የአይስላንድ ዜጎች የአውሮፓ ኅብረት አባል ለመሆን ድርድር የመጀመር ዕቅድን ውድቅ አደረጉ
አይስላንዳውያን፣ ከ13 ዓመት በፊት የተቋረጠው እና አገራቸውን የአውሮፓ ኅብረት አባል እንድትሆን የተደረገው ድርድር እንደገና እንዲጀመር የቀረበውን ሃሳብ በሕዝበ ውሳኔ ውድቅ አደረጉ።
ቅዳሜ ዕለት ድምፅ ከሰጡት 225,031 የአገሪቱ ዜጎች ውስጥ 52.8 በመቶ የሚሆኑት አይስላንድ መንግሥት ያቀረበውን ዕቅድ መቃወማቸውን ‘አርዩቪ’ የተባለው የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።
47.2 በመቶ የሚሆኑት መራጮች ደግሞ ሀሳቡን ደግፈውታል። ዕቅዱን ውድቅ የማድረግ ውሳኔ ብልጫ ያገኘው በ12,600 ገደማ የድምፅ ልዩነት ነው።
የጠቅላይ ሚኒስትር ክሪስትሩን ፍሮስታዶቲር መካከለኛ ግራ ዘመም መንግሥት ይህ ሕዝበ ውሳኔ ሊያካሄድ ያቀደው በአውሮፓውያኑ ቀጣይ ዓመት 2027 ነበር።
ይሁን እንጂ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ግሪንላንድን እንደሚጠቀልሉ በመናገራቸው እና በሌሎች ዓለም አቀፍ ውጥረቶች ምክንያት ሕዝበ ውሳኔው ከተያዘለት ቀን አስቀድሞ ተደርጓል።
400 ሺህ ገደማ ነዋሪዎች የሚገኙባት የደሴት አገር የተነሳው ክርክር ግን እንደ ግሪንላንድ ከደኅንነት ስጋት ይልቅ፤ የአሳ ኢንዱስትሪን የተመለከተ ነው።
በዚህ ሕዝበ ውሳኔው በአገሪቱ መምረጥ ከሚችሉ 270,000 ገደማ ሰዎች መካከል 82.5 በመቶ የሚሆኑት ድምፅ ሰጥተዋል። ይህ ተሳትፎ በአውሮፓውያኑ 2009 ከተካደሄው ምርጫ ወዲህ ያልታየ የመራጮች ተሳትፎ መሆኑን ‘አርዩቪ’ ዘግቧል።
አይስላንድ አሁንም ቢሆን የአውሮፓ ኅብረት የአንድ ገበያ እና ከፓስፖርት ነፃ የሸንገን ቀጣና አባል ነች። የአውሮፓ ኅብረት ሙሉ አባል መሆን የኅብረቱ የጉምሩክ ሥርዓትን እንድትቀላቀል፣ በሂደትም ዩሮ ገንዘብን እንድትጠቀም ያደርጋት ነበር።
አይስላንድ በአውሮፓውያኑ 2008 የፋይናንስ ቀውስ ከተከሰተ እና የባንክ ሥርዓቷ ከወደቀ በኋላ በ2009 የአውሮፓ ኅብረትን ለመቀላቀል ጥያቄ አቅርባ ነበር።
ኅብረቱን የመቀላቀል ሂደቱ በጥሩ ሁኔታ እየተጓዘ በነበረበት ወቅት በ2013 የአውሮፓ ኅብረትን የሚቃወም መንግሥት ወደ ሥልጣን በመውጣቱ ድርድሩ ተቋርጧል። በወቅቱ ዋነኛ መሰናክል የነበረው የዓሳ ማጥመድ ጉዳይ አሁንም እንቅፋት መሆኑን ቀጥሏል።
ከአይስላንድን የውጭ ንግድ ውስጥ 40 በመቶ ገደማው የሚሸፈነው የዓሳ እና የባሕር ኢንዱስትሪ ነው።
አውሮፓ ኅብረትን መቀላቀልን የሚቃወሙ አብዛኞቹ መራጮች፣ የኅብረቱ የጋራ የዓሳ ሀብት ፖሊሲ የሚተገበር ከሆነ ከፍተኛ ገቢ በሚያስገኙት የዓሳ ማጥመጃ ስፍራዎች ላይ ያላቸውን ቁጥጥር አሳልፈው ለመስጠት እንደሚገደዱ ያስባሉ።