በምርጫ ማግሥት ውጥረት ውስጥ በገባችው ዛምቢያ ተቃዋሚ ፖለቲከኛው የአገር ክህደት ክስ ተመሠረተቸባው
ከፍተኛ የፖለቲካዊ ውጥረት በተፈጠረባት ዛምቢያ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ የሆኑት ብሪያን ሙንዱቢሌ የአገር ክህደት ክስ እንደተመሠረተባቸው ጠበቃቸው ተናገሩ።
ሐሙስ ዕለት የታሰሩት ሙንዱቢሌ፣ ባለሥልጣናት እያካሄዱት የነበረውን ሰዎች የተገደሉበት ዘመቻ በመሸሽ ተደብቀው ነበር።
ተቃዋሚ ፖለቲከኛው በቅርቡ አገሪቱ የተካሄደውን እና ፕሬዝዳንት ሃካይንዴ ሂቺሌማ መሪነታቸውን ለሁለተኛ የሥልጣን ዘመን ያስቀጠሉበትን የምርጫ ውጤት ተቃውመው ነበር።
ቀጥሎም ዛምቢያ ባለሥልጣናት የሙንዱቢሌ ፓርቲ የሆነው ‘ኤንአርፒዩፒ’ በትጥቅ የታገዘ አመጽ ለማካሄድ አቅዷል የሚል ክስ አሰምተዋል። ፓርቲው ግን ክሱን ውድቅ አድርጓል።
ተቃዋሚው ሙንዱቢሌ በአገር ክህደት ወንጀል ክስ እንደተመሠረተባቸው ጠበቃ ሚልነር ካቶሎ ቅዳሜ ምሽት ተናግረዋል።
ጠበቃው ‘ዛምቢያን አይ’ ለተባለው መገናኛ ብዙኃን እንደተናገሩት፣ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪው ለቀረቡባቸው ክሶች በፍርድ ቤት ምላሽ ለመስጠት እየጠበቁ ነው።
እንደ ጠበቃው ገለጻ፣ ለምክትል ፕሬዝዳንትነት በዕጩነት በመቅረብ ከሙንዱቢሌ ጋር አብረው ሲወዳደሩ የነበሩት ማኬቢ ዙሉን ጨምሮ 17 ሰዎች የአገር ክህደት ክስ ቀርቦባቸዋል።
በነሐሴ መጀመሪያ በተካሄደው ምርጫ ሙንዱቢሌ 38 በመቶ ድምፅ ሲያገኙ፤ ፕሬዝዳንቱ ሂቺሌማ ደግሞ 60 በመቶ እንደተሰጣቸው ይፋዊው ውጤት ያሳያል።
የፀጥታ ኃይሎች ምርጫው በተካሄደ ማግሥት፣ በዋና ከተማዋ ሉሳካ በሚገኝ እና ከሙንዱቢሌ ጋር ግንኙነት ባለው ቤት ውስጥ ብርበራ አካሂደው ነበር። በዚህ ዘመቻ የቀድሞ የካቢኔ ሚኒስትር የገደሉ ሲሆን፣ በርካታ ፖለቲከኞችንም አስረዋል።
ሙንዱቢሌ እና ዙሉ ከዘመቻው በኋላ በከተማዋ በሚገኝ የተባበሩት መንግሥታት ሕንፃ ውስጥ ተሸሽገው ነበር። አገሪቱ ፕሬዝዳንተ ተመድ ተቃዋሚውን ፖለቲከኛ አሳልፎ እንዲሰጥ ያደረጉትን ጫና ተከትሎ ግን ሁለቱም ተይዘዋል።
የዛምቢያ ባለሥልጣናት፣ ምርጫው ላይ በፍርድ ቤት ክስ ለማቅረብ የመጨረሻ ቀን በሆነው ሰኞ ዕለት ፍርድ ቤቶችን በመዘጋታቸው፣ ተቃዋሚዎች ውጤቱ ላይ ይግባኝ ማቅረብ አልቻሉም።
ሂቺሌማ ነገ ሰኞ ለሁለተኛ የሥልጣን ዘመናቸው ቃለ መሀላ እንደሚፈጽሙ ይጠበቃል።