ከአሜሪካ ጋር የተደረገው ድርድር መክሸፉን ተከትሎ፣ ካናዳ የዋሽንግተን ምርቶች ላይ እኩል ታሪፍ እንደምትጥል አስታወቀች

ታትሟል
የንባብ ጊዜ: 2 ደቂቃ

አሜሪካ እና ካናዳ በመጨረሻ ሰዓት ሲያደርጉት የነበረው ድርድር ያለ ውጤት መበተኑን ተከትሎ የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር የካናዳ ምርቶች ላይ የጣለው አዲሱ ዙር ታሪፍ ተግባራዊ መሆን ጀመረ።

ለአርብ ምሽት ተቀምጦ የነበረው ቀነ ገደብ ከመጠናቀቁ ጥቂት አስቀድሞ ድርድሩ መቋረጡን ያስታወቁት የካናዳ ጠቅላይ ሚኒስትር ማርክ ካርኒ፣ በእያንዳንዱ አሜሪካ ታሪፍ ልክ ከአገሪቱ የሚመጡ ምርቶች ላይ ቀረጥ እንደሚጥሉ ገልጸዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ "በአሜሪካ የቀረቡት ነጥቦች ላይ በመጨረሻ ደቂቃ የተደረጉት ለውጦች ኢፍትሐዊ፣ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም የሌላቸው እና የትኛውንም ስምምነት እውነተኝነት ጥያቄ ውስጥ የሚከትቱ ናቸው" ሲሉ ተችተዋል።

ፕሬዝዳንት ትራምፕ ወደ አሜሪካ በሚገቡ 20 ቢሊዮን ዶላር ዋጋ ያላቸው የካናዳ ምርቶች ላይ ከነሐሴ አጋማሽ አንስቶ 50% ታሪፍ እንደሚጥሉ ዝተው ነበር። ይህንን ተከትሎ ከሐምሌ ጀምሮ ሁለቱ አገራት ሲደራደሩ ቆይተዋል።

ትራምፕ በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ ሁለቱ አገራት "እጅግ ጥሩ" የንግድ ስምምነት ለመፈረም መቃረባቸውን በመግለጽ የታሪፍ እርምጃውን በጊዜያዊነት አግደውት ነበር።

የተሰጠው ቀነ ገደብ ሊጠናቀቅ ጥቂት ደቂቃዎች ሲቀሩ ግን ንግግር ያደረጉት የካናዳው ጠቅላይ ሚኒስትር ካርኒ፣ በድርድሩ "ወሳኝ መሻሻሎች" ታይተው የነበረ ቢሆንም የተገኘው ውጤት "ለካናዳውያን የወጠንነውን ግብ ለማሳካት በቂ አልነበሩም" በማለት ንግግሩ መክሸፉን አስታውቀዋል።

"በዚህ ምክንያት ዛሬ ምሽት ከአሜሪካ ጋር የሚደረገውን የንግድ ድርድር ለማቋረጥ ወስኛለሁ፣ ተደራዳሪዎችም ወደ ኦታዋ እንዲመለሱ አዝዣለሁ" ብለዋል።

ካርኒ ይህንን ካሉ በኋላ መግለጫ ያወጡት የአሜሪካ የንግድ ተወካይ ጄሚሰን ግሪር በበኩላቸው፣ "ዛሬ ምሽት፣ ካናዳ የንግድ ስምምነቱ በዚህ ሳምንቱ በተስማማንባቸው ነጥቦች መሠረት እንዲጠናቀቅ ፈቃደኛ ሳትሆን ቀርታለች" ሲሉ ወቅሰዋል።

"አሜሪካ፣ ምርቶችን ወደ ገበያችን ከሚልኩ የትኛውም ዋነኛ ኤክስፖርተሮች በተሻለ ሁኔታ ካናዳን ለማስተናገድ ዕድል ብታቀርብም፣ በካናዳ በኩል የቀረቡ አዳዲስ ጥያቄዎች እና ሌሎች ቃል ኪዳኖችን ወደ ኋላ የመመለስ ሁኔታዎች ምክንያት ባለፉት ቀናት የተደረሰው ጥንቃቄ የተሞላበት ሚዛናዊ [ስምምነት] ቀልብሰውታል" ሲሉም በኤክስ ገጻቸው ባወጡት መግለጫ አስፍረዋል።

የድርድሩ መክሸፍ፣ በዚህ ሳምንት መጀመሪያ የአሜሪካ እና የካናዳ ባለሥልጣናት ሁለቱንም አገራት የሚጠቅም ስምምነት ላይ ሊደረስ እንደሚችል ሲሰጡት የነበረውን ተስፋ የቀለበሰ ሆኗል።

የሁለቱ አገራት ተደራዳሪዎች በካናዳ ብረት እና አልሙኒየም ላይ የተጣለው የአሜሪካ ታሪፍ ከ50% ወደ 25% እንዲሁም በካናዳ አውቶሞቢሎች ላይ የተጣለው ቀረጥ ደግሞ ከ25% ወደ 15% እንዲቀነስ የሚያደርግ ስምምነት ላይ ለመድረስ ሲነገጋሩ እንደነበር ተሰምቷል።

በምላሹም የካናዳ ግዛቶች እንደገና የአሜሪካ የአልኮል መጠጦችን መሸጥ እንዲጀምሩ የማድረግ ሀሳብ ተነስቶ ነበር።

ፕሬዝዳንት ትራምፕ ባለፈው ዓመት ጥር ላይ ወደ ሥልጣን ከተመለሱ ወዲህ በሁለቱ ግዙፍ የንግድ አጋሮች መካከል ውጥረት ተፈጥሯል። ትራምፕ ሰፊ ዓለም አቀፍ ታሪፍ መጣላቸውም ለብዙ አሥርተ ዓመታት በካናዳ እና በአሜሪካ መካከል የነበረውን ነጻ የንግድ ገበያ አፍርሷል።

አሁን ድርድሩ በመክሸፉ የካናዳ ምርቶች የ50% ታሪፍ ይጠብቃቸዋል። ታሪፉ እንደ ወይን፣ የወተት ተዋጽኦዎች፣ ሲሚንቶ እና አልባሳት ባሉ በበርካታ ምርቶች ላይ ይተገበራል።

የአሁኑ ታሪፍ፣ አሜሪካ ከዚህ ቀደም በካናዳ ብረት፣ አልሙኒየም፣ አውቶሞቢሎች እና እንጨቶች ላይ ከጣለችው ቀረጥ በተጨማሪነት የተጣለ ነው።