እስራኤል በደኅንነት ስጋት ምክንያት የጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ ልጅን ከአሜሪካ አስወጣች

የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ልጅ አሜሪካ ውስጥ ለሕይወቱ የሚያሰጋ ሁኔታ በመፈጠሩ እንዲወጣ መደረጉን የእስራኤል የአገር ውስጥ ደኅንነት መሥሪያ ቤት 'ሺን ቤት' አስታወቀ። የደኅንነት ተቋሙ ባወጣው መግለጫ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የመጀመሪያ ልጅ ያኢር ኔታኒያሁ ላይ ጉዳት የሚያደርስ ከፍተኛ ስጋት መኖሩን መገምገሙን እንዲሁም “ከጥበቃ ቡድኑ ጋር በአስቸኳይ ከአሜሪካ ወጥቶ ወደ እስራኤል እንዲመለስ” ውሳኔ ላይ መደረሱን ገልጿል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. የአይስላንድ ዜጎች የአውሮፓ ኅብረት አባል ለመሆን ድርድር የመጀመር ዕቅድን ውድቅ አደረጉ

    አይስላንዳውያን፣ ከ13 ዓመት በፊት የተቋረጠው እና አገራቸውን የአውሮፓ ኅብረት አባል እንድትሆን የተደረገው ድርድር እንደገና እንዲጀመር የቀረበውን ሃሳብ በሕዝበ ውሳኔ ውድቅ አደረጉ።

    ቅዳሜ ዕለት ድምፅ ከሰጡት 225,031 የአገሪቱ ዜጎች ውስጥ 52.8 በመቶ የሚሆኑት አይስላንድ መንግሥት ያቀረበውን ዕቅድ መቃወማቸውን ‘አርዩቪ’ የተባለው የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።

    47.2 በመቶ የሚሆኑት መራጮች ደግሞ ሀሳቡን ደግፈውታል። ዕቅዱን ውድቅ የማድረግ ውሳኔ ብልጫ ያገኘው በ12,600 ገደማ የድምፅ ልዩነት ነው።

    የጠቅላይ ሚኒስትር ክሪስትሩን ፍሮስታዶቲር መካከለኛ ግራ ዘመም መንግሥት ይህ ሕዝበ ውሳኔ ሊያካሄድ ያቀደው በአውሮፓውያኑ ቀጣይ ዓመት 2027 ነበር።

    ይሁን እንጂ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ግሪንላንድን እንደሚጠቀልሉ በመናገራቸው እና በሌሎች ዓለም አቀፍ ውጥረቶች ምክንያት ሕዝበ ውሳኔው ከተያዘለት ቀን አስቀድሞ ተደርጓል።

    400 ሺህ ገደማ ነዋሪዎች የሚገኙባት የደሴት አገር የተነሳው ክርክር ግን እንደ ግሪንላንድ ከደኅንነት ስጋት ይልቅ፤ የአሳ ኢንዱስትሪን የተመለከተ ነው።

    በዚህ ሕዝበ ውሳኔው በአገሪቱ መምረጥ ከሚችሉ 270,000 ገደማ ሰዎች መካከል 82.5 በመቶ የሚሆኑት ድምፅ ሰጥተዋል። ይህ ተሳትፎ በአውሮፓውያኑ 2009 ከተካደሄው ምርጫ ወዲህ ያልታየ የመራጮች ተሳትፎ መሆኑን ‘አርዩቪ’ ዘግቧል።

    አይስላንድ አሁንም ቢሆን የአውሮፓ ኅብረት የአንድ ገበያ እና ከፓስፖርት ነፃ የሸንገን ቀጣና አባል ነች። የአውሮፓ ኅብረት ሙሉ አባል መሆን የኅብረቱ የጉምሩክ ሥርዓትን እንድትቀላቀል፣ በሂደትም ዩሮ ገንዘብን እንድትጠቀም ያደርጋት ነበር።

    አይስላንድ በአውሮፓውያኑ 2008 የፋይናንስ ቀውስ ከተከሰተ እና የባንክ ሥርዓቷ ከወደቀ በኋላ በ2009 የአውሮፓ ኅብረትን ለመቀላቀል ጥያቄ አቅርባ ነበር።

    ኅብረቱን የመቀላቀል ሂደቱ በጥሩ ሁኔታ እየተጓዘ በነበረበት ወቅት በ2013 የአውሮፓ ኅብረትን የሚቃወም መንግሥት ወደ ሥልጣን በመውጣቱ ድርድሩ ተቋርጧል። በወቅቱ ዋነኛ መሰናክል የነበረው የዓሳ ማጥመድ ጉዳይ አሁንም እንቅፋት መሆኑን ቀጥሏል።

    ከአይስላንድን የውጭ ንግድ ውስጥ 40 በመቶ ገደማው የሚሸፈነው የዓሳ እና የባሕር ኢንዱስትሪ ነው።

    አውሮፓ ኅብረትን መቀላቀልን የሚቃወሙ አብዛኞቹ መራጮች፣ የኅብረቱ የጋራ የዓሳ ሀብት ፖሊሲ የሚተገበር ከሆነ ከፍተኛ ገቢ በሚያስገኙት የዓሳ ማጥመጃ ስፍራዎች ላይ ያላቸውን ቁጥጥር አሳልፈው ለመስጠት እንደሚገደዱ ያስባሉ።

  2. እስራኤል በደኅንነት ስጋት ምክንያት የጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ ልጅን ከአሜሪካ አስወጣች

    የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ልጅ አሜሪካ ውስጥ ለሕይወቱ የሚያሰጋ ሁኔታ በመፈጠሩ እንዲወጣ መደረጉን የእስራኤል የአገር ውስጥ ደኅንነት መሥሪያ ቤት 'ሺን ቤት' አስታወቀ።

    የደኅንነት ተቋሙ ባወጣው መግለጫ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የመጀመሪያ ልጅ ያኢር ኔታኒያሁ ላይ ጉዳት የሚያደርስ ከፍተኛ ስጋት መኖሩን መገምገሙን እንዲሁም “ከጥበቃ ቡድኑ ጋር በአስቸኳይ ከአሜሪካ ወጥቶ ወደ እስራኤል እንዲመለስ” ውሳኔ ላይ መደረሱን ገልጿል።

    ነገር ግን ሺም ቤት በጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ ልጅ ደኅነንት ላይ ስጋት ስለደቀነው ጉዳይ ምንነት ያለው ነገር የለም።

    ይህ ውሳኔ ይፋ የሆነው አንድ ዘገባ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ልጅ ፍሎሪዳ ውስጥ ከአንድ ዓመት በፊት የኢራን የግድያ ሴራ ዒላማ ሆኖ እንደነበረ ካመለከተ በኋላ ነው።

    አባቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ የመንግሥታቸው ደጋፊ ከሆነው የቴሌቪዥን ጣቢያ ጋር ባደረጉት የስልክ ቃለ ምልልስ ላይ “ኢራን ከልጆቼ አንዱን ዒላማ አድርጋለች። ከልጆቼ መካከል አንዱን ለመግደል ሞክራለች” ሲሉ ከስሰው ነበር።

    ኒውስማክስ የተባለው የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ረቡዕ ዕለት ባሠራጨው ዘገባ የደኅንነት ተቋማት ጥቃቱ ሊፈጸም የነበረው በኢራን ሊሆን እንደሚችል ያምናሉ ብሎ ነበር።

    ያኢር ኔታኒያሁ ለበርካታ ዓመታት ማያሚ ውስጥ ኖሯል። በኑሮውም ቅንጡ ሕይወትን የሚመራ ሲሆን በእስራኤል የደኅንነት አባላት ጥበቃ ይደረግለት ነበር።

    ሐማስ በእስራኤል ላይ ጥቃት ፈጽሞ ጋዛ ውስጥ ጦርነት እያካሄደች በነበረበት ጊዜ እስራኤላውያን ጦር ሠራዊቱን ሲያገለግሉ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ልጅ ግን ከአገር ውጪ ይኖራል የሚል ትችት ሲቀርብባቸው ነበር።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ልጃቸው አሜሪካ ውስጥ የሚደረግለትን ጥበቃ በተመለከተ ለቻናል 14 በሰጡት ቃለ ምልልስ፣ ጥበቃው ባይደረግለት ኖሮ ገዳዮቹ “ይሳካላቸው ነበር” በማለት ተከላክለዋል።

    የቀኝ ክንፍ አክቲቪስት የእና የፖድካስት አቅራቢ ሆነው ያኢር ኔታኒያሁ ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ በንቃት የሚሳተፍ ሲሆን፣ በእስራኤል ፖለቲካ ላይ አስተያየት ከመስጠት በተጨማሪ የአባቱን የፖለቲካ ተቀናቃኞች፣ የመንግሥታቸው ተቺዎችን እና ጋዜጠኞችን በማጥቃት ይታወቃል።

  3. በምርጫ ማግሥት ውጥረት ውስጥ በገባችው ዛምቢያ ተቃዋሚ ፖለቲከኛው የአገር ክህደት ክስ ተመሠረተቸባው

    ከፍተኛ የፖለቲካዊ ውጥረት በተፈጠረባት ዛምቢያ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ የሆኑት ብሪያን ሙንዱቢሌ የአገር ክህደት ክስ እንደተመሠረተባቸው ጠበቃቸው ተናገሩ።

    ሐሙስ ዕለት የታሰሩት ሙንዱቢሌ፣ ባለሥልጣናት እያካሄዱት የነበረውን ሰዎች የተገደሉበት ዘመቻ በመሸሽ ተደብቀው ነበር።

    ተቃዋሚ ፖለቲከኛው በቅርቡ አገሪቱ የተካሄደውን እና ፕሬዝዳንት ሃካይንዴ ሂቺሌማ መሪነታቸውን ለሁለተኛ የሥልጣን ዘመን ያስቀጠሉበትን የምርጫ ውጤት ተቃውመው ነበር።

    ቀጥሎም ዛምቢያ ባለሥልጣናት የሙንዱቢሌ ፓርቲ የሆነው ‘ኤንአርፒዩፒ’ በትጥቅ የታገዘ አመጽ ለማካሄድ አቅዷል የሚል ክስ አሰምተዋል። ፓርቲው ግን ክሱን ውድቅ አድርጓል።

    ተቃዋሚው ሙንዱቢሌ በአገር ክህደት ወንጀል ክስ እንደተመሠረተባቸው ጠበቃ ሚልነር ካቶሎ ቅዳሜ ምሽት ተናግረዋል።

    ጠበቃው ‘ዛምቢያን አይ’ ለተባለው መገናኛ ብዙኃን እንደተናገሩት፣ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪው ለቀረቡባቸው ክሶች በፍርድ ቤት ምላሽ ለመስጠት እየጠበቁ ነው።

    እንደ ጠበቃው ገለጻ፣ ለምክትል ፕሬዝዳንትነት በዕጩነት በመቅረብ ከሙንዱቢሌ ጋር አብረው ሲወዳደሩ የነበሩት ማኬቢ ዙሉን ጨምሮ 17 ሰዎች የአገር ክህደት ክስ ቀርቦባቸዋል።

    በነሐሴ መጀመሪያ በተካሄደው ምርጫ ሙንዱቢሌ 38 በመቶ ድምፅ ሲያገኙ፤ ፕሬዝዳንቱ ሂቺሌማ ደግሞ 60 በመቶ እንደተሰጣቸው ይፋዊው ውጤት ያሳያል።

    የፀጥታ ኃይሎች ምርጫው በተካሄደ ማግሥት፣ በዋና ከተማዋ ሉሳካ በሚገኝ እና ከሙንዱቢሌ ጋር ግንኙነት ባለው ቤት ውስጥ ብርበራ አካሂደው ነበር። በዚህ ዘመቻ የቀድሞ የካቢኔ ሚኒስትር የገደሉ ሲሆን፣ በርካታ ፖለቲከኞችንም አስረዋል።

    ሙንዱቢሌ እና ዙሉ ከዘመቻው በኋላ በከተማዋ በሚገኝ የተባበሩት መንግሥታት ሕንፃ ውስጥ ተሸሽገው ነበር። አገሪቱ ፕሬዝዳንተ ተመድ ተቃዋሚውን ፖለቲከኛ አሳልፎ እንዲሰጥ ያደረጉትን ጫና ተከትሎ ግን ሁለቱም ተይዘዋል።

    የዛምቢያ ባለሥልጣናት፣ ምርጫው ላይ በፍርድ ቤት ክስ ለማቅረብ የመጨረሻ ቀን በሆነው ሰኞ ዕለት ፍርድ ቤቶችን በመዘጋታቸው፣ ተቃዋሚዎች ውጤቱ ላይ ይግባኝ ማቅረብ አልቻሉም።

    ሂቺሌማ ነገ ሰኞ ለሁለተኛ የሥልጣን ዘመናቸው ቃለ መሀላ እንደሚፈጽሙ ይጠበቃል።

  4. የኢራን ጠቅላይ መሪ የባሕረ ሰላጤው ሙስሊም አገራት “እውነተኛ ጠላታቸውን” እንዲጋፈጡ አሳሰቡ

    የኢራን ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻሜኒ ሙስሊም አገራት፣ በተለይም በባሕረ ሰላጤው የሚገኙ መሪዎች “እውነተኛውን ጠላታቸውን” እንዲለዩ አሳሰቡ።

    ወደ ሥልጣን ከመጡ ወዲህ በግልፅ ታይተው የማይታወቁት የኢራን ጠቅላይ መሪ ዛሬ እሁድ በፅሑፍ ባተስላለፉት መልዕክት፣ በሙስሊሞች መካከል የሚፈጠር መከፋፈል የተቀናቃኝ ኃይሎችን ፍላጎት የሚያሳካ እንደሆነ ገልጸዋል።

    ሞጅታባ ኻሜኒ ይህንን መልዕክት ያስተላለፉት የነብዩ መሐመድ የልደት ቀን በሚዘከርበት የሙስሊሞች አንድነት ሳምንት ምክንያት ነው።

    ሙስሊሞች በተለያዩ መስኮች እና በጋራ የመከላከያ ዘርፍ አንድነት እንዲኖራቸው ጥሪ ያቀረቡት ጠቅላይ መሪው፣ “በማወቅም ይሁን ባለማወቅ” በሙስሊሞች መካከል ክፍፍል የሚፈጥር ማንኛውም አካል የእስልምናን ጠላቶች እየረዳ ነው ብለዋል።

    ሙስሊሞች አንድነት ቢኖራቸው ኖሮ ፍልስጤማውያን እንዲህ “እጅግ ረዳት አልባ” አይሆኑ እንደነበርም መጥቀሳቸውን የዜና ወኪሉ ሮይተርስ ዘግቧል።

    የባሕረ ሰላጤው ሕዝቦች እና መንግሥታት “በእስልምና ሰንደቅ ሥር አንድ ቢሆኑ” ኖሮ “ማንነት የሌላቸው ወሮበሎች” መሬቶቻቸውን እና ሀብቶቻቸውን ለመያዝ ይደፍሩ ነበር ወይ? ሲሉ ለባሕረ ሰላጤው አረብ መሪዎች ጥያቄ አቅርበዋል።

    "የምሰጠው ተደጋጋሚ እና ጥብቅ ምክር፣ እውነተኛ ጠላታችሁ ማን እንደሆነ ማወቅ፣ ሴራዎቻቸውን መረዳት እና መጋፈጥ አለባችሁ የሚል ነው” በማለትም ለእስላማዊ አገራት በተለይም በምዕራብ እስያ ቀጣና እና በፋርስ ባሕረ ሰላጤ ዳርቻ ለሚገኙ መሪዎች መልዕክት አስተላልፈዋል።

  5. በኔፓል እና በቲቤት ድንበር የጎርፍ አደጋ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ከ700 ሲያልፍ ከ2,800 በላይ ሰዎች የደረሱበት አልታወቀም

    በኔፓል እና ቲቤት ድንበር ላይ በተከሰተው ከባድ የመሬት መንሸራተት እና የጎርፍ አደጋ ምክንያት ሕይወታቸው ያለፈ ሰዎች ቁጥር 734 መድረሱን የኔፓል ባለሥልጣናት ተናገሩ። ከአደጋው በኋላ የደረሱበት ያልታወቀ ሰዎች ቁጥር ደግሞ 2,850 ገደማ ደርሷል።

    ረቡዕ ዕለት በተከሰተው እንዲሁም ቤቶችን እና መንገዶችን ጠራርጎ በወሰደው የጎርፍ አደጋ የተጎዱ ሰዎችን ለመታደግ የሚደረገው ጥረት አምስተኛ ቀኑን ይዟል። ለነፍስ አድን ሥራው 20 ሺህ ገደማ የፀጥታ ኃይሎች ተሰማርተዋል።

    የኔፓል ባለሥልጣናት በጎርፍ አደጋው የሞቱ ሰዎች ብዛት ትናንት ከነበረበት 675 ወደ 734 ማደጉን አስታውቀዋል።

    ቲቤት በምትገኝባት ቻይና ውስጥ ያለ የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ደግሞ በቲቤት በኩል 16 ሰዎች መሞታቸውን ገልጿል።

    ኔፓል ከ2400 በላይ ሰዎች መጥፋታቸውን ያስታወቀች ሲሆን፣ ቻይና በበኩሏ የጠፉባት ሰዎች 546 መሆናቸውን ገልጻለች። የደረሱበት ካልታወቀው ሰዎች ውስጥ 261 ያህሉ ከ23 አገራት የተወጣጡ የውጭ አገር ዜጎች ናቸው።

    ስፍራው ላይ ሌላ የጎርፍ አደጋ ሊከሰት ይችላል የሚል ስጋት ባለበት ሁኔታ ውስጥ የሚንቀሳቀሱት የነፍስ አድን ሠራተኞች፣ የአሁኑ ሰዓት በሕይወት ያሉ ተጎጂዎች ጋር ለመድረስ ወሳኝ ጊዜ መሆኑን ተናግረዋል።

    የመጀመሪያ ደረጃ ሪፖርቶች አደጋው የተከሰተው በኔፓል እና በቲቤት ድንበር ላይ የመሬት መንቀጥቀጥ በማጋጠሙ እንደሆነ ሲገልጹ ነበር። ይሁን እንጂ ጎርፉ የተከሰተው “የበረዶ ግግር በመፍረሱ” እንደሆነ የአሜሪካ የጂኦሎጂካል ሰርቬይ ተቋም አረጋግጧል።

    የተደረመሰው የበረዶ ግግር ሸለቆው ወለል ላይ ያረፈበት ኃይል እጅግ ከፍተኛ በመሆኑ 5.2 በሬክተር ስኬል የተመዘገበ ንዝረት እንዳስከተለ የተቋሙ መረጃ አመልክቷል። ይህ ንዝረትም በወንዙ የታችኛው ተፋሰስ ላይ ተከታይ አስከፊ ተጽዕኖዎችን” መፍጠሩ ተገልጿል።

  6. አሜሪካ የሚጠበቅባትን ሳትፈጽም ሆርሙዝ ወሽመጥ እንደማይከፈት ኢራን አስታወቀች

    የሆርሙዝ ወሽመጥን በሚመለከት ኢራን እና ኦማን ከመግባባት ላይ መድረሳቸውን፣ ነገር ግን ወሳኙ የባሕር ላይ መተላለፊያ የሚከፈተው አሜሪካ የሚጠበቅባትን ግዴታ ስትወጣ ብቻ መሆኑን የኢራን ባለሥልጣን ተናገሩ።

    የኢራን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ካዜም ጋሪባባዲ እንዳስታወቁት የሆርሙዝ ወሽመጥን በሚመለከት በሁለቱ አገራት መካከል በተደረገው ንግግር ለሚተላለፉ መርከቦች ጊዜያዊ የጉዞ መስመር በመክፈት ላይ ከመግባባት መደረሱን ገለጹ። ነገር ግን ሆርሙዝ የሚከፈተው አሜሪካ የሚጠበቅባትን ስትፈጽም ነው ብለዋል።

    ስለዚህም የሆርሙዝ ወሽመጥ ለመርከቦች ዝውውር ዝግ ሆኖ የሚቆይ ሲሆን፣ መርከቦች የሚያልፉ ከሆነም የኢራንን “ዕውቅና እና ፈቃድ” ማግኘት ይጠበቅባቸዋል።

    ምክትል ሚኒስትሩ “በሆርሙዝ በኩል መርከቦች በሚያልፉበት ሁኔታ ላይ ከኦማን ጋር መግባባት ላይ ደርሰናል፤ ነገር ግን አሜሪካ ግዴታዋን እስክትወጣ ድረስ መተላለፊያው ዝግ ሆኖ ይቆያል” ብለዋል።

    ከአሜሪካ የሚጠበቀው ያሉት ግዴታ ኢራን ከአሜሪካ ጋር ፓኪስታን ውስጥ በተፈራረሙት የመግባቢያ ስምምነት መሠረት ዋሽንግተን ኢራን ላይ የምትፈጽመውን ወታደራዊ ጥቃት ሙሉ ለሙሉ ማቆምን እና ቴህራን ላይ የጣለችውን የባሕር ላይ እንቅስቃሴ ዕቀባን ማንሳትን ይጨምራል።

    ይህ የኢራን ቅድመ ሁኔታ የተሰማው የሆርሙዝ ወሽመጥ አዋሳኝ አገራት በሆኑት በኦማን እና በኢራን ከፍተኛ ዲፕሎማቶች መካከል ድርድር ተደርጎ በወሽመጡ ላይ አዲስ የመተላለፊያ መስመር ለመክፈት የሚያስችል ስምምነት ላይ ከደረሱ በኋላ ነው።

    የኢራን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጋሪባባዲ “የሆርሙዝ ወሽመጥ ሙሉ ለሙሉ ዝግ ነው፣ መርከቦች የሚያልፉ ከሆነም ለኢራን ማሳወቅ እና ፈቃድ ማግኘት ይኖርባቸዋል” ሲሉ 'ፋርስ' ለተባለው የአገሪቱ ዜና ወኪል ተናግረዋል።

    በወሽመጡ ላይ ሠራዊቷን አሰማርታ ቁጥጥር እደያረገች እንደሆነ የምትናገረው አሜሪካ መርከቦች እየተላለፉ መሆናቸውን ብትገልጽም፤ የኢራኑ ባለሥልጣን ግን የአገራቸው ጦር ሠራዊት በሆርሙዝ ላይ የሚደርገውን እንቅስቃሴ እየቆጣጠረ በመሆኑ መርከቦች እየተንቀሳቀሱ ነው መባሉን “ውሸት” ሲሉ ውድቅ አድርገውታል።

  7. በኪየቭ በደረሰ ጥቃት ቢያንስ 37 ሰዎች ሲገደሉ በመቶዎች የሚቆጠሩ ደግሞ ተፈናቀሉ

    አርብ ዕለት በኪየቭ በሚገኝ መጋዘን ላይ ሩሲያ የድሮን ጥቃት ከፈጸመች በኋላ ፍንዳታ በመከሰቱ 37 ሰዎች ሲገደሉ ወደ 400 የሚጠጉ ደግሞ ከቤት ንብረታቸው ለቅቀው እንዲወጡ ተደረገ።

    ፕሬዝዳንት ቮሎዲሚር ዜሌንስኪ ፍንዳታው በአካባቢው በሚገኙ የመኖሪያ ሕንፃዎች እና በአረጋውያን የእንክብካቤ ማዕከል ላይ ጉዳት አድርሷል ብለዋል።

    በመጋዘኑ ውስጥ ተተኳሾች ተከማችተው እንደነበረ ለማወቅ ምርመራ ተጀምሯል።

    የአካባቢው አስተዳዳሪ ቲሙር ትካቼንኮ፣ ከቆሰሉት 42 ሰዎች መካከል አራት ሕጻናት እንደሚገኙበት ተናግረዋል።

    ቅዳሜ ማለዳ ላይ በቡቻ አውራጃ በሚገኘው ሥፍራ የተጎዱ ሰዎችን የመፈለግ እና የማዳን ሥራዎች እየተከናወኑ ነው።

    ዜሌንስኪ በኤክስ ገጻቸው ላይ "መመሪያዎቹ ግልጽ ናቸው። ተተኳሾችን በቤቶች ውስጥ ወይም የመኖሪያ ሕንፃዎች አቅራቢያ መቀመጥ የለባቸውም። [ከምርመራ በኋላ] ተገቢ ድምዳሜ ላይ እንደርሳለን" ሲሉ ጽፈዋል።

    ከ300 በላይ የድንገተኛ አደጋ ሠራተኞች ጥቃቱ ወደ ተፈጸመበት ማይላ መንደር መሰማራታቸውን ተናግረው በዚያም "የአረጋውያንና የአካል ጉዳተኞች የእንክብካቤ ማዕከል" ከተጎዱት ሕንጻዎች መካከል አንዱ ነው ብለዋል።

    “በግልጽ ቸልተኝነት በማሳየት የወንጀል ክስ ተከፍቷል” ሲሉ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ልጥፍ ላይ አጋርተዋል።

    የዩክሬን ዋና አቃቤ ሕግ ቢሮ በመኖሪያ ሕንፃዎች አቅራቢያ "ፈንጂዎችን እና ተቀጣጣይ ቁሳቁሶችን የማስቀመጥ እና የማከማቸት ሕጋዊነት" እየመረመረ መሆኑን አስታውቋል።

    “ይህንን ውሳኔ የወሰኑ ባለሥልጣናት ድርጊት” እንደሚጣራም ጨምሮ ገልጿል።

    የሩሲያ የመከላከያ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ ጦሩ በማይላ "ለኤፍፒ-1/ኤፍፒ-2 ረዥም ርቀት የሚጓዙ ሰው አልባ አውሮፕላኖች የሚያገለግሉ መለዋወጫዎች እና ማስተኮሻዎች" የተቀመጡበት "የተተኳሾች ማከማቻ መጋዘን" ዒላማ ማድረጉን ገልጿል።

  8. የኢራኑ ፕሬዚዳንት ትራምፕ ቀውስ መፍጠራቸውን እንዲያቆሙ በመጠየቅ ችግሮች በንግግር ይፈታሉ አሉ

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን ቅዳሜ ዕለት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ተጨማሪ ቀውስ ከመፍጠር እንዲቆጠቡ አሳስበው፣ ችግሮች በውይይት እና የመግባቢያ ስምምነቱን ተግባራዊ በማድረግ ሊፈቱ እንደሚችሉ ተናገሩ።

    ፔዜሽኪያን በቴህራን በተካሄደ ሥነ ሥርዓት ላይ "በውይይቱ እና በመግባቢያ ሰነዱ መሠረት ከቀጠልን ችግሮቹን እንፈታለን እና መብቶቻችንን እናስጠብቃለን" ሲሉ መናገራቸውን ሜህር የዜና ኤጀንሲ ዘግቧል።

    "ትራምፕ ተጨማሪ ቀውስን ባይፈጥሩ እና እስራኤል አለመረጋጋትን ባትፈጥር እና ጠብ ባትጭር ለአገሪቱ፣ ለቀጣናው እና ለዓለም ጥቅም ነው" ሲሉ አክለዋል።

    ፔዜሽኪያን ኢራን ጦርነትን እንደማትደግፍ፤ ነገር ግን ለማንኛውም ጥቃት ብርቱ ምላሽ እንደምትሰጥ ተናግረዋል።

    “ጦርነትን አንወድም፤ ነገር ግን ለየትኛውም ጠብ አጫሪነት በጽናት ቆመን ራሳችንን እንከላከላለን” ሲሉ በንግግራቸው ላይ ጠቅሰዋል።

    በተጨማሪም "ግዛቱን ለመከላከል ቆርጦ የተባበረ አንድ አገር እጅ እንዲሰጥ የሚያስገድድ ኃይል" እንደሌለም ተናግረዋል።

    ቴህራን ችግሮችን በውይይት ለመፍታት እንደምትፈልግ ቢናገሩም፣ የኢራን ሕዝብ፣ ባለሥልጣናት እና የጦር አዛዦች ለዛቻ እና ጠበኝነት "በፍፁም እጅ እንደማይሰጡ" አፅንዖት ሰጥተዋል።

    ፕሬዝዳንቱ እስራኤል በሙስሊም አገሮች መካከል ክፍፍል ለመፍጠር ትፈልጋለች ሲሉም ከስሰዋል።

    አክለውም በሙስሊም አገሮች መካከል ያለው አንድነት እንዲህ ዓይነቱን ጥረት ሊያደናቅፍ እንደሚችልም ተናግረዋል።

    ፔዜሽኪያን ሕዝቡ እንዲረጋጋ እና ከመንግሥት ጋር እንዲተባበር ጥሪ አቅርበው፣ የኢራን ጠላቶች በጫና አገሪቱን እንደምትንበረከክ ማመን የለባቸውም ብለዋል።

    እስራኤል እና አሜሪካ የካቲት 21/2018 ዓ.ም. ኢራን ላይ ጦርነት የጀመሩት የአገሪቱን ከፍተኛ ባለሥልጣናትን እንዲሁም ቁልፍ የአመራር እና ወታደራዊ ማዕከላትን ዒላማ በማድረግ ነበር።

    ነገር ግን በጦርነት እና በድርድር ውስጥ ሳትበገር የቆየችው ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን በመዝጋት በአሜሪካ እና በአካባቢው አገራት እንዲሁም በዓለም ምጣኔ ሀብት ላይ ከባድ ተጽዕኖን ማሳደር ችላለች።

    በሰኔ ወር በኢራን እና አሜሪካ መካከል የሚካሄደውን ጦርነት በተኩስ አቁም ጋብ ለማድረግ ያስችላል የተባለ የመግባቢያ ስምምነት በፓኪስታን እና ኳታር አደራዳሪነት እንዲፈራረሙ ማድረግ ተችሎ ነበር።

    ​​​​​​​ነገር ግን በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ዘላቂ መፍትሄ ላይ ባለመደረሱ ዳግም ውጥረት አገርሽቷል።

  9. የቀድሞው የዋይት ሐውስ ባልደረባ የትራምፕ ንግግር ላይ በመወራረዱ 172 ሺህ ዶላር እንዲከፍል ተፈረደበት

    የቀድሞው የዋይት ሐውስ የጽሑፍ ማንበቢያ ማሽን ተቆጣጣሪ የትራምፕ ንግግር ላይ በመወራረዱ ከ172,000 ዶላር በላይ እንዲከፍል ተፈረደበት።

    ጋብሬኤል ፔሬዝ እአአ ከኅዳር 2025 እስከ የካቲት 2026 ድረስ ፕሬዚዳንት ትራምፕ በንግግራቸው ወቅት ምን ሊሉ እንደሚችሉ በአቋማሪ ድርጅቶች በኩል ተወራርዶ በርካታ ገንዘቦችን አሸንፏል።

    አቋማሪ ድርጅቶችን የሚቆጣጠረው መሥሪያ ቤት፣ ፔሬዝ ያገኘውን 107,539.02 ዶላር ትርፍ እንዲሁም ተጨማሪ ቅጣት 65,000 ዶላር እንዲከፍል ወስኖበታል።

    የጽሑፍ ማንበቢያ ወይንም ቴሌፕሮምፕተር በጽሑፍ የተዘጋጀ ንግግርን በስክሪን ላይ የሚያሳይ ማሽን ነው። ቴሌፕሮምፕተር ባለሥልጣናት ወረቀት ሳይዙ ስክሪኑን በመመልከት ንግግራቸውን ለታዳሚዎች እንዲያቀርቡ ያስችላል።

    ከአውሮፓውያኑ 2016 አንስቶ የዋይት ሐውስ ሠራተኛ የሆነው ጋብርኤል ፔሬዝ፣ በአሜሪካው ቤተ መንግሥት የሚገኘው እና ፕሬዝዳንቱን ጨምሮ የተለያዩ ባለሥልጣናት ለንግግራቸው የሚጠቀሙበት ቴሌፕሮምፕተር ተቆጣጣሪ ነው።

    ግለሰቡ ውርርዱን ሲያካሂድ የነበረው ‘ካልሺ’ በተባለው እና ሰዎች በዓለም የሚከናወኑ ኹነቶችን በተመለከተ በመገመት መወራረድ በሚያስችለው ድረ ገጽ ላይ ነበር።

    ካልሺ የዋይት ሐውሱ ሠራተኛ ያገኘውን ትርፍ ከማውጣቱ በፊት መወራረጃ አካውንቱ እንዲታገድ ማድረጉን በወቅቱ አስታውቋል።

    ዋይት ሐውስ በቀድሞ ሠራተኛው ላይ ስለተጣለው ቅጣት እስካሁን ድረስ ያለው ነገር የለም።

    አርብ ዕለት የቅጣት ውሳኔውን ይፋ ያደረገው ተቆጣጣሪ መሥሪያ ቤት፣ የትራምፕን ንግግር ቀድሞ ማወቁን ለውርርድ “ተገቢ ባልሆነ መንገድ" መጠቀም” እንዲሁም “የተሰጠውን ኃላፊነት እና የተጣለበትን እምነት መጣስ ነው” ብሏል።

    አክሎም የተጣለበት ቅጣት ዝቅ ያለው በምርመራ ወቅት ባደረገው ትብብር የተነሳ መሆኑን አብራርቷል።

    ፔሬዝ ለሦስት ዓመት ያህል ምንም ዓይነት ውርርድ ላይ እንዳይሳተፍም ታግዷል።

    የአቋማሪ ድርጅቱ ጠበቃ ቦቢ ዴኖልት ውሳኔውን አድንቀው “ማንም ሆነ ማን መመሪያዎቻችንን ወይም የፌደራል ሕግን ከጣሰ ቅጣት ይቀበላል ” ብለዋል።

  10. በኔፓል የጎርፍ አደጋ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ከ600 በላይ ደረሰ

    በኔፓል እና ቲቤት ድንበር ላይ በደረሰው የጎርፍ አደጋ የሞቱ ሰዎች ቁጥር 626 መድረሱን የአገሪቱ ብሔራዊ የአደጋ ቅነሳ እና አስተዳደር ባለሥልጣን አስታወቀ።

    ባለሥልጣኑ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጹ ላይ ባጋራው መረጃ መሠረት 2ሺህ 426 ሰዎች አሁንም ድረስ የደረሱበት እንደማይታወቅ ይፋ አድርጓል።

    ፖሊስ ቀደም ብሎ 616 ሰዎች መሞታቸውን ገልጾ የነበረ ቢሆንም የባለሥልጣኑ መረጃ የሟቾች ቁጥር በፍጥነት እየጨመረ መምጣቱን ያሳያል።

    የደረሱበት ያልታወቁ ሰዎች ቁጥርም ከነበረበት 1,924 በፍጥነት ጨምሯል።

    በጎርፍ አደጋው 517 የውጭ አገር ዜጎች የጠፉ ሲሆን ቤተሰቦች እና ወዳጅ ዘመዶች ከመንግሥት የሚወጡ መረጃዎችን በቅርበት እየተከታተሉ ነው።

    ኔፓል ከቻይና ጋር በምትዋሰንበት ድንበር አቅራቢያ በደረሰው የጎርፍ አደጋ የሞቱ እና የጠፉ ሰዎችን እየፈለገች ባለችበት አራተኛ ቀን ያጋጠመው የአየር ጠባይ በሂሊኮፕተር የሚደረግ ሃሰሳን አስተጓጉሏል።

    የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች እና ወታደራዊ ባለሥልጣናት ከረቡዕ ጀምሮ በአደጋው የተጎዱ እና የሞቱ ሰዎችን ለማውጣት እየሰሩ ነው።

    የተወሰኑ ከአደጋው የተረፉ ሰዎች ከጭቃ ውስጥ ማውጣት የተቻለ ሲሆን የሕይወት አድን ሠራተኞች የጠፉ ሰዎችን ለማግኘት የተለያዩ ሥፍራዎች ላይ ሃሰሳ እያደረጉ ነው።

    የኔፓል ጦር ቃል አቀባይ ብርጋዴር ጄነራል ራጃ ራም ባስኔት ቅዳሜ ማለዳ የአየር ሁኔታው እስኪሻሻል ድረስ በሂሊኮፕተር የሚደረግ ፍለጋ ለጊዜው መቆሙን ተናግረዋል።

  11. በኢራን ጦርነት የተነሳ 400 መርከቦች በባሕረ ሰላጤው ቆመው እንደሚገኙ የመንግሥታቱ ድርጅት አስታወቀ

    በመካከለኛው ምሥራቅ ባለው ጦርነት 400 መርከቦች በባሕረ ሰላጤው መቆማቸውን የመንግሥታቱ ድርጅት የባሕር ኤጀንሲ አስታወቀ።

    አርብ ዕለት ዓለም አቀፉ የባሕር ላይ ድርጀት (አይኤምኦ) የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ 400 ነዳጅ ጫኝ መርከቦች እና 6,000 ባሕረተኞች በባሕረ ሰላጤው ለስድስት ወራት መንቀሳቀስ ባለመቻላቸው መቆማቸውን ገልጿል።

    የአይኤምኦ ኃላፊ አርሴኒዮ ዶሚንጌዝ “የተወሰኑ መርከቦች እና ሠራተኞቻቸው ባሕረ ሰላጤውን ማቋረጥ ቢችሉም፣ ግጭቱ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ 400 የሚሆኑ መርከቦች ከ6,000 ሠራተኞቻቸው ጋር አካባቢውን ያለምንም የደኅንነት ስጋት ለቅቀው መውጣት አልቻሉም” ብለዋል።

    የዓለም አንድ አምስተኛ ነዳጅ በሚተላለፍበት እና ወሳኝ በሆነው ሆርሙዝ ወሽመጥ ያለውን ሁኔታ “ያልተፈታ” ሲሉ ገልጸውታል።

    የመንግሥታቱ ድርጅት ኤጀንሲ የካቲት 21፣ 2018 ዓ.ም. የኢራን ጦርነት ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ በወሽመጡ በኩል የሚያልፉ መርከቦች ላይ 70 ጥቃቶች መፈጸማቸውን እና 19 ባሕረተኞች መሞታቸውን አረጋግጧል።

    ዶሚንጌዝ እንደገለጹት፣ ለነዳጅ እና ለማዳበሪያ የሚሆኑ ወሳኝ የአቅርቦት ሰንሰለቶች መስተጓጎል በዓለም ዙሪያ በሚገኙ ማኅበረሰቦች እና ኢኮኖሚዎች ላይ "ከባድ" መዘዞችን ያስከትላል።

    በተለይም "ከፍተኛ ስጋት እና እርግጠኛነት በጠፋበት ሁኔታ" ውስጥ ለሚኖሩ በሺዎች የሚቆጠሩ "ንፁኀን" ሁኔታው እጅግ አሳሳቢ መሆኑን ጠቁመዋል።

    ዶሚንጌዝ በወሽመጡ የሚደረግ የመርከብ እንቅስቃሴ ነፃነትን ወደነበረበት ለመመለስ፣ ከአባል አገራት እና ከመርከብ ትራንስፖርት ዘርፍ “አዲስ የፖለቲካ ቁርጠኝነት” እንዲኖር ጠይቀዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን በሰኔ ወር የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመው የመጨረሻውን የሰላም ስምምነት ላይ ለመድረስ ድርድር ማድረግ ጀምረው ነበር።

    ነገር ግን በኋላ ላይ በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚደረግ የመርከቦች እንቅስቃሴ ላይ መግባባት ላይ ባለመደረሱ ንግግሮቹ ተቋርጠዋል።

  12. የአሜሪካ ዲፕሎማቶች በመካከለኛው ምሥራቅ ወደሚገኙ ኤምባሲዎች መመለስ ጀመሩ

    የአሜሪካ ዲፕሎማቶች እና የተወሰኑ የቤተሰብ አባላቶቻቸው በመካከለኛው ምሥራቅ ወደሚገኙ ኤምባሲዎች መመለስ ጀመሩ።

    በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኙ ዲፕሎማቶች የኢራን ጦርነት በተጀመረ በመጀመርያዎቹ ሳምንታት ውስጥ ለቅቀው እንዲወጡ ተነግሯቸው ነበር።

    ምንም እንኳን ኤምባሲዎቹ በሙሉ አቅማቸው ወደ ሥራ ባይገቡም ከዚህ ሳምንት ጀምሮ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በሠራተኞቹ እና በእንቅስቃሴያቸው ላይ ጥሏቸው የነበሩ ገደቦችን ማንሳት ጀምሯል።

    ለውጦቹ የትራምፕ አስተዳደር በኢራን ላይ የያዘውን ፖሊሲ መለወጡን አያሳይም የተባለ ሲሆን፣ አሁን ከወታደራዊ ዘመቻ ይልቅ የኢኮኖሚ ጦርነት ማድረጉን እንደሚቀጥል ተጠቅሷል።

    የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በመካከለኛው ምሥራቅ በሚገኙ ኤምባሲዎች የሚሠሩ ዲፕሎማቶች እንዲመለሱ የወሰነው በዋናነት ከሰው ኃይል ፖሊሲ ጋር በተያያዙ ሕጋዊ ሁኔታዎች መሆኑ ተገልጿል።

    ሕጎቹ ዲፕሎማቶቹ ደመወዝና ለራሳቸውም ሆነ ለቤተሰቦቻቸው የሚሰጡ ጥቅማጥቅሞችን እያገኙ ከሥራ ቦታቸው ውጭ ሊቆዩ የሚችሉበትን ጊዜ የሚገድቡ ናቸው ተብሏል።

    የኢራን ጦርነት አርብ ዕለት ስድስተኛ ወሩን የያዘ ሲሆን በኳታር፣ ኩዌት እና ባሕሬን የሚገኙ ዲፕሎማቶች እና ቤተሰቦቻቸው እንደሚመለሱ ተነግሯል።

    በባሕሬን እና በኩዌት የሚገኙ ዲፕሎማቶች መውሰድ የሚችሉት ከ18 ዓመት በላይ የሆናቸውን የቤተሰብ አባላቶቻቸውን መሆኑም ተገልጿል።

    በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ፣ በእስራኤል የሚገኙ የአሜሪካ መንግሥት ሠራተኞች ቤተሰቦች በሙሉ እንዲሁም በሊባኖስ ከሚሠሩት ሠራተኞች ዕድሜያቸው ከ21 ዓመት በላይ የሆኑ ቤተሰቦቻቸው ወደ አገራቸው እንዲመለሱ ፈቃድ ተሰጥቷቸዋል።

    እነዚህ ኤምባሲዎች ኢራን አሜሪካ እና እስራኤል ለከፈቱባት ጦርነት የአጸፋ እርምጃ መውሰድ ስትጀምር ለቅቀው እንዲወጡ ትዕዛዝ የተሰጣቸው ናቸው።

    የኢራን ጦርነት እንደተጀመረ በሌሎች አምስት አገራት የሚገኙ የአሜሪካ ኤምባሲ ሠራተኞችም እንዲወጡ የተደረገ ሲሆን እነርሱም በቅርቡ እንዲመለሱ ሊደረግ ይችላል ተብሏል።

  13. በኔፓል የጎርፍ አደጋ የሟቾች ቁጥር 579 ሲደርስ፤ 2,000 የሚጠጉ ሰዎች የደረሱበት አልታወቀም

    ከትናንት በስቲያ በኔፓል በተከሰተው ድንገተኛ የጎርፍ አደጋ የሞቱ ሰዎች ቁጥር 579 መድረሱ ሲገለጽ፤ በሺዎች የሚቆጠሩ የደረሱበት አልታወቀም።

    የኔፓል የአደጋ ጊዜ ኤጀንሲ እንደገለጸው ከጠፉት ሰዎች መካከል ቢያንስ 517ቱ የውጭ ዜጎች ናቸው።

    ከኔፓል ጋር በምትዋሰነው የቻይናዋ ራስ ገዝ አስተዳደር ቲቤትም በአደጋው አምስት ሰዎች የሞቱ ሲሆን ከ550 በላይ የሚሆኑ መጥፋታቸውን የቻይና የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    ሁኔታዎች በፍጥነት የሚለዋወጡ በመሆኑ የተለያዩ ባለሥልጣናት የሚገልጹት ቁጥር የተለያየ ቢሆንም የሟቾች ቁጥር እየጨመረ ነው።

    አደጋው ከተከሰተ ከሁለት ቀናት በኋላም የነፍስ አድን ጥረቱ እንደቀጠለ ነው።

    የጠፉ ሰዎችን በተመለከተ የሚወጡ መረጃዎችን ወዳጅ ዘመዶቻቸው በጭንቀት እየጠበቁ ይገኛሉ።

    በቻይና እና ኔፓል ድንበር ላይ የተፈጠረው መጠኑ እየጨመረ ያለ ሐይቅ ፈንድቶ ሌላ ጎርፍ ሊያስከትል ይችላል በሚልም ተሰግቷል።

    በቲቤት የተሰማሩ የቻይና የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች፣ የሐይቁ ዳርቻዎች ተንዶ ድጋሚ የከፋ ጎርፍ ሊከሰት ይችል እንደሆነ ትናንት ጥናት ሲያደርጉ ውለዋል።

    በተፈጠረው ስጋት ምክንያትም በቲቤት የተሰማሩ የአደጋ ጊዜ ሰራተኞች ሥራቸውን እንዲያቋርጡ ተደርጓል።

    አስከፊው ድንገተኛ የጎርፍ አደጋ የተከሰተው ረቡዕ ዕለት በቲቤት በኩል ያለ የበረዶ ግግር መናዱን ተከትሎ ነው።

    አደጋው የተከሰተበት የኔፓል-ቲቤት ድንበር በየዓመቱ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ጎብኚዎችን ያስተናግዳል።

  14. በሱዳን መዲና ኻርቱም ለሁለት ዓመታት ተጥሎ የቆየው የሰዓት እላፊ ተነሳ

    በሱዳን ጦር የሚመራው መንግሥት ከሁለት ዓመት በፊት በኻርቱም ላይ ተጥሎ የነበረውን የሰዓት እላፊ እና የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማንሳቱን የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    ባለሥልጣናቱ ይህንን እርምጃ የወሰዱት ጦሩ በተፈላሚው ፈጥኖ ደራሽ ኃይል (አርኤስኤፍ) ተይዛ የነበረችውን ከተማዋን መልሶ ከተቆጣጠረ ከ18 ወራት በኋላ ነው።

    ሆኖም ግጭቱ በግዛቷ ደቡባዊ እና ምዕራባዊ አካባቢዎችም እንደቀጠለ ሲሆን ጦርነቱ ወደ ሱዳን ድንበሮች እየተዛመተ መሆኑን የሚያሳዩ መረጃዎች አሉ።

    ከአራት ዓመት በፊት በሥልጣን ሽኩቻ ሰበብ በአገሪቱ በተቀሰቀሰው ጦርነት አምስት ሚሊዮን የሚጠጉ የኻርቱም ነዋሪዎች ለመፈናቀል ተዳርገው ነበር።

    ከመጋቢት ወር ጀምሮ ግን ግጭቱ በመቆሙ ተፈናቅለው ከነበሩት ውስጥ ከ2 ሚሊዮን በላይ ነዋሪዎች መመለሳቸውን ዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት (አይኦኤም) ገልጿል።

    አሁን ላይ የሰዓት እላፊው እንዲነሳ መደረጉም በከተማ ያለውን እንቅስቃሴ ወደ መደበኛ ሁኔታ ለመመለስ ያለመ ነው።

    መንግሥት በከተማዋ ያለውን ዋና አየር ማረፊያ ለተወሰኑ በረራዎች ክፍት ያደረገ ሲሆን የንግድ ተቋማት እና ኤምባሲዎችም እንዲመለሱ እያበረታታ ነው።

    ሆኖም ነዋሪዎች አሁንም ኑሯቸውን እንደገና ለማቋቋም ተቸግረዋል።

    አብዛኞቹ ነዋሪዎች ወደ ከተማዋ ሲመለሱ በርካታ ሕንፃዎች ወድመው እና ተዘርፈው ነው ያገኙት። ከዚህም በተጨማሪ አርኤስኤፍ ቢያስተባብልም በኤሌክትሪክ መሰረተ ልማት ላይ ፈፀመው በተባለው የድሮን ጥቃት የኃይል መቋረጥ አጋጥሟቸዋል።

    አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ቢነሳም ባለሥልጣናቱ የአርኤስኤፍ ታጣቂዎች ሰርገው ሊገቡ ይችላሉ የሚልም ስጋት አላቸው። በመሆኑም በግዛቷ የደኅንነት ፍተሻ መካሄዱ የሚቀጥል እንደሆነ እና በምሽት የሚጓዙ መንገደኞችም መታወቂያ መያዝ እንደሚኖርባቸው የሱዳን የዜና ወኪል ዘግቧል።

  15. የዓለማችን በዕድሜ ትንሹ ባህላዊ ንጉሥ በ34 ዓመታቸው አረፉ

    በዓለም በዕድሜ ትንሹ ንጉሥ የነበሩት የኡጋንዳ ባህላዊ መሪ በ34 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸውን ጠቅላይ ሚኒስትራቸው አስታወቁ።

    ኦዮ ኒይምባ ካባማ ኢጉሩ ሩኪዲ አራተኛ የአባታቸውን ሞት ተከትሎ ነበር በአውሮፓውያኑ 1995 በሦስት ዓመታቸው የቶሮ ንጉሥ ሆነው የተሰየሙት።

    ይህም የዓለማችን በዕድሜ ትንሹ ንጉሥ እንዲሆኑ ያደረጋቸው ሲሆን፣ 18 ዓመት እስከሚሞላቸው ድረስ እናታቸው በተካተቱበት እና ሦስት አባላት ባሉት ምክር ቤት ንጉሣዊ ሥርዓቱ ሲመራ ነበር።

    የቶሮ ግዛት የንጉሡን ሞት መንስዔ አልገለጸም። ሆኖም የአገሪቷ መገናኛ ብዙኃን አንድ የኡጋንዳን መንግሥት ሚኒስትር ጠቅሶ እንደዘገበው ንጉሡ በጠና ታመው በአሜሪካ ህክምና ሲደረግላቸው ነበር።

    ቶሮ በምዕራብ ኡጋንዳ የሚገኝ እና ረዥም ታሪክ ባለው ጥንታዊ የባንቱ ባህላዊ መንግሥት የሚመራ ግዛት ነው።

    ኡጋንዳ በሕዝብ በተመረጠ ፕሬዝዳንት ብትመራም፣ ፖለቲካዊ ሥልጣን ባይኖራቸውም ተፅእኖ መፍጠር የሚችሉ በርካታ ባህላዊ መሪዎች አሏት።

    በዓለም የድንቃ ድንቅ መዝገብ ውስጥ የዓለማችን በዕድሜ ትንሹ ባህላዊ ንጉሥ በሚል ስማቸው የሰፈረው ኦዮ፣ ከ2 ሚሊዮን በላይ የሚገመት የቶሮን ሕዝብ ሲመሩ ነበር። ኦዮ በ19ኛው ክፍለ ዘመን የተመሠረተው ንጉሣዊ ሥርዓት 13ኛው ንጉሥ ነበሩ።

    ሕልፈታቸውን ያስታወቁት የቶሮ ጠቅላይ ሚኒስትር ካልቪን አርምስትሮንግ ሪዎማይር፣ የንጉሡ ህልፈት ለንጉሣውያን ቤተሰቦች እና ለቶሮ ሕዝብ “ትልቅ እጦት” ነው ብለዋል።

    “በዚህ ከባድ ወቅት የቶሮ ሕዝብ በአንድነት፣ በመረጋጋት እና በፀሎት እንዲቀጥል ጥሪ አቀርባለሁ” ሲሉም ንጉሣ በሰላም እንዲያርፉ ተመኝተዋል።

    የቶሮ ግዛት ንጉሡን ለመምረጥ በዘር የሚተላለፍ ንጉሣዊ ሥርዓትን ይከተላል። ኦዮ በይፋ ስላላገቡ ዘውዱን ማን ይረከባል የሚለው አይታወቅም። ሆኖም ጠቅላይ ሚኒስትራቸው “የዘውዱ ሽግግር የተረጋገጠ ነው” ብለዋል።

    ግርማዊነታቸው “ወራሽ የሆነ ልዑል ትተው ነው ያረፉት። ማንነቱ በተገቢው ጊዜ፣ በቶሮ መንግሥት ወግ እና ባህል መሠረት ይገለጻል” ሲሉ አስረድተዋል።

    ኦዮ በሕዝብ ዘንድ የተወደዱ እና በወጣቶች አቅም ማጎልበት፣ በትምህርት እና በአካባቢ ጥበቃ እንዲሁም በኤችአይቪ/ኤድስ ግንዛቤ ማስጨበጥ ሥራዎችን ሲያበረታቱ እንደነበር ዴይሊ ሞኒተር ጋዜጣ ዘግቧል።

  16. ሁሉም አገራት የአሜሪካን ማዕቀብ ከመተግበር እንዲቆጠቡ ኢራን አሳሰበች

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር “የኢኮኖሚ ሽብር” ሲል የገለፀውን የአሜሪካን ማዕቀብ በማውገዝ፣ ሁሉም አገራት እና መንግሥታት ማዕቀቡን ተግባራዊ ከማድረግ እንዲቆጠቡ አሳሰበ።

    ሚኒስቴሩ በመግለጫው፣ አሜሪካ በኢራን ላይ የጣለችውን የአንድ ወገን ማዕቀብ በመተግበር መሳተፍ የአንድን አገር "ሕገ ወጥ ፈቃድ" በሉዓላዊ አገር ላይ በመጣል ሕጋዊ የሆነውን "የኢኮኖሚ እና የንግድ ግንኙነትን ለማወክ ከመተባበር" ጋር ተመሳሳይ ነው ብሏል።

    ይህም የተባበሩት መንግሥታት ቻርተር የሚያረጋግጠው ‘የሉዓላዊ አገራት እኩልነት’ መርኅ ጥሰት ላይ መሳተፍ እንደሆነ መግለጫው አስረድቷል።

    የአሜሪካ ማዕቀቦች "ሙሉ በሙሉ ሕገ ወጥ እና ኢ- ፍትሃዊ እንዲሁም የተባበሩት መንግሥታትን ቻርተር፣ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊነት ሕግን እና የሰብዓዊ መብቶችን" የሚጥስ እንደሆነም መግለጫው ጠቅሷል።

    በመሆኑም ሁሉም አገራት እና መንግሥታት ለእንደዚህ ዓይነት ማዕቀቦች ዕውቅና ከመስጠት እና ከማጽደቅ እንዲሁም ሕገ ወጥ እርምጃን ከመተግበር መቆጠብ እንዳለባቸው አሳስቧል።

    ሚኒስቴሩ ጨምሮም አሜሪካ ኢራንን በኢኮኖሚ ለማግለል የወጠነችው ዕቅድ “በውስጥ ጉዳዮች ጣልቃ መግባትን እና በአገራት መካከል የሚደረገውን ትብብር ማወክን” የሚከለክለውን የተባበሩት መንግሥታትን መርኅ የሚጥስ ነው ብሏል።

    ሚኒስቴሩ ይህን ያለው አሜሪካ ከኢራን ጋር የንግድ ግንኙነት ባላቸው ተቋማት፣ ባንኮች እና አገራት ላይ ጭምር ማዕቀቦችን በመጣል እንደምትቀጣ ካስታወቀች በኋላ ነው።

  17. ከአሜሪካ ጋር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትን መመለስ እንደሚቻል የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ገለፁ

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ከኳታሩ ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጋር ቴህራን ውስጥ ካደረጉት ንግግር በኋላ፣ ከአሜሪካ ጋር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትን ወደነበረበት መመለስ “የማይቻል አይደለም” ሲሉ ተናገሩ።

    አራግቺ ከኳታሩ ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሼኽ ሞሐመድ ቢን አብዱልራህማን ቢን ጃሲም አል ታኒ ጋር “ውጤታማ ውይይት” እንዳደረጉ በኤክስ ገጻቸው ላይ ተናግረዋል።

    “ዲፕሎማሲን ወደ ትክክለኛው መንገድ መመለስ የማይቻል አይደለም። ይህ የሚወሰነው አሜሪካ በአንድ ቀላል እውነታ ላይ በሚኖራት ግንዛቤ ነው፤ ጫና መፍጠር አይሰራም” ብለዋል።

    “አሜሪካ እምነትን መገንባት፣ በአክብሮት መናገር፣ መብቶቻችንን መቀበል እና የገባችውን ቃል መፈፀም አለባት” ሲሉ የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አክለዋል።

    በኢራን እና አሜሪካ መካከል ያለውን ውጥረት ለማርገብ ዶሃ እየሠራች ባለችበት ወቅት ነው ሼኽ ሞሐመድ ሐሙስ ዕለት በቴህራን ጉብኝት ያደረጉት።

    በጉብኝታቸውም ከኢራኑ ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን፣ ከአራግቺ፣ ከፓርላማ አፈጉባዔው ሞሐመድ ባገር ጋሊባፍ እና ከኢራን ጠቅላይ ብሔራዊ የደኅንነት ምክር ቤት ፀሐፊ ሞህሰን ረዛኢ ጋር ተነጋግረዋል።

    በአሜሪካ እና ኢራን መካከል የተጀመረውን ውይይት ማስቀጠል የሚቻልበትን ሁኔታ መፍጠር እንዲሁም በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ጊዜያዊ የጋራ የመርከብ መተላለፊያ መንገድ ማበጀት እና አካባቢውን ከፈንጂዎች እና ሌሎች መሣሪያዎች የማፅዳት ጥረቶች የተነጋገሩባቸው ጉዳዮች ናቸው።

    የአሜሪካ እና እስራኤልን ጥቃት ተከትሎ የካቲት ወር ላይ ጦርነቱ ከተቀሰቀሰ ወዲህ የኳታር የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በኢራን ጉብኝት ሲያደርጉ የአሁኑ የመጀመሪያቸው ነው።

  18. የሱዳን ጦር ከሁለት ዓመት በላይ በካርቱም ጥሎት የነበረውን የሰዓት እላፊ አነሳ

    የሱዳን ጦር ከሁለት ዓመት በላይ በካርቱም ላይ ጥሎት የነበረውን የሰዓት እላፊ ማንሳቱን የአገሪቱ ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን ዘገበ።

    የጦሩ ባለሥልጣናት የሰዓት እላፊውን ያነሱት ከተማዋን ከፈጥኖ ደራሽ ኃይሉ ካስለቀቁ ከ18 ወራት በኋላ ነው።

    በሱዳን እየተካሄደ ያለው የእርስ በእርስ ጦርነት ከካርቱም ውጭ ባሉ የአገሪቱ ከተሞች እንደቀጠለ ነው።

    የአገሪቱ ጦር ካርቱምን ከአማጺያኑ ካስለቀቀ በኋላ ከሁለት ሚሊዮን በላይ ሰዎች ወደካርቱም ተመልሰው መደበኛ ሕይወታቸውን ቀጥለዋል።

    ነገር ግን በጦርነት ምክንያት በርካታ መሠረተ ልማቶች በመውደማቸው በተደጋጋሚ የኤሌትሪክ መቆራረጥ እንደሚያጋጥማቸው ይነገራል።

    የፈጥኖ ደራሹ ኃይሎች ወደ ከተማዋ ሰርገው እንዳይገቡ ለመከላከል የጦሩ አባላት በየጊዜው የቅኝት ስራ እንደሚሰሩ የአገሪተ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    በምሽት የሚንቀሳቀሱ የከተማዋ ነዋሪዎችም ማንነታቸውን የሚገልጽ መታወቂያ ይዘው እንዲንቀሳቀሱ አሳስበዋል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ ቻድ የሱዳን ጦር በድንበር አቅራቢያ በፈጸመው የአየር ድብደባ የአገሪቱ ጦር ላይ ጉዳት ማድረሱን ገልጻ ከስሳለች።

    የሱዳን ጦር የቻድ መንግሥት ክስን ውድቅ አድርጓል።

    የአሜሪካ መንግሥት የሱዳን ጦርነት ከአገሪቱ ድንበር ሊያልፍ ይችላል የሚል ስጋት እንዳለው ገልጿል።

  19. የአሜሪካ ጦር በአውሮፓ "ከፍተኛ የሚሳዔል መቃወሚያ እጥረት" እንደገጠመው ተዘገበ

    የአሜሪካ መከላከያ በኢራን እያካሄደ ካለው ጦርነት ጋር በተያያዘ በአውሮፓ ከፍተኛ የሆነ ዘመናዊ የሚሳዔል መቃወሚያዎች እጥረት እንደገጠመው የፈረንሳዩ የዜና ወኪል ዘገበ።

    አሶሼትድ ፕሬስ የአሜሪካ መከላከያ ባለሥልጣናትን እና የኔቶ ኃላፊዎችን ጠቅሶ እንደዘገበው ጦሩ “እጅግ ወሳኝ በሆነ ደረጃ” ላይ የሚገኝ ዘመናዊ የሚሳኤል መቃወሚያ እጥረት አጋጥሞታል።

    ይህ ሁኔታ የኔቶ አባል አገራት ከሩሲያ ሊሰነዘር ለሚችል ጥቃት ተጋላጭ የሚያደርግ በመሆኑ ስጋት መፈጠሩን ጨምረው አስረድተዋል።

    የአሜሪካ መከላከያ ባለሥልጣናት እጥረቱ በይበልጥ የተፈጠረው የሩሲያን ተምዘግዛጊ ባሌስቲክ ሚሳዔልን መትቶ መጣል በሚችለው ፓትሮይት ተብሎ በሚጠራው የሚሳዔል መቃወሚያ ላይ ነው ብለዋል።

    የኔቶ ኃላፊዎች በአሜሪካ ጦር እና በአውሮፓ በሚገኙ የኔቶ አባል አገራት ዘንድ የፓትሮይት ሚሳዔል እጥረት መኖሩን አረጋግጠዋል።

    ስማቸው እንዳይገለጽ የጠየቁ ኃላፊዎች በአውሮፓ የሚገኘው የአሜሪካ ጦር “በእርግጠኝነት” ከሩሲያ ሊተኮስ የሚችል ባሌስቲክን የሚያከሽፍበት ፓትሮይት ሚሳዔል እጥረት አለበት ብለዋል።

    ኃላፊዎቹ ከሩሲያ ለሚሰነዘር ማንኛውንም የባሌስቲክ ሚሳዔል ጥቃት ለመከላከል ያለው አቅም “በጣም ውስን” መሆኑን ጨምረው ገልጸዋል።

    ምንም እንኳን በኔቶ አባል አገራት ላይ ሩሲያ የባለስቲክ ሚሳዔል ጥቃት ትፈጽማለች ተብሎ ባይጠበቅም የሲአይኤ ዳይሬክተር ጆን ራትክሊፍ በዚህ ሳምንት ወደ ሞስኮ ተጉዘው ሩሲያ ጥቃት እንዳትፈጽም ማስጠንቀቃቸውን ዎል ስትሪት ጆርናል ዘግቧል።

    ሐሙስ ዕለት የሲአይኤ ኃላፊ መልዕክቱን ለፑቲን አድርሰው እንደሆን የተጠየቁት ትራምፕ “በዚህ ጉዳይ ላይ አስተያየት መስጠት አልፈልግም፤ ነገር ግን ጥቃት አይፈጽሙም” ሲሉ በደፈናው መልሰዋል።

  20. ትራምፕ አሜሪካንን ከመሩ ፕሬዝዳንቶች ሁሉ የተለየሁ ነኝ አሉ

    አነጋጋሪ ጉዳዮችን በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ በማጋራት የሚታወቁት ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ራሳቸውን እስካሁን አሜሪካንን ከመሩ ፕሬዝዳንቶች ሁሉ የላቁ መሆናቸውን ገለጹ።

    የመጀመሪያዎቹን ጨምሮ በፈታኝ ሁኔታ ውስጥ አሜሪካንን የመሩ የ34 ፕሬዝዳንቶችን ምሥል በመደርደር የተለያዩ ደረጃዎችን የሰጡት ትራምፕ ራሳቸውን “ከሁሉም ያላቁ” አድርገው በማቅረብ መነጋገሪያ ሆነዋል።

    በትሩዝ ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ በአሜሪካ ፕሬዝዳንቶች ታሪክ ራሳቸውን “የታላቆች ታላቅ” በሚለው ደረጃ ላይ በማስቀመጥ ሌሎቹን በተለያዩ ደረጃዎች “ደካማ” እስከሚል ፈርጀው ከእሳቸው ስር አስቀምጠዋቸዋል።

    በርካቶቹን የአሜሪካ ቀደምት ፕሬዝዳንቶች ከዝርዝሩ ውስጥ ባለማካተትም ቦታ ነፍገዋቸዋል። ምናልባትም ያልተካተቱት “ደካማ” ከተባሉት በታች ያሏቸውን ሊሆን ይችላል።

    ከአውሮፓውያኑ 1789 አሜሪካ 47 ፕሬዝዳንቶች ተፈራርቀው የመሯት ሲሆን፣ በትራምፕ የደረጃ ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት ግን 34ቱ ብቻ ናቸው። የዓለማችን የዲሞክራሲ ተምሳሌት የምትባለውን አገር እስካሁን ሴት ፕሬዝዳንት አልመራቻትም።

    ትራምፕ ከንጽጽር ያቀረቧቸውን ቀደምት ፕሬዝዳንቶች በስድስት ክፍል የመደቧቸው ሲሆን፣ ራሳቸውን “የታላላቆች ታላቅ”፣ እርሳቸውን የሚከተሉትን ደግሞ “ታላቅ”፣ ከዚያም “ለታላቅነት የቀረቡ”፣ “መካከለኛ”፣ “ከመካከለኛ በታች” እና ደካሞች” ብለዋቸዋል።

    “ደካማ” ከሚለው ምድብ ስር ያካተቷቸው ከእሳቸው የቀደሙትን ባራካ ኦባማ እና ጆ ባይደንን እንዲሁም ጂሚ ካርተር፣ ዋረን ሃርዲንግ እና ኡሊሴስ ግራንት ይገኙበታል።