ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
በታሪክ ታይቶ የማይታወቅ የኤል ኒኖ ክስተት ሊያጋጥም እንደሚችል ተመራማሪዎች አስጠነቀቁ
ከፓስፊክ ውቅያኖስ ላይ የሚነሳው የኤል ኒኖ ክስተት በመቶ ዓመታት ታሪክ ውስጥ ከፍተኛው ሊሆን እንደሚችል የአየር ንብረት ተመራማሪዎች አስጠነቀቁ።
በየሰባት ዓመቱ የሚያጋጥም የአየር ንብረት ክስተት የሆነው ኤል ኒኖ የዓለምን የሙቀት መጠን የሚጨምር ሲሆን ለአስከፊ የአየር ሁኔታ የመጋለጥ ዕድልን ይጨምራል።
ኤል ኒኖ የሚከሰተው በምሥራቅ እና መካከለኛው ፓስፊክ ውቅያኖስ በሚፈጠር የባሕር ወለል ሙቀት እና የንፋስ ሁኔታ ለውጥ ሲሆን፣ አሁን በውቅያኖሱ ላይ እየታየ ያለው የኤል ኒኖ ክስተት ከፍተኛ እንደሚሆን ተተንብዩዋል።
በዚህም ምክንያት ቀጣዩ የአውሮፓውያኑ ዓመት "በታሪክ እጅግ ሞቃታማው" የመሆን ዕድሉ ከፍተኛ ሊሆን እንደሚችል የሚቲዮሮሎጂ ባለሙያዎች አስጠንቅቀዋል።
ይህ የአየር ንብረት ለውጥ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተፅዕኖ እያሳደረ መሆኑን የተለያዩ መረጃዎች አመልክተዋል። በሕንድ የዝናብ መጠን ከአማካዩ የቀነሰ ሲሆን በአትላንቲክ ውቅያኖስ አካባቢ ያለውን የነፋስ እንቅስቃሴንም አግዶታል።
በኢትዮጵያ፣ በአብዛኛው ኤርትራ፣ በደቡብ ሱዳን፣ በኡጋንዳ፣ በጂቡቲ፣ በሱዳን እንዲሁም በምዕራባዊ እና ባሕር ዳርቻ የኬንያ ክፍሎች ከመደበኛው ያነሰ የዝናብ መጠን እንደሚጠበቅም ቀደም ሲል ዓለም አቀፉ የሜትሮሎጂ ተቋም ባወጣው ትንበያ ገልጾ ነበር።
በኢትዮጵያ አንዳንድ አካባቢዎችም ከመደበኛው ያነሰ የክረምት ዝናብ እያስተናገዱ ነው።
ኤል ኒኖ በዩናይትድ ኪንግደም በመኸር ወቅት ከፍተኛ ዝናብ ሊያስከትል እንደሚችል ተተንብዩዋል። የዩኬ የሚቲዮሮሎጂ ቢሮ ኃላፊ ፕሮፌሰር አዳም ስኬፍ " በትንበያዎቻችን እንዲህ ዓይነት የኤል ኒኖ ምልክት ዓይቼ አላውቅም" ብለዋል።
ኤልኒኖ ተፈጥሯዊ የአየር ንብረት ለውጥ ሲሆን ከሁለት እስከ ሰባት ዓመት ጊዜ ውስጥ እየተደጋገመ ይከሰታል። ለአንድ ዓመት ያህልም ይቆያል።
በፓስፊክ ውቅያኖስ ከምሥራቅ ወደ ምዕራብ የሚነፍሰው እርጥበት አዘል ነፋስ የተዳከመ ሲሆን የሚመለስበትም ሁኔታዎች ታይተዋል። ይህም ሞቃታማ አየር በምሥራቅ በኩል እንዲዛመት አድርጓል።
ከውቅያኖሶች ወጥቶ ወደ ከባቢ አየር የሚለቀቀው ሙቀት የዓለም የሙቀት መጠንን የሚጨምር ሲሆን የዝናብ ወቅትን ያዛባል።
ተመራማሪዎች ኤል ኒኖ እንደተከሰተ የሚያውጁት ከባሕር ጠለል በላይ የሙቀት መጠን በአማካይ ከ0.5 ዲግሪ ሴልሽየስ ወይም ከዚያ በላይ ሲሆን ነው። ይህም የነፋስን አቅጣጫ የማስቀየር፣ እርጥበት አዘል የአየር ሁኔታን የመለወጥ አቅም አለው።
አሁን ላይ ያለው ግን ከ2 ዲግሪ ሴልሽየስ በላይ ተለክቷል።
የዩኬ ሚቲዮሮሎጂ ቢሮ እንዳለው በዚህ ዓመት መጨረሻ ላይ የሙቀት መጠኑ 3 ዲግሪ ሴልሽየስ ሊደርስ ይችላል። ይህም ከአውሮፓውያኑ 1950 ወዲህ ታይቶ የማይታወቅ ምን አልባትም ከ19ኛው ክፍለ ዘመን ወዲህ በጣም ከፍተኛው ክስተት ይሆናል።
ሌሎች የአየር ንብረት ተመራማሪ ቡድኖችም የዩኬው ሚቲዮሮሎጂ ቢሮ ከመዘገበው የበለጠ 4 ዲግሪ ሴልሺየስ እንደሚሆን ተንብየዋል።
ይህ ከሆነ ምንም እንኳን አስቀድሞ ይህን መናገር ባይቻልም " በ500 ወይም 1000 ዓመታት ውስጥ እጅግ አስከፊው የኤል ኒኖ ክስተት ሊሆን ይችላል" ሲሉ አስጠንቅቀዋል።