ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
ከአሜሪካ የመመለስ ስጋት የገጠማቸው ኢትዮጵያውያን ቀጣይ ዕጣ ምንድን ነው?
የአሜሪካ ፍርድ ቤት በአገሪቱ ለመኖር እና ለመሥራት የሰጠውን ጊዜያዊ ፍቃድ እንዲያቆም መወሰኑን ተከትሎ ወደ ኢትዮጵያ የመመለስ ጉዳይ ስጋት እንደፈጠረባት በተማሪ ቪዛ ወደ አሜሪካ ያቀናችው እና በኋላም በጊዜያዊ ጥበቃ ሁኔታ (ቲፒኤስ) የቆየችው ሩት (ስሟ የተቀየረ) ትናገራለች።
ሩት፤ በ18 ዓመቷ የመጀመሪያ ዲግሪ ትምህርቷን በአሜሪካ ለመከታተል የሞከረችበት ወቅት የኮቪድ-19 ወረርሽኝ ጊዜ በመሆኑ ሂደቷም የተለየ ነበር።
አንድ ሴሚስተር በኦንላይን ከተማረች በኋላ፣ ኤምባሲው በኮቪድ-19 ምክንያት ሥራ አቁሞ ስለነበር እንደገና ክፍት ሲሆን፣ የቪዛ ሂደቷን አጠናቅቃ ለሁለተኛው ሴሚስተር ወደ አሜሪካ ተጉዛለች።
የዩኒቨርሲቲ ትምህርቷን እየተማረች በነበረችበት ወቅት የጊዜያዊ ጥበቃ ሥርዓት (ቲፒኤስ ወይም TPS) ተጠቃሚ ሆና በአሜሪካ መቆየቷን ትናገራለች። በዚያን ወቅት የመጀመሪያ ዲግሪዋን ጨርሳ የማስተርስ ዲግሪዋን ለመማር እየሞከረች ነበር።
ሆኖም አሜሪካ ውስጥ ማስተርስ ዲግሪ መማር እንደጠበቀችው ቀላል አልነበረም። የመጀመሪያ ዲግሪዋን ነጻ የትምህርት ዕድል አግኝታ መማሯን የምትገልጸው ሩት፣ ለማስተርስ ትምህርት ግን ተመሳሳይ ዕድል ማግኘት ከባድ ሆኖባታል።
በዚህ ሁኔታ ኢትዮጵያ መመለስ ወይም በአሜሪካ ሌሎች ሥራዎችን እየሠራች የሚቀጥለውን የሕይወት ምዕራፍ ማሰስ የሚል አማራጭ እንደነበራት ትናገራለች።
በወቅቱ ወደ ኢትዮጵያ መመለስ ትፈልግ የነበረ ቢሆንም፣ ከጓደኞቿ እና በአካባቢዋ ከሚገኙ ሰዎች የምትሰማው ምክር ግን "ኢትዮጵያ ብትመለሺ እንደምታስቢው ቀላል አይሆንም" የሚል ነበር።
"ኢትዮጵያ ውስጥ ሠርተሽ ራስሽን ችለሽ መኖር ራሱ ትግል ነው" የሚሉ ምክሮች መስማቷ ወደ አገር መመለስ የሚለውን አማራጯን እርግፍ አድርጋ እንድትተው እንዳደረጋት ትናገራለች።
"ለዓመታት ሠርቼ ያጠራቀምኩትን ገንዘብ ሳጠፋው ነው የሚታየኝ" ስትል በተለይም በትምህርት የመቀጠል ሕልሟን ሳታሳካ ወደ ኢትዮጵያ ብትመለስ ነገሮች ከባድ እንደሚሆኑባት ትገልጻለች።
ሩት እንደምትለው፣ ጊዜያዊ ጥበቃ የማግኘት ሂደቱ ቀላል ነበር። ከኢሚግሬሽን ጋር በተያያዙ መሠረታዊ ጥያቄዎች እና ወንጀል ወይም ከሽብርተኝነት ጋር የተያያዘ ተግባር እንዳልፈጸመች የሚያረጋግጡ ጥያቄዎች እንደተጠየቀች ትናገራለች። ከዚያም በ15 ቀን ገደማ ውስጥ ፈቃዱ ደረሳት።
የጊዜያዊ ጥበቃ ሁኔታ በአሜሪካ ውስጥ ከተወሰኑ አገራት ለመጡ ስደተኞች ከሰብአዊ ጉዳዮች ጋር በተያያዘ ጥበቃ ለማድረግ የሚሰጥ ጊዜያዊ የሕግ ከለላ ሲሆን፤ ተጠቃሚዎቹ በአሜሪካ በሕጋዊ መንገድ እንዲሠሩ እና ከአገሪቱ እንዳይባረሩ ያስችላል።
በአውሮፓውያኑ 2022 ይህንን ጥበቃ ለኢትዮጵያውያን የሰጠው የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን አስተዳደር ሲሆን፣ በኢትዮጵያ በወቅቱ በቀጠለው ግጭት እና ሰብአዊ ቀውስ ምክንያት ኢትዮጵያውያን ወደ አገራቸው ቢመለሱ አደጋ ሊያጋጥማቸው ይችላል በሚል የተወሰነ ነበር።
ነገር ግን በ2025 መጨረሻ የዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር በኢትዮጵያ ያለው ሁኔታ መሻሻሉን በመጥቀስ ጥበቃውን ለማቋረጥ መወሰኑን አሳወቀ።
ይህንን እርምጃ በመቃወም ጉዳዩ ወደ ፍርድ ቤት ቀርቦ፣ የቦስተን ዲስትሪክት ፍርድ ቤት ዳኛ ብራያን መርፊ የጥበቃው መቋረጥ እንዳይፈጸም ጊዜያዊ እገዳ ጣሉ።
በኋላም የአሜሪካ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የትራምፕ አስተዳደር ለሄይቲ እና ሶሪያ ዜጎች የተሰጠውን ተመሳሳይ ጥበቃ እንዲያቋርጥ በ6 ለ3 ድምጽ ከፈቀደ በኋላ፣ በኢትዮጵያውያን የጊዜያዊ ጥበቃ ሁኔታ ጉዳይ ላይም የሕግ ክርክሩ ቀጥሏል።
የጊዜያዊ ጥበቃ ሁኔታ እንዲጠበቅ የሕግ ክርክሮችን በማንሳት እና አፍሪካውያን በአገራቸው ባሉት ቀውሶች ምክንያት ከአሜሪካ እንዳይባረሩ ለማድረግ ሲሠራ የቆየው 'አፍሪካን ኮሚኒቲስ ቱጌዘር'፣ የጥበቃው መቋረጥ በአሜሪካ የሚኖሩ 5000 የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያንን ለከፍተኛ አደጋ ይዳርጋል ብሏል።
የድርጅቱ የአደረጃጀት እና የአባላት ተሳትፎ ምክትል ሥራ አስፈጻሚ ዳይሬክተር የሆኑት በርት ባዩ ለቢቢሲ እንደገለጹት ቡድኑ፤ የጊዜያዊ ጥበቃ ሁኔታ እንዲታገድ ሲወሰን በሁለት ምክንያቶች ውሳኔዎቹን ተቃውሟል።
አንደኛው መከራከሪያ፣ ውሳኔው ጥቁሮች ላይ ያነጣጠረ "ዘረኝነትን ነው" የሚል ነው።
ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ የጊዜያዊ ጥበቃ ሁኔታ አካሄድን የሚወስነው የኮንግረስ ሕግ "በአገሪቱ ውስጥ ያለው ሁኔታ ታይቶ ወደ አገራቸው መመለስ የሚችሉ ከሆነ ብቻ ነው የጊዜያዊ ጥበቃ ሁኔታን መሰረዝ ያለባችሁ" ማለቱን በማንሳት እንደሆነ ያስረዳሉ።
ለዚህም በተባበሩት መንግሥታት እና በአሜሪካ መንግሥት የወጡ የደኅንነት ሪፖርቶች እንደማመሳከሪያነት መቅረባቸውን በንት ተናግረዋል።
በአሜሪካ ኖርዝ ካሎላይና እና ሚኒሶታ ግዛት የኢሚግሬሽን ጠበቃ ሆነው ያገለገሉት አቶ እስራኤል ጎበና እንደሚያስረዱት፣ የጊዜያዊ ጥበቃ ሁኔታ በራሱ ለዘለቄታው በአሜሪካ ለመኖር የሚያበቃ አይደለም።
"አንዳንዶቹ በዚህ ሁኔታ ውስጥ ያሉ ሰዎች የቤተሰብ፣ የሥራ፣ የትምህርት ወይም ሌላ የኢሚግሬሽን ጉዳይ ሊኖራቸው ይችላል" ይላሉ። የፖለቲካም ጥገኝነት ያቀረቡም ሊኖሩ እንደሚችሉ ይጠቁማሉ።
ሩት የፖለቲካ ጥገኝነት እንድትጠይቅ የሚያደጋት ምንም ዓይነት ምክንያት ባለመኖሩ እንዳልሞከረች ትናገራለች።
"ምንም ዓይነት ግለሰባዊ ጥቃት ደርሶብኝ አያውቅም። ያልደረሰብኝን ነገር ደግሞ ማውራት ለአገሬም ገጽታ ጥሩ ነው ብዬ አላምንም" ስትል ምክንያቷን ታስረዳለች።
በአሜሪካ ዲግሪዋን ከያዘች በኋላ ወደ ተቀጣሪነት ለመሸጋገር የሚያበቃትን የሥራ ፈቃድ ለማግኘት የሚቀጥራት አካል የኢሚግሬሽን ጉዳዩዋን ስፖንሰር ሊያደርግ እንደሚገባ የምትናገረው ሩት፤ ይሄ ዕድል እንዳልገጠማት ነው የምትገልጽው።
በዚህም ምክንያት የጊዜያዊ ጥበቃ ሁኔታ እስከአሁን በአሜሪካ እንድትቆይ እና ከትምህርቷ ውጪ የሆኑ የሥራ ዕድሎችን እንድትሞክር ያስቻላት ብቸኛ አማራጯ እንደነበር ታስረዳለች።
ማክሰኞ ነሐሴ 12፣ 2018 ዓ. ም. ከምትሠራበት ቦታ ሥራዋን ጨርሳ ስትወጣ ኢትዮጵያውያን ላይ የጊዜያዊ ጥበቃ ሁኔታ እንዳይነሳ ተጥሎ የነበረው እግድ መነሳቱን እንደሰማች ወዲያው ሥራ ለማቆም መወሰኗን ሩት ትገልጻለች።
ወደ ኢትዮጵያ መመለስን ፈጽሞ ባትፈልገውም የሚሆነውን ከማየት ውጪ ምንም አማራጭ እንደሌላትም ትናገራለች።
የሕግ ባለሙያው አቶ እስራኤል በበኩላቸው፤ ጥበቃው ውስጥ ያሉ ሰዎች ከአሜሪካ እንዳይባረሩ እንደ የፖለቲካ ጥገኝነት መጠየቅ እና ሌሎች ዓይነት የኢሚግሬሽን አማራጭ እንዲወስዱ ይመክራሉ። ነገር ግን ይህም ማድረግ ለቆይታቸው ዋስትና እንደማይሆን ያስረዳሉ።
የአፍሪካን ኮሚኒቲስ ቱጌዘር የአደረጃጀትና የአባላት ተሳትፎ ምክትል ሥራ አስፈጻሚ ዳይሬክተር የሆኑት በርት ባዩ፤ በአሜሪካ የተወለዱ ልጆች ያሏቸው ቤተሰቦችም ሌላ ተጽዕኖ ሊገጥማቸው እንደሚችል ጠቁመዋል።
ወላጆች የሕግ ሰነድ የሌላቸው ሲሆን፣ ልጆቻቸው የአሜሪካ ዜጎች ሊሆኑ ስለሚችሉ የቤተሰብ መበተን ሊከሰት እንደሚችል ይገልጻሉ።
ቀጣዩ ሂደት ግን በፍርድ ቤት ካለቀ በኋላ በአሜሪካ ሕግ አውጪው አካል ኮንግረስ ላይ የሚመሠረት መሆኑን በንት ገልጸዋል።
የድርጅቱ ቀጣይ ሥራም በጊዜያዊ ሁኔታ ይኖሩ የነበሩ ሰዎች ወደ ቋሚ ነዋሪነት እንዲሸጋገሩ ሕግ እንዲወጣ መግፋት ነው ብለዋል።
ይህ ቀላል ሂደት እንዳልሆነም ተጠቁሟል። በኮንግረስ ውስጥ ይህን ለውጥ የሚደግፉ የተመረጡ ተወካዮች እንዳሉ፣ እንዲሁም የስደተኞችን አስተዋጾ የሚገነዘቡ አካላት እንዳሉ ጠቁመዋል።
ወደ ኢትዮጵያ የመመለስ ሂደቱ ወዲያውኑ የሚፈጸም አይሆንም ሲሉ ግምታቸውን ያስቀመጡት በንት፤ መንግሥት ትዕዛዝ ማውጣት እና ይህንን ትዕዛዝ ለጥበቃው ተጠቃሚዎች ማድረስ እንዳለበት አስረድተዋል። እስካሁን ግን እንደዚህ ያለ ትዕዛዝ ወይም እርምጃ እንደሌለ ገልጸዋል።
በአሜሪካ በአጠቃላይ ወደ 1.3 ሚሊዮን ገደማ ሰዎች ጊዜያዊ ጥበቃ ሁኔታ እንዳላቸው ያነሱት ዳይሬክተሩ፤ ይህን ሁሉ ሰው በአንድ ጊዜ በሕጉ መሠረት ይዞ ማስወጣት ከባድ በመሆኑ "ጊዜ ሊወስድ እንደሚችል" ጠቁመዋል።