ትራምፕ የአሜሪካ አጋር የሆነችው ኦማን ከኢራን ጋር ባለው ንግግር ጣልቃ የምትገባ ከሆነ ጥቃት እንደሚፈፅሙባት መዛታቸውን ፎክስ
ኒውስ ዘገበ።
አሜሪካ እና ኦማን የሆርሙዝ ወሽመጥን ለማስከፈት ከቴህራን ጋር በተናጠል እየተደራደሩ ነው።
አሜሪካ ኢራን ላይ ጦርነት ከከፈተች ጊዜ ጀምሮ የዓለም አንድ አምስተኛ የነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ መጓጓዣ የሆነው ወሽመጥ
ተዘግቷል።
ፎክስ ኒውስ እንደዘገበው ትራምፕ ኦማንን ያስጠነቀቁት በስልክ በሰጡት ቃለ ምልልስ ወቅት ነው።
የኢራን ባለሥልጣናት ከኦማን ጋር የሚያደርጉትን ድርድር እያጠናቀቁ እንደሆነ ተናግረው ነበር።
ይህ በእንዲህ እንዳለ በአሜሪካ እና ኢራን መካከል ለስልሳ ቀናት የተፈረመው የተኩስ አቁም መግባቢያ ሰነድ ጊዜው በመጠናቀቅ
ላይ ይገኛል።
ሰኞ እለት ትራምፕ በኦቫል ኦፊስ በሰጡት መገለጫ ቢቢሲ የመግባቢያ ሰነዱ እንዲራዘም ይፈልጉ እንደሆን ጠይቆ “አልፈልግም”
ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።
በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የሚደረገው ንግግር በዋናነት የሚያተኩረው የሆርሙዝ ወሽመጥን ማስከፈት ላይ ነው።
ኦማን በወሽመጡ ደቡባዊ ክፍል የምትዋሰን ሲሆን በግጭቱ ውስጥ ገለልተኛ ወገን መሆኗን ስትገልጽ ቆይታለች።
ይሁን እንጂ ኢራን ተደጋጋሚ ጥቃት የፈጸመችባት ሲሆን አሁን ወሽመጡ እንዲከፈት በሚደረገው ድርድር ውስጥ ቁልፍ ሚና
እየተጫወተች ትገኛለች።
ዋሺንግተን ይህ የመርከቦች መተላለፊያ እንዲከፈት የራሷን ጥረት እያደረገች ትገኛለች።
ፎክስ ኒውስ ትራምፕ “ኦማን ጣልቃ የምትገባ ከሆነ ከባድ ድብደባ ይደርስባታል” ማለታቸውን ዘግቧል።
ትራምፕ ጣልቃ መግባት ሲሉ ምን ምን እንደሚያካትት ግልጽ አይደለም።
በዚሁ ቃለ ምልልሳቸው ላይ አሜሪካ በኢራን ጦር፣ ምጣኔ ሃብት እና ፖለቲካ ውስጥ ወሳኝ ከሆነው ኃይል ከሆነው ከእስላማዊ
አብዮታዊ ዘብ ጋር በእጅ አዙር ግንኙነት እንዳላቸው ተናግረዋል።
የእስላማዊ አብዮታዊ ዘቡ ቃል አቀባይ የትራምፕን ንግግር አስተባብሏል።
ቃል አቀባዩ ለኢራን የዜና ወኪል ታስኒም ኒውስ "በአብዮታዊ ዘቡ ባለሥልጣናት እና በአሜሪካውያን መካከል ምንም
ዓይነት ውይይት አልተደረገም፤ እናም ይህ የትራምፕ ውሸት በጦርነቱ ሽንፈት እና ተስፋ መቁረጥ ሰበብ የመጣ ግራ መጋባት እና ቅዠት
ምክንያት የተፈጠረ ተስፋ መቁረጥ ብቻ ነው" ብለዋል።
ትራምፕ ኦማን ላይ ዛቻውን
የሰነዘሩት ኢራን ሁለቱ አገራት በወሽመጡ መርከቦች
ማለፍ እንዲችሉ ስምምነት ላይ መድረሳቸውን ከተናገረች ከጥቂት ሰዓታት
በኋላ ነው።
የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል
ባጋይ ለጋዜጠኞች "የመጓጓዣ መስመሩን ካርታ በተመለከተ መግባባት ላይ ተደርሷል" ብለዋል።
ሁለቱም ወገኖች የጋራ መግለጫ ከማውጣታቸው በፊት ዝርዝር ጉዳዮችን እንደሚያጠናቅቁ ተናግረዋል። ኦማን ቀደም ሲል ውይይቱ በአዎንታዊ መልኩ እየሄደ መሆኑን ገልጻ ነበር።
በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ የኢራን የውጭ ጉዳይ
ሚኒስትር አባስ አራግቺ፣ ወሽመጡ ዳግም ሙሉ በሙሉ እንዲከፈት አሜሪካ የመግባቢያ ሰነዱን በመጣሷ
ካሳ መክፈሏ ላይ ይወሰናል ብለው ነበር።
ሮይተርስ አንድ የኢራን ባለሥልጣንን ጠቅሶ ቴህራን በባሕረ ሰላጤው ውስጥ ከሚጓዙ የጭነት መርከቦች ከ5 በመቶ እስከ 7 በመቶ የሚደርስ ክፍያ እንደምትጠብቅ ዘግቧል።