድሮን ማጥቃታቸውን አስታውቀዋል።

    በተጨማሪም የኩዌት ጦር ኃይል ከኢራን በሚሰነዘሩ ጥቃቶች ምክንያት የአገሪቱ የአየር መከላከያ ሥርዓቶች በተጠንቀቅ እንዲቆሙ መደረጋቸው ተገልጿል።

    በማክሰኞው ምሽት በሲሪክ አካባቢ በሚገኘው የኮህስታክ መንደር በተፈጸመ የአሜሪካ የአየር ጥቃት፣ በሰርግ ሥነ ሥርዓት ላይ የነበሩ ቢያንስ አምስት ሲቪሎች መገደላቸውን እና ከ60 በላይ ሰዎች መቁሰላቸው ተዘግቧል።

    በኢራን መገናኛ ብዙኃን መረጃ መሠረት ከሟቾቹ መካከል አንድ ሕፃን ይገኛል፤ ከቆሰሉት አብዛኞቹም ከደህስታክ መንደር የሆኑ ሴቶች እና ሕፃናት ናቸው።

  7. የአሜሪካ ጥቃት ሰርግ ላይ የነበሩ አራት ሰዎችን መግደሉን ተከትሎ ኢራን የአጸፋ እርምጃ መውሰዷ ተገለጸ

    የአሜሪካ ጦር ማክሰኞ ምሽት በድጋሚ ኢራንን መምታቱን ተከትሎ፣ ቴህራን ኢራቅ እና ዮርዳኖስ ውስጥ በሚገኙ የዋሽንግተን ጦር ሰፈሮች ላይ ጥቃት መክፈቷን የአገሪቱ መንግሥታዊ መገናኛ ብዙኃን እና የዮርዳኖስ ጦር አስታወቁ።

    አሜሪካ ደቡባዊ ኢራን ውስጥ ሲሪክ ከተማ የፈጸመችው የሚሳዔል ጥቃት ስብርባሪ ሰርግ እየተካሄደ የነበረበት ቤት ላይ በማረፉ ሕጻን ልጅን ጨምሮ አራት ሰዎች መገደላቸውን የኢራን ቀይ ጨረቃ ማኅበር ገልጿል። ከ50 በላይ ሰዎች መጎዳታቸውንም ማኅበሩ ተናግሯል።

    የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም)፣ ኢራን ላይ ጥቃት የተፈጸመው፣ እስላማዊው አብዮታዊ ዘብ በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚያልፉ የንግድ መርከቦች ላይ “በቅርቡ ያደረቸጋውን የጥቃት ሙከራዎች” ተከትሎ እንደሆነ ገልጿል።

    የአሜሪካ ተተኳሾች በኢራን ቻባሃር እና ኮናራክ የተባሉ አካባቢዎችን እንዲሁም ጂሮፍት ውስጥ የሚገኝ አየር ማረፊያን መምታታቸውን የኢራን መንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል። ቃሽም ደሴት እና የወደብ ከተማው ባንዳር አባስ ውስጥም ፍንዳታ መሰማቱን በዘገባቸው ጠቅሰዋል።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ አሜሪካ ጥቃቶቹን በመፈጸሟ “ትጸጸታለች” ሲል ዝቷል። ዘቡ ዛሬ ረቡዕ ጠዋት ላይ ዮርዳኖስ ውስጥ በሚገኘው የአሜሪካ የባህር ኃይል ጦር ሰፈር ላይ በርካታ የባለስቲክ ሚሳዔሎችን ማስወንጨፉን ከፊል ይፋዊ የሆነው ታስኒም የዜና ወኪል ዘግቧል።

    የዮርዳኖስ ጦር 13 ባለስቲክ ሚሳዔሎችን ማክሸፉን ገልጿል። ከእነዚህ ውስጥ 10 ያህሉ ሲወድሙ፣ ሦስቱ ገጠራማ አካባቢዎች ላይ መውደቃቸውን አስታውቋል። ኢራን በፈጸመችው ጥቃት የሞተም ሆነ የተጎዳ ሰው የለም።

    የኩዌት ጦር ደግሞ የአገሪቱ አየር መከላከያ ስርዓት ዛሬ ረቡዕ ንጋት ላይ ከኢራን ለተወነጨፉ ሚሳዔሎች ምላሽ እየሰጠ መሆኑን ተናግሯል።

    የኢራንን ጥቃት ተከትሎ ባህሬን ውስጥም በርካታ ፍንዳታዎች መሰማታቸውን የኢራኑ መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ማክሰኞ ምሽት አሜሪካ ጥቃት መፈጸሟ በተገለጸበት ሰዓት፣ ኢራን የአጸፋ እርምጃ ከወሰደች “እጅግ በጠነከረ እና ከፍተኛ ደረጃ” በድጋሚ እንደምትመታ አስጠንቅቀው ነበር።

    ሁለቱ አገራት በድጋሚ ግጭት ውስጥ የገቡት፣ አሜሪካ ከሐምሌ ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ እሁድ ምሽት በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ በሚገኘው የኢራኑ ላራክ ደሴት ውስጥ ጥቃት ከፈጸመች በኋላ ነው።

    ኢራንም በዮርዳኖስ የሚገኙ የአሜሪካ አየር ኃይል ጦር ሰፈሮች ላይ ሚሳዔሎችን በማስወንጨፍ እና ወደ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ድሮን በመላክ የአጸፋ እርምጃ ወስዳ ነበር።

  8. የኬንያ አቪዬሽን ሠራተኞች ለሁለት ቀናት በረራዎች እንዲስተጓጎሉ ያደረገውን አድማ አቆሙ

    በኬንያ ዋና ከተማ ናይሮቢ ከሚገኘው ዋና አየር ማረፊያ እና ከሌሎች አገሪቱ ስፍራዎች የሚነሱ በረራዎች ለሁለት ቀናት እንዲስተጓጎሉ ያደረጉት የኬንያ የአቪዬሽን ሠራተኞች አድማቸውን አቆሙ።

    አድማው የቆመው ሠራተኞቹን የወከለው ማኅበር የደመወዝ ጥያቄ እና ሌሎች ቅሬታዎች እንዲፈቱ ከአገሪቱ መንግሥት ጋር ስምምነት በመድረሱ ነው።

    ማኅበሩ እና የአገሪቱ ባለሥልጣናት ሠራተኞች ወዲያውኑ ወደ ሥራ እንዲመለሱ የሚያደርግ ስምምነት ዛሬ ማክሰኞ ተፈራርመዋል።

    እሁድ ዕለት ቀስ በቀስ በተጀመረው አድማ ምክንያት በቀጣናው ቁልፍ የትራንስፖርት ማዕከል በሆነው የናይሮቢው በጆሞ ኬንያታ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ውስጥ በመቶዎች የሚቆጠሩ መንገደኞች ተስተጓጉለው ታይቷል።

    ሠራተኞቹ የተሻለ የሥራ ሁኔታ እንዲኖር እና ከዚህ ቀደም መግባባት የተደረበት ስምምነት ተግባራዊ እንዲሆን ሲጠይቁ ነበር።

    የሠራተኞች ማኅበሩ መሪ ሞስ ንዲዬማ ዛሬ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ “የአድማ እርምጃው እንዲቆም እንዲሁም መደበኛው የሥራ እንቅስቃሴ እንዲመለስ እና አገልግሎቶች እንዲጀመሩ አባሎቻችንን እየጠየቅን ነው” ብለዋል።

    “ሥራ ላይ ያሉ [ሠራተኞች] የተከማቹ በረራዎችን ማቃለል እንዲጀምሩ እየጠየቅን ነው” ሲሉም አክለዋል።

    የኬንያ የትራንስፖርት ሚኒስትር ዴቪስ ቺርቺር አድማው እንዲካሄድ ምክንያት የሆኑ ቅሬታዎች የሚፈቱበትን መንገድ በተመለከተ ከማኅበሩ ጋር ስምምነት ላይ መደረሱን ተናግረዋል።

    “እዚህ መድረሳችን አሳዛኝ ነበር፣ ነገር ግን ከዚህ ወጥተናል። አሁን ቁጥሩ የለንም፤ ነገር ግን በኢኮኖሚው ላይ የደረሰው ኪሳራ ከፍተኛ መሆኑ ያሳዝናል” ብለዋል።

    ሰኞ ዕለት በረራ የተስተጓጎለባቸው ተጓዦች በናይሮቢው ዋና አየር ማረፊያ ተሰብስበው ታይተዋል። የተወሰኑትም አዲስ ዜና ጥበቃ ምሽቱ በአየር ማረፊያው አሳልፈዋል።

    ኬንያ ኤርዌይስ ለስድስት ሰዓታት የቆየ የበረራ መዘግየት እንዳጋጠመ እና ያልተነሱ በረራዎች በመጠራቀማቸው የተወሰኑት እንዲሰረዙ መደረጉን አስታውቋል።

    ለመስተጓጎሉ ይቅርታ የጠየቀው አየር መንገዱ፣ ተጓዦች ያለ ቅጣት በረራቸውን መቀየር እንደሚችሉ ገልጿል።

  9. አሜሪካ ወደ ስምምነቱ ከተመለሰች ኢራንም በትግበራው እንደምትሳተፍ አስታወቀች

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዤኪያን፤ አሜሪካ መግባቢያ ሰነዱን ወደ መተግበር ከተመለሰች ቴህራንም ወደ ስምምነቱ እንደምትመለስ ተናገሩ።

    የኢስላማባድ የመግባቢያ ሰነድ ላይ የተቀመጡ ኃላፊነቶችን አሜሪካ የምትወጣ ከሆነ ኢራንም በምላሹ በአፋጣኝ ስምምነቱን እንደምትተገብር ገልጸዋል።

    በቢሽኬክ የሻንጋይ ትብብር ጉባዔ ላይ ንግግር ያደረጉት የኢራን ፕሬዝዳንት “አሜሪካ የፕሬዝዳንቷ ፊርማ ያረፈበትን ስምምነት ከሁለት ሳምንት በላይ አልጠበቀችም። ስምምነቱን በመጣሷ በአጸፋው ከኢራን ተገቢው ምላሽ ተሰጥቷታል” ብለዋል።

    አሜሪካ ወደ ስምምነቱ ከተመለሰች ኢራንም የመግባቢያ ሰነዱን እንደምትተገብር አስረድተዋል።

    ባለፉት ጥቂት ሳምንታት ውስጥ የኢራን ፖለቲከኞች እና ወታደራዊ ኃላፊዎች እንደተናገሩት ከሆነ አሜሪካ ወደ ስምምነቱ ከተመለሰች ቴህራንም ተመሳሳይ ውሳኔ ላይ የምትደርስ ይሆናል።

  10. በኔፓል በጎርፍ አደጋ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ወደ 1,000 ተቃረበ

    በኔፓል በደረሰው የጎርፍ አደጋ ሳቢያ የሞቱ ሰዎች ቁጥር 987 መድረሱን የአገሪቱ የአደጋ መከላከል ተቋም አስታወቀ።

    ኔፓል ከቲቤት ጋር በምትዋሰንበት አካባቢ በደረሰው የጎርፍ አደጋ ምክንያት 3,916 ሰዎች እስካሁን የደረሱበት አልታወቀም። ከጠፉት ሰዎች መካከል ከ600 በላይ የሚሆኑት በትሪሹሊ ወንዝ በውሃ ኃይል ማመንጫ ይሠሩ የነበሩ ናቸው።

    በኃይል ማመንጫው ጭቃ ተዳፍኖባቸው መውጣት ያልቻሉ ሠራተኞችን በሕይወት ለማግኘት ርብርብ ቀጥሏል።

    ወደ ዋሻዎቹ አየር እንዲገባ ማድረግ የተቻለ ሲሆን ወደ አንደኛው ዋሻ መግባት ቢቻልም ሰዎች እንዳልተገኙ ተገልጿል።

    የ33 ዓመቱ መኃንዲስ አውሩስ ባንዳሪ ባለቤት አኑሻላ ባንዳሪ ለቢቢሲ “ባገኘው ብዬ እመኛለሁ፤ ወደ ቤት ቢመጣ ብዬ እመኛለሁ” ብላለች።

    የኔፓል ጠቅላይ ሚኒስትር ባላንድራ ሻህ እንደተናገሩት ትናንት ሰኞ ከሥፍራው 279 ሰዎችን ማውጣት ተችሏል።

    በፍለጋው የኔፓል፣ የቻይና፣ የሕንድ፣ ኮሪያ እና አውስትራሊያ ባለሙያዎች እየተሳተፉ ነው።

  11. ኢራን ለሚፈጸሙባት ጥቃቶች መነሻ የሆኑ አገራትን ዒላማ እንደምታደርግ አስጠነቀቀች

    ኢራን በአሜሪካ ለሚፈጸምባት ጥቃት ምንጭ የሆኑ የአካባቢው አገራትን ዒላማ በማድረግ አጸፋ እንደምትመልስ አስጠነቀቀች።

    የኢራን ጦር ኃይሎች ጠቅላይ መምሪያ ባወጣው መግለጫ፣ በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኙ አገራት የአሜሪካ ጥቃት መነሻ መሆናቸውን ቀጥለዋል ሲል ከስሷል።

    “አንዳንድ የቀጣናው አገራት ምንም እንኳን የጥቃቶች መነሻ እንደማይሆኑ ከዚህ ቀደም ያወጡት መግለጫ ቢኖርም፣ አሁንም አሜሪካ ግዛታቸውን በመጠቀም ኢራንን እንድትጠቃ እያስቻሉ ነው" ሲል አስጠንቅቋል።

    ይህ ከፍተኛ የኢራን ወታደራዊ ተቋም በመግለጫው፣ ኢራን ለሚፈጸምባት “የማንኛውም ጥቃት ምንጭ የሆነ ቦታን ዒላማ” እንደምታደርግም አስታውቋል።

    መግለጫው ኢራን “የጎረቤት አገራትን ሉዓላዊነት እያከበረች ቢሆንም፣ የሚፈጸምን ማንኛውንም ጥቃት ፈጽሞ አትታገስም፤ እንዲሁም እጅግ ከባድ ምላሽ ትሰጣለች” ብሏል።

    ጨምሮም ባለፉት ቀናት ኢራን በተለያዩ ኢላማዎች ላይ የፈጸመቻቸው ጥቃቶችም በዚሁ ምክንያት ለአሜሪካ ጥቃት የተሠጡ ምላሾች መሆናቸውን ገልጿል።

    እሁድ ሌሊት አሜሪካ በላርክ ደሴት ላይ የፈጸመችውን ጥቃት ተከትሎ፣ ኢራን በዮርዳኖስ እና በተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የሚገኙ የአሜሪካ ወታደራዊ ጦር ሠፈሮችን ዒላማ አድርጋ የአጸፋ ጥቃት መፈጸሟ ተገልጿል።

  12. የአሜሪካ ጦር ዋና ፀሐፊ ከመከላከያ ሚኒስትሩ ጋር ባለመግባባታቸው ሥልጣን ለቀቁ

    የአሜሪካ ጦር ኃይል ዋና ፀሐፊ ከመከላከያ ሚኒስትሩ ጋር ባላቸው አለመግባባት ምክንያት የሥራ መልቀቂያ ደብዳቤያቸውን ለፕሬዝዳንት ትራምፕ ማስገባታቸውን ዎል ስትሪት ጆርናል ዘገበ።

    የጦሩ ዋና ፀሐፊ ዳንኤል ድሪስኮል ከኃላፊነታቸው የሚለቅቁት ከመከላከያ ሚኒስትሩ ፒት ሄግሴት ጋር ለወራት የዘለቀን አለመግባባት እና የአመለካከት ልዩነትን ተከትሎ መሆኑ ተነግሯል። ድሪስኮል በሚቀጥሉት ቀናት የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱን (ፔንታገን) እንደሚለቁም ተጠቁሟል።

    ዎል ስትሪት ጆርናል ሰኞ ዕለት እንደዘገበው፣ በድሪስኮል እና በሄግሴት መካከል ያለው ውዝግብ በተለይ የአሜሪካ የምድር ጦር ኃይል ወደፊት በሚከተለው አቅጣጫ እና ከፍተኛ አዛዦችን ከኃላፊነታቸው በማንሳት ጉዳይ ላይ ተባብሶ ነበር።

    ዋይት ሐውስ በበኩሉ የድሪስኮልን አስተዋጽኦን በማድነቅ፣ የፕሬዝዳንት ትራምፕን የመከላከያ ፖሊሲ በመተግበር፣ የጦር ኃይሉን ዝግጁነት እና የውጊያ ብቃት በማጠናከር እንዲሁም በሩሲያና በዩክሬን መካከል በተካሄዱ ድርድሮች ውስጥ ውጤታማ ሚና ተጫውተዋል ብሏል።

    የድሪስኮል ሥራ መልቀቅ በአሜሪካ ጦር ኃይል አስተዳደር ላይ ተጨማሪ ችግርን ሊፈጥር እንደሚችልም ተገልጿል።

    በዎል ስትሪት ጆርናል ዘገባ መሠረት፣ ከድሪስኮል መልቀቅ በኋላ በአሜሪካ ወታደራዊ መዋቅር ውስጥ በአገሪቱ ምክር ቤት የተሾመ ሲቪልም ሆነ ወታደራዊ መሪ አይኖርም ተብሏል። ዝርዝሩን እዚህ ያንብቡ፦ የአሜሪካ ጦር ዋና ፀሐፊ ለወራት የዘለቀ ውጥረትን ተከትሎ ሥልጣናቸውን ለቀቁ

  13. አሜሪካ በጦርነቱ ቅድሚያ የምትሰጠው የሆርሙዝ ወሽመጥን “ነጻ ዝውውር ለማረጋገጥ” መሆኑን ገለጸች

    አሜሪካ ከኢራን ጋር እያደረገች ባለችው ጦርነት አሁን ላይ ያላት ግብ በሆርሙዝ ወሽመጥ ነጻ ዝውውር እንዲኖር ማስቻል እንደሆነ የአገሪቱ ምክትል ፕሬዝዳንት ጄዲ ቫንስ ተናገሩ።

    ቫንስ ከፎክስ ኒውስ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ እንደገለጹት፤ ያለፈው እሑድ በላርክ ደሴት ላይ አሜሪካ ያደረሰችው ጥቃት ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ ቦምብ እንዳታጠምድ ለማስቆም ያለመ ነው።

    የኢራን አስተዳደር የነዳጅ እና ጋዝ የውጭ ንግድን ለመግታት የሚያደርገው ጥረት “ስትራቴጂያዊ ውጤታማነት” እንደሚጎድለው ጄዲ ቫንስ ተናግረዋል።

    ምክትል ፕሬዝዳንቱ የኢራንን መሪዎች “እብዶች” ብለው አንጓጥጠዋል።

    “በጣም እንግዳ የሚሆንብኝ ነገር የነዳጅ እና ጋዝ እንቅስቃሴን ለማስቆም በሚል አጋሮቻቸው ላይ ሳይቀር መተኮሳቸው ነው” ብለዋል።

    በተባበሩት መንግሥታት የኢራን ቋሚ አምባሳደር በበኩላቸው፤ ለድርጅቱ ዋና ጸሐፊ በላኩት ደብዳቤ አሜሪካ በላርክ ደሴት የፈጸመችውን ጥቃት አውግዘዋል።

    “አሜሪካ፣ እንዲሁም የምታደርሰውን ነውጠኛ ጥቃት እና ሌሎችም ሕገ ወጥ ተግባሮቿን የሚደግፉ፣ የሚያሳልጡ ወይም የሚሳተፉ አካላት በድርጊታቸው ለሚደርስባቸው ከፍተኛ የአጸፋ ምላሽ ኃላፊነቱን ይወስዳሉ” ብለዋል።

    ኢራን ለተመድ የፀጥታው ምክር ቤት በጻፈችው ደብዳቤ፤ አሜሪካ የድርጅቱን መርሕ በመጣስ የምትፈጽመውን ጥቃት በአፋጣኝ እንድታቆም ጠይቃለች።

    በተጨማሪም አሜሪካ በፋርስ ባሕረ ሰላጤ እና በሆርሙዝ ወሽመጥ ያለውን የባሕር ላይ እንቅስቃሴ አደጋ ውስጥ እንዳትከት አሳስባለች።

  14. ከኢራን ጋር ባልተቋጨ ጦርነት ውስጥ ያሉት ትራምፕ “ኢራን ተሸንፋለች” አሉ

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ሠራዊታቸው ባለፉት ወራት በኢራን ላይ በወሰደው ወታደራዊ እርምጃ ኢራን መሸነፏ ግልጽ ነው ሲሉ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ጻፉ።

    ፕሬዝዳንቱ በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያ መድረካቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሁፍ በጦርነቱ ኢራን የነበራትን ሁሉንም ነገሮች አጥታ ለሽንፈት ተዳርጋለች ብለዋል።

    “ኢራን በይፋ የተሸነፈች ሀገር ናት። አብቅቶላታል። የባሕር ኃይል የላትም፣ የአየር ኃይል የላትም፣ ብሔራዊ ገንዘቧ ዋጋ አጥቷል፣ ለወታደሮቿ እና ለፖሊሶቿ መክፈል አትችልም፣ የዋጋ ንረቱ 300 በመቶ ደርሷል፣ አመራሩም ተበታትኖ አገሪቱን መወከል አይችልም” ብለዋል።

    ጨምረውም “ያላቸው ነገር ከአሜሪካ የሚወጣ የሐሰት ዜና እና የራሳቸውን ተቃዋሚዎች የመግደል ፍላጎት ብቻ ነው። ከ100,000 በላይ ሰዎችን ገድለዋል፤ በሰብአዊነት ላይ የተፈጸመ የጦር ወንጀል በመፈጸማቸውም ለፍርድ ሊቀርቡ ይገባል” ሲሉ ጽፈዋል።

    ትራምፕ ይህንን ይበሉ እንጂ ኢራን ባለፉት ስድስት ወራት ከእስራኤል እና ከአሜሪካ የተፈጸመባትን ጥቃት ተቋቁማ በቀጣናው ባሉ የአሜሪካ ተቋማት ላይ የድሮን እና የሚሳዔል ጥቃቶችን እየፈጸመች ነው።

    በተጨማሪም ከፍተኛ የነዳጅ ምርት ለዓለም ገበያ የሚተላለፍበትን የሆርሙዝ ወሽመጥን በመዝጋት በዓለም የነዳጅ ገበያ ላይ ጫና ማሳደር ችላለች።

    በእርግጥም ኢራን በጦርነቱ ከፍተኛ ጉዳት የደረሰባት ቢሆንም አሁንም ከኃያሏ አሜሪካ ጋር ተፋጥጣ ትገናለች። ጦርነቱን ለማብቃት ድርድሮች እየተደረጉ ቢሆንም ከውጤት ላይ አልደረሱም።

    በወታደራዊ እርምጃ የምትፈልገውን ውጤት ያላገኘችው ኢራንን በምጣኔ ሀብት ጫና ለማንበርከክ የአሜሪካ የገንዘብ ሚኒስቴር አዳዲስ ማዕቀቦች እና ዕገዳዎችን በኢራን እና በአጋሮቿ ላይ ተግባራዊ እንደሚያደርግ አስታውቋል።

  15. “ፕሬዝዳንት ትራምፕ ሆርሙዝን የአሜሪካ ግዛት ማድረግ ቀርቶ ማለም አይችሉም”- ኢራን

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አገራቸው ከኢራን ጋር ጦርነት ውስጥ ከገባችባቸው ነገሮች አንዱ የሆነውን የሆርሙዝ ሰርጥ የአገራቸው ግዛት ለማድረግ በተደጋጋሚ መናገራቸው የማይሆን ነገር ነው ሲሉ የኢራን ወታደራዊ መኮንን ተናገሩ።

    የኢራን ጦር ኃይሎች ዋና ቃል አቀባይ ብርጋዴር ጄኔራል አቦልፋዝል ሸካርቺ እንደተናገሩት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት በተግባር የሆርሙዝ ወሽመጥን የአሜሪካ ግዛት ማድረግ ቀርቶ “ማለም እንኳ አይችሉም” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    ታስኒም የተባለው የኢራን ዜና ወኪል እንደዘገበው፣ ሸካርቺ ለአንድ መገናኛ ብዙኃን በሰጡት ቃለመጠይቅ “የአሜሪካ ኃይሎች በዚህ ክልል እንዲኖሩ፣ አንዲገኙ አንፈቅድም፤ እንዲሁም ከምዕራብ የእስያ ክፍል ለማስወጣት ቆርጠናል” ብለዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን ጦርነት ውስጥ ከገቡ በኋላ ከፍተኛ መጠን ያለው ነዳጅ የሚተላለፍበት የሆርሙዝ ወሽመጥ ለመርከቦች እንቅስቃሴ አስቸጋሪ ከመሆኑ በተጨማሪ ለረጅም ጊዜ ተዘግቷል።

    አሜሪካም ከኢራን ጋር በምታደርጋቸው ድርድሮች መተላለፊያው እንዲከፈት ማድረግ ዋነኛ ዓላማዋ ከማድረጓ በተጨማሪ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ሆርሙዝን የአሜሪካ ይዞታ እንደሚያደርጉ በተደጋጋሚ ሲናገሩ ቆይተዋል።

  16. ኤምሬትስ ግዛቷ ውስጥ በሚገኝ የአሜሪካ ጦር ሰፈር ላይ ጥቃት ተፈጽሟል መባሉን አስተባበለች

    የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ የመከላከያ ሚኒስቴር አል-ማንሃድ አየር ማረፊያ በኢራን ጥቃት ተፈጽሞበታል በሚል የወጣውን ዘገባ 'ትክክል አይደለም' ሲል አስተባበለ።

    ጥቃቱን በሚመለከት የኢራን ጦር በሰጠው መግለጫ እሁድ ሌሊት አሜሪካ በኢራን ላርክ ደሴት ላይ ለፈጸመችው ጥቃት በወሰደው የአጸፋ እርምጃ፣ “ኤምሬትስ ውስጥ ባለው አል-ማንሃድ ጦር ሰፈር የሚገኙ የአሜሪካ ኃይሎች እና ሄሊኮፕተሮችን” በበርካታ አውዳሚ ድሮኖች መምታቱን ገልጿል።

    ሆኖም የኤምሬትስ የመከላከያ ሚኒስቴር ጥቃት መፈጸሙን ውድቅ አድርጎ በአገሪቱ የባሕር ክልል ውስጥ አንድ ድሮን ብቻ መታየቱን አስታውቋል።

    ነገር ግን ሚኒስቴሩ ተገኘ ስለተባለው ስለዚህ ድሮን ተጨማሪ ዝርዝር አልሰጠም። ድሮኑ ተመትቶ ወድቆ ወይም ወደ ዒላማው ደርሶ እንደሆነ አላብራራም።

    ይሁን እንጂ የኤምሬትስ መከላከያ ሚኒስቴር “ማንኛውም ሊፈጠር የሚችል ስጋትን ለመጋፈጥ በከፍተኛ ሁኔታ ዝግጁ ነን” ሲል አስገንዝቧል።

    እንዲሁም ዜጎች “መረጃን ከኦፊሴላዊ ምንጮች ብቻ እንዲያገኙ እና አሉባልታ እና የተሳሳተ ወሬ ከማሠራጨት እንዲቆጠቡ” ጥሪ አቅርቧል።

  17. የአሜሪካ እና ኢራን ግጭት ዳግም ማገርሸቱን ተከትሎ የነዳጅ ዋጋ ጨመረ

    አሜሪካ ከስድስት ሳምንታት በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ እሁድ ምሽት ኢራን ላይ በፈጸመችው ጥቃት የመካከለኛው ምሥራቅ ግጭት ማገርሸቱን ተከትሎ በዓለም አቀፍ ገበያ የነዳጅ ዋጋ ጨመረ።

    ባለፈው ሳምንት ቅናሽ ሲመዘገብበት የነበረው የነዳጅ ዋጋ ከአሜሪካ ጥቃት በኋላ የሁለት በመቶ ገደማ ጭማሪ ታይቶበታል።

    የነዳጅ ዋጋ መለኪያ ተደርጎ የሚቆጠረው ብሬንት የአንድ በርሜል ድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ የ1.77 ዶላር ጭማሪ ታይቶበት በ89.87 ዶላር እየተሸጠ ነው።

    አሜሪካ ከሐምሌ ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ በሚታወቅ ደረጃ በፈጸመችው የትናንቱ ጥቃት ላራክ በተባለው የኢራን ደሴት የሚገኙ ሁለት ማስወንጨፊያዎችን መምታቷን አስታውቃለች።

    ይህንን ተከትሎም ኢራን በዮርዳኖስ እና በተባበሩት አረብ ኤምሬቶች የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሠፈሮች ላይ ጥቃት መፈጸሟን ገልጻለች።

    ስድስት ወራት ያስቆጠረው የኢራን ጦርነት በዓለም የነዳጅ ገበያ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ አሳድሯል። ከዓለም የነዳጅ እና ፈሳሽ የተፈጥሮ ጋዝ ምርት ውስጥ 20 በመቶ ገደማው የሚተላለፍበት ሆርሙዝ ወሽመጥ በኢራን በመዘጋቱ የአንድ በርሜል ነዳጅ ዋጋ ከ100 ዶላር በላይ ደርሶ ነበር።

    ሁለቱ አገራት የሚፈጽሟቸው ጥቃቶች ረገብ ማለታቸውን ተከትሎ ደግሞ ቅናሽ ተስተውሏል።

    ወሳኝ የባሕር መስመር የሆነው ሆርሙዝም በዛሬው ዕለት ጥቃት እንዳስተናገደ ተገልጿል። የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ባወጣው መግለጫ “በሆርሙዝ ወሽመጥ ደቡባዊ ክፍል በኩል ለማለፍ የሞከረ ሕገ ወጥ ነዳጅ ጫኝ መርከብ” ላይ ጥቃት መፈጸሙን አስታውቋል።

    መርከቡ “በሁለት የተጠመዱ የባሕር ፈንጂዎች በመመታቱ በእሳት እንደተያያዘ እና ሙሉ በመሉ እንደቆመ” ገልጿል። በወሽመጡ ላይ የተጣለውን “የደኅንነት መመሪያ የሚጥሱ መርከቦች ዕጣ ከዚህ ያነሰ እንደማይሆንም” አስጠንቅቋል።

    በአሜሪካ እና ኢራን መካከል ግጭት ማገርሸቱ እንዲሁም በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ የሚታየው ሁኔታ፣ የባሕር መስመሩን ለማስከፈት ጥረት ሲያደርጉ የነበሩ አካላትን ስጋት ላይ ጥሏል።

  18. በኔፓል የጎርፍ አደጋ የሞቱ ሰዎች ከ900 በላይ ሲደርስ፤ 4,200 በላይ ጠፍተዋል

    ባለፈው ሳምንት ኔፓል እና በቲቤት ድንበር ላይ በተከሰተው ድንገተኛ ጎርፍ እና የመሬት መንሸራተት አደጋ የሞቱ እና የደረሱበት ያልታወቀ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ ነው።

    አደጋው ከደረሰ ከስድስት ቀናት በኋላ የሚካሄደው ሰዎችን የመፈለግ ጥረት የቀጠለ ሲሆን፣ በተለይ የደረሱበት ያልታወቀ ሰዎች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ ጨምሯል።

    በተራራማ አካባቢው በተከሰተው በዚህ ከባድ አደጋ የሞቱት ሰዎች ቁጥር ከ150 ተነስቶ ትናንት እሁድ 781 ደርሶ የነበረ ሲሆን፣ ዛሬ ሰኞ ደግሞ ወደ 903 ተሻግሯል።

    የኔፓል ብሔራዊ የአደጋ መከላከል እና አስተዳደር ባለሥልጣን ትናንት እሁድ ባወጣው መረጃ የጠፉ ሰዎች ቁጥር 2,502 እንደሆነ አስታውቆ ነበር። ዛሬ ሰኞ ጠዋት ግን አሃዙ ወደ 4,247 ከፍ ብሏል።

    በዚህም ምክንያት አደጋው ከደረሰ ከስድስት ቀናት በኋላ የጠፉ ሰዎች ቁጥር መጨመሩ የሞቱ ሰዎች ብዛት በቀጣይ ቀናት ከፍተኛ ሊሆን ይችላል የሚል ስጋት ፈጥሯል።

    በአደጋው የተለያዩ አገራት ዜጎች እና በተለያዩ ሥራዎች ላይ ተሰማርተው የነበሩ ሰዎች ለሞት ተዳርገዋል ወይም እስካሁን የደረሱበት አልታወቀም።

    በዚህም መሠረት የደረሱበት ሳይታወቅ እየተፈለጉ ካሉት መካከል 3,655 ኔፓልያውያን እና 592 የውጭ አገራት ዜጎች ይገኙበታል።

    እንዲሁም 933 በኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ማዕከል ውስጥ ሥራ ላይ የነበሩ እና 102 የኔፓል መንግሥት ፖሊሶች፣ ወታደሮች እና የጉምሩክ መኮንኖችም ከጠፉት መካከል ናቸው።

    የጠፉትን ሰዎች የማፈላለጉ ሥራ በቀጠለበት ጊዜ፣ በየዕለቱ የበርካታ ሰዎች አስከሬኖች እየተገኘ መሆኑ የሟቾች ቁጥር ሊጨምር እንደሚችል አመልክቷል።

    በአደጋው የሞቱት እና የደረሱበት ያልታወቀ ሰዎች አብዛኞቹ ከኔፓል ሲሆን ከአጎራባቿ ቲቤትም ጥቂት የማይባሉ ሰዎች ጉዳት ደርሶባቸዋል። በቲቤት እስካሁንም 16 ሰዎች መሞታቸውን ሲረጋገጥ 546 ሰዎች ደግሞ መጥፋታቸውን የቻይና መንግሥት የመገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

  19. ኢራን በአረብ ኤምሬት ውስጥ በሚገኝ የአሜሪካ ጦር ሰፈር ላይ ጥቃት መፈጸሟን ገለጸች

    ዳግም ባገረሸው የኢራን እና የአሜሪካ ግጭት የኢራን ጦር የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ ውስጥ የሚገኝን የአሜሪካ ጦር ሰፈር ማጥቃቱን አስታወቀ።

    ሠራዊቱ እንዳለው አል-ማንሃድ በተባለው “የአሜሪካ ሄሊኮፕተሮች እና ሠራዊት ጦር ሰፈር” ላይ ጥቃት ተፈጽሟል።

    የኢራን ጦር ኃይል የሕዝብ ግንኙነት ክፍል እንዳስታወቀው ጥቃቱ የተፈጸመው እሁድ ምሽት አሜሪካ በኢራኗ ላርክ ደሴት ላይ ለፈጸመችው ጥቃት አጸፋ ነው።

    እሁድ ሌሊት የአሜሪካ ኃይሎች ላርክ ደሴት ላይ የሚገኙ ሁለት የኢራን ሚሳዔል ማስወንጨፊያዎችን ዒላማ አድርገው ጥቃት ፈጽመው ነበር።

    በምላሹም ዮርዳኖስ ውስጥ ሁለት የአሜሪካ ጦር ሰፈሮችን ዒላማ በማድረግ በሚሳዔል እና በድሮኖች ጥቃት መፈጸሙን የኢራን አብዮታዊ ዘብ አስታውቋል።

    በአሜሪካ ጥቃት የተፈጸመበት የኢራን ደሴት በፋርስ ባሕረ ሰላጤ ውስጥ ከሚገኙ የኢራን ነዳጅ ወደ ውጭ ከሚላክባቸው ስፍራዎች ዋነኛው እና ወሳኙ ነው።

    አብዛኛው የኢራን ነዳጅ ወደ ውጪ የሚላከውም በደሴቱ ላይ ከሚገኙ የነዳጅ ማስተላለፊያ ማዕከላት ነው።

  20. አሜሪካ በሳምንታት ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ኢራን ላይ ጥቃት ስትፈጽም፤ ቴህራን የአጸፋ እርምጃ ወሰደች

    የአሜሪካ ጦር ከሐምሌ ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ በኢራን በፈጸመው ጥቃት ላራክ ደሴት ላይ የሚገኙ ማስወንጨፊያዎችን መምታቱን አንድ የዋሽንግተን ባለሥልጣን ተናገሩ።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ ቃል አቀባይ ቲም ሃውኪንስ “የእስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ኃይሎች የባህር ውስጥ ፈንጂዎችን የያዙ ሮኬቶችን ወደ ሆርሙዝ ወሽመጥ ለመተኮስ ሲዘጋጁ ታይተዋል” ሲሉ በአሜሪካ የቢቢሲ አጋር ለሆነው ሲቢኤስ ኒውስ ተናግረዋል።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ እሁድ ምሽት በተፈጸመው ጥቃት ሁለት ሰዎች መገደላቸውን እና ሌሎች ሁለት ሰዎች መቁሰላቸውን አስታውቋል። ለዚህ ጥቃት “ምላሽ እና ቅጣት” እንደሚሰጥም ዝቷል።

    አብዮታዊ ዘቡ ቆየት ብሎ ባወጣው መግለጫ፣ በዮርዳኖስ በሚገኙ የአሜሪካ ወታደራዊ ዒላማዎች ላይ ጥቃት መፈጸሙን እንደገለጸ የኢራን መንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    ቢቢሲ ስለ ጥቃቱ አስተያየት ለማግኘት ለአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ ጥያቄ አቅርቧል።

    የዮርዳኖስ ጦር ከአብዮታዊ ዘቡ መግለጫ ከአጭር ጊዜ በኋላ በሰጠው ገለጻ፣ ወደ አገሪቱ የተወነጨፉ ስምንት ሚሳዔሎችን ማክሸፉን አስታውቋል።

    የዮርዳኖስ ጦር በመግለጫው “ዛሬ ሰኞ ንጋት ላይ የአገሪቱን የአየር ክልል ጥሰው የገቡ ስምንት ሚሳዔሎች በአየር መከላከያ ስርዓቶች ተጠልፈዋል” ማለቱን ‘ፔትራ' የተሰኘው የመንግሥት ዜና ወኪል ዘግቧል፥።

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ዳግም አስጀምረውት የነበረውን ወታደራዊ ዘመቻ ሐምሌ ላይ ካስቆሙ ወዲህ በሚታወቅ ደረጃ ኢራን ላይ ጥቃት ሲፈጸም የትናንት ምሽቱ የመጀመሪያው ነው።

    ላራክ ደሴት ቁልፍ ወደብ ከሆነው ‘ባንዳር አባስ’ ፊት ለፊት የሚገኝ ደሴት ነው። ስፍራው ለዓለም አቀፍ የመርከብ ጉዞ ወሳኝ በሆነው ሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ይገኛል።

    በአሁኑ ሰዓት ኢራን በወሽመጡ እንዲያልፉ የምትፈቅድላቸው ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ለፍተሻ በዚህ ደሴት በኩል እንዲጓዙ ታደርጋለች። መርከቦቹ ወሽመጡን ለማለፍ 2 ሚሊዮን ዶላር እንዲከፍሉ እያስገደደች መሆኑም ተዘግቧል።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ቃል አቀባይ ሆሴን ሞሄቢ ጥቃቱን “በትራምፕ አገዛዝ የተፈጸመ ስልታዊ እና ገዳይ ስህተት” ሲሉ ጠርተውታል። “ጠላት በኢኮኖሚያዊም ሆነ በወታደራዊ መስኮች የዚህን የተሳሳተ ስሌት መዘዝ ዋጋ ይከፍላል” ሲሉም ተናግረዋል።

    ደሴቱ ላይ የተካሄደው ጥቃት የተፈጸመው በድሮን መሆኑን ከአብዮታዊ ዘቡ ጋር ግንኙነት ያለው ታስኒም የዜና ወኪል ዘግቧል።

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ ቀጥሎ ባወጣው መግለጫ፣ በላራክ ደሴት ለደረሰው ምት በተወሰደ የአጸፋ እርምጃ፣ በዮርዳኖስ በሚገኙት ‘ኪንግ ሁሴን’ እና ‘አል አዝራቅ’ የአሜሪካ ጦር ሰፈሮች ላይ የባለስቲክ ሚሳዔል ጥቃት መፈጸሙን አስታውቋል።

    በዚህ ጥቃት “ከፍተኛ ጉዳት” ማድረሱን እና “ቴክኒካዊ መሠረተ ልማቶች፣ የጥገና ተቋማት እና የጠላት ተዋጊ ጄቶች የሚገኙባቸው ስፍራዎችን” ዒላማ ማድረጉን ገልጿል።

    አሜሪካ እና እስራኤል በየካቲት ኢራን ላይ በፈጸሙት ጥቃት የተጀመረው ይህ ጦርነት አድማሱን ወደ መካከለኛው ምሥራቅ አስፍቷል።

    ኢራን በወሰደችው የአጸፋ እርምጃ እስራኤልን፣ የአሜሪካ ጦር ሠፈሮችን እንዲሁም በባሕረ ሰላጤው የሚገኑ የአጋር አገራትን መትታለች። የሆርሙዝ ወሽመጥም ለመርከብ ጉዞ ዝግ ሆኗል። ጦርነቱ አሁን ስድስተኛ ወሩን አልፏል።