በኦሮሚያ ክልል የደገም ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ በታጣቂዎች ተገደሉ

የፎቶው ባለመብት, Paartii Badhaadhinaa Damee Dagam
በኦሮሚያ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ደገም ወረዳ ታጣቂዎች ትናንት እሁድ ነሐሴ 17/2018 ዓ.ም. በፈጸሙት ጥቃት የወረዳው ዋና አስተዳዳሪ ተፈራ ደሴ መገደላቸውን ምንጮች ለቢቢሲ ተናገሩ።
በጥቃቱ በወረዳው የምትገኘው አኖ ቀሬ ቀበሌ ሊቀ መንበር አስፋወሰን ኃይሌን ጨምሮ ሌሎች ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ ሰዎች ጉዳት እንደደረሰባቸውም ተገልጿል።
የዞኑ የፀጥታ መዋቅር ምንጮች ለቢቢሲ አፋን ኦሮሞ እንደተናገሩት፣ ዋና አስተዳዳሪው የተገደሉት እሁድ ከሰዓት በኋላ ሲሆን ጥቃት የተፈጸመው በደገም ወረዳ አኖ ቀሬ ቀበሌ ውስጥ ነው።
በዕለቱ በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች እና በታጣቂዎች መካከል የተኩስ ልውውጥ ሲደረግ እንደነበር ምንጮቹ አስረድተዋል። የቀበሌ ሊቀ መንበሩን ጨምሮ ጉዳት የደረሰባቸው ሰዎች በሰላሌ ዩኒቨርሲቲ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ሕክምና እያገኙ መሆኑንም ጠቅሰዋል።
ቢቢሲ ያነጋገራቸው ምንጮች፣ በመንግሥት ባለሥልጣናቱ ላይ ለተከፈተው ጥቃት ተጠያቂ ያደረጉት በክልሉ የሚንቀሳቀሱትን የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት (ኦነሠ) ታጣቂዎችን ነው። ታጣቂ ቡድኑ እስካሁን ስለ ጥቃቱ መረጃ ያለው ነገር የለም።
የደገም ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ የአቶ ተፈራን መገደል በተመለከተ ከክልሉ መንግሥትም ይሁን ከሰሜን ሸዋ ዞን አስተዳደር የተሰጠ አስተያየት የለም። ቢቢሲ ከዞኑ ዋና አስተዳደሪ መረጃ ለማግኘት ያደረገው ጥረት አልተሳካም።
በክልሉ በሰሜን ሸዋ ዞን ውስጥ ባለልጣናትን ዒላማ ያደረገ ጥቃት ሲፈጸም ይህ የመጀመሪያው አይደለም።
በየካቲት 2017 ዓ.ም. ሱሉልታ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አበበ ወርቁ በታጣቂዎች መገደላቸው ይታወሳል።
መንግሥት በሽብር ቡድንነት የፈረጀው እና 'ሸኔ' ብሎ የሚጠራው የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት በወቅቱ በወጣው መግለጫው ለጥቃቱ ኃላፊነቱን ወስዷል።
በዚያው ዓመት ታኅሣሥ ላይ ደግሞ የዞኑ የውሃ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ስዩም አበራ፣ የዞኑ አደጋ መከላከል ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ጌታሁን እጄታ እና የዞኑ የፋይናንስ ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሙሉነህ ግዛው ተገድለዋል።
ጥቅምት ላይ በተመሳሳይ የወጫሌ ወረዳ አስተዳዳሪ የሆኑት ንጉሤ ኮሩን ጨምሮ ከ45 በላይ ሰዎች የሚሆኑ የመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች መገደላቸውን ነዋሪዎች ለቢቢሲ አፋን ኦሮሞ ተናግረው ነበር።





