ኢራን ከዚህ በኋላ ለአሜሪካ ጥቃት የምትሰጠው ምላሽ ከሚጠበቀው በላይ የከፋ ይሆናል አለች
አሜሪካ በዚህ ሳምንት በኢራን ዒላማዎች ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት መልሳ መጀመሯን ተከትሎ ከዚህ በኋላ ኢራን ለሚፈጸምባት ጥቃት የምትመልሰው አጸፋ ከሚጠበቀው በላይ እንደሚሆን የአገሪቱ ምክትል ፕሬዝዳንት ተናገሩ።
የኢራን ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዝዳንት ሞሐመድ ሬዛ አሬፍ፣ አሜሪካ ባለፉት ቀናት በኢራን ላይ የፈጸመቻቸውን ጥቃቶች “ወንጀል” ሲሉ ገልጸው፣ “ከእንግዲህ በኋላ የእኛ ምላሽ ሚዛናዊ አይሆንም” ብለዋል።
ምክትል ፕሬዝዳንቱ በኤክስ የማኅበራዊ ትስስር ገጽ ላይ ባሰፈሩት ጽሑፍ፣ “አሜሪካ በኢራን ሕዝብ ላይ የፈጸመቻቸው አዳዲስ ወንጀሎች የእኛን የደኅንነት ስሌቶች እና የመከላከያ መርኅን ቀይረውታል” ሲሉ ጽፈዋል።
ይህንንም ተከትሎ በአሜሪካ ለሚፈጸሙ ጥቃቶች “ከዚህ በኋላ የምንሰጠው ምላሽ ሚዛናዊ ያልሆነ፣ በበርካታ ደረጃዎች የሚፈጸም እና የአጥቂውን ደኅንነት የሚያሳጣ ይሆናል” ሲሉም አክለዋል።
የኢራኑ የተቀዳሚ ምክትል ፕሬዝዳንት በመጨረሻም “አሜሪካውያን ቤንዚን እና ሌሎች ነዳጆችን ስለማከማቸት ማሰብ ይኖርባቸዋል” በማለትም አስጠንቅቀዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የኢራን ፓርላማ የብሔራዊ ደኅንነት እና የውጭ ጉዳይ ኮሚቴ ኃላፊ ኢብራሂም አዚዚ፣ ኢራን እስካላፈቀደች ድረስ የሆርሙዝ ወሽመጥ ለመርከቦች እንቅስቃሴ ዝግ ሆኖ እንደሚቆይ ተናገሩ።
የአገሪቱ ምክር ቤት ከፍተኛ ባለሥልጣኑ “የሆርሙዝ ወሽመጥ ያለ እስላማዊት ሪፐብሊክ ኢራን ፈቃድ አይከፈትም፤ ይህም በግልጽ የሚታይ ነው” በማለት በአሁኑ ወቅት ያለውን ሁኔታ ጠቅሰዋል።
አዚዚ እንዳሉት፣ አሜሪካ ባለፉት ስድስት ወራት ወሳኙን የባሕር መተላለፊያ ለማስከፈት ያደረገቸው ጥረት ስላልተሳከ በአሁኑ ጊዜ “ክፉ ድርጊቶችን እየፈጸመች ነው” ሲሉ ከስሰዋል።
አሜሪካ በወታደራዊ ጥቃት በኢራን ላይ ጫና ለማሳደር ከምደታርገው ዘመቻ በተጨማሪ ሌሎች ማዕቀቦች እና እገዳዎችን ተግባራዊ በማድረግ ኢራንን በምጣኔ ሀብት ለማዳከም አዲስ ዘመቻ ጀምራለች።
እንዲሁም ባለፉት ቀናት አሜሪካ፣ በተለያዩ የኢራን ግዛቶች ውስጥ ጥቃቶችን ስትፈጽም ኢራንም በአጸፋው በዮርዳኖስ፣ በኩዌት እና በተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሠፈሮችን ዒላማ በማድረግ ጥቃት አድርሳለች።