የኢንስታግራም እና ፌስቡክን ገጽታ እስከወዲያኛው ሊለውጥ የሚችለው የፍርድ ቤት ክስ

ማርክ ዙከርበርግ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

ታትሟል
የንባብ ጊዜ: 3 ደቂቃ

ሜታ ታዳጊዎችን ለአደጋ ከማጋለጥ ጋር የተያያዙ ተከታታይ ክሶች ቀርበውበታል።

የኩባንያው የማኅበራዊ ሚዲያ ገጾች የታዳጊዎችን ደኅንነት አልጠበቁም በሚል ከቀረቡት ክሶች አንዱ ነገ ማክሰኞ በፍርድ ቤት ይታያል።

ከሕዝብ በተውጣጡ ፍርድ ሰጪዎች (ጁሪ) የሚታየው ክስ ሜታ ከገጠሙት ፈተናዎች ትልቁ እንደሚሆን ተገልጿል።

ክሱ የተመሠረተው በአውሮፓውያኑ 2023 ሲሆን፤ ከሳሾቹ ካሊፎርኒያ እና ኒው ዮርክን ጨምሮ 30 የአሜሪካ ግዛቶች ናቸው።

ሜታ ፌደራል እና የተለያዩ ግዛቶች ያወጧቸውን የታዳጊዎች የግል መረጃ ጥበቃ ሕግጋት ጥሷል በሚል ተከስሷል። የአሜሪካ ግዛቶች ሜታ እስከ አንድ ትሪሊዮን ዶላር እንዲቀጣ ጠይቀዋል።

በተጨማሪም ኢንስታግራም እና ፌስቡክን እስከወዲያኛው የሚቀይር የአሠራር ለውጥ እንዲተገበር ሲሉ በፍርድ ቤት ከስሰዋል።

መለወጥ አለባቸው ከተባሉ መካከል 'ላይክ' ማስቀረት እና ማለቂያ የሌለው መረጃ አሰሳ (ኢንፋይናይት ስክሮል) ይገኙበታል።

ሜታ ከተሸነፈ ታዳጊዎች ማኅበራዊ ሚዲያ የሚጠቀሙበትን መንገድ የሚቀይሩ ጉልህ ለውጦችን ለመተግበር ይገደዳል።

የአሜሪካ ግዛቶች ኢንስታግራም እና ፌስቡክ የሚሠሩበትን መንገድ ከመቀየር በተጨማሪ ሌሎችም ማሻሻያዎች እንዲደረጉ ጠይቀዋል። የተወሰኑት ለውጦች የሚከተሉት ናቸው፦

  • ታዳጊ ተጠቃሚዎች በቤተሰቦቻቸው ቁጥጥር እንዲደረግባቸው የሚያስችል አሠራር መዘርጋት
  • አንድን መረጃ አስከትሎ ሌላ ዶፓሚን ሆርሞንን የሚያነቃቃ መረጃ አለመስጠት
  • የሰዎችን ገጽታ መለወጥ የሚችለውን አርትኦት (ፊልተር) ማቆም
  • ቪድዮ በቀጥታ እንዲጫወት የሚያደርገውን (አውቶፕለይ) ማቆም
  • ከአንድ በላይ አካውንት እንዳይከፈት ማገድ
  • እንደ ኢንስታግራም 'ስቶሪስ' የሚጠፉ ልጥፎችን ማቆም

እነዚህ ገጽታዎች ሜታ አሁን ላለው ቅርጽ መሠረታዊ ናቸው።

ገጽታዎቹ ልጆች እና ታዳጊዎች ማኅበራዊ ሚዲያው ላይ ለረዥም ጊዜ እንዲቆዩ እና ደጋግመው እንዲጠቀሙት እንደሚያደርጉ ከሳሾቹ ገልጸዋል።

ታዳጊዎች ማኅበራዊ ሚዲያውን የሚጠቀሙበትን መጠን ለመቀነስ ቢፈልጉም ሜታ ይህንን እርምጃ መውሰድን ከባድ እንደሚያደርገው ክሱ ያመለክታል።

በተደጋጋሚ የጥቆማ መልዕክት (ኖቲፊኬሽን) በመላክ ታዳጊዎች ወደ መተግበሪያው እንዲመለሱ ያደርጋል ተብሏል።

ስልክ የያዘች ታዳጊ

የፎቶው ባለመብት, Reuters

Skip podcast promotion and continue reading
የቢቢሲ አማርኛ ዩቲዩብ ቻናል

ዜና፣ ትንታኔ እና ታሪኮችን በምሥል እና በድምጽ ለማግኘት

ይህንን በመጫን ሰብስክራይብ ያድርጉ

End of podcast promotion

ሜታ ታዳጊዎችን ዒላማ በማድረግ፣ ሱስ በማስያዝ "መበዝበዙን" ከሳሾቹ የአሜሪካ ግዛቶች አስታውቀዋል።

መተግበሪያውን ለማስፋፋት እና ገቢውን ለማሳደግ ታዳጊዎችን ሱስ የሚያስይዝ አሠራር መዘርጋቱም ተመልክቷል።

በዛሬ ሰኞ የአክስዮን ገበያ የ1.5 ትሪሊዮን ዶላር ዋጋ ያለው ሜታ፣ የቀረቡበትን ክሶች አስተባብሏል።

የሜታ ቃል አቀባይ "እነዚህን ክሶች አንቀበልም። ታዳጊዎችን ለመደገፍ ያለንን የረዥም ጊዜ ቁርጠኛነት በማስረጃ እንደምናሳይ እርግጠኛ ነን" ብለዋል።

ጉዳዩን የሚከታተሉት የካሊፎርያዋ ዳኛ የቮን ጎንዛሌዝ ሮጀርስ ናቸው።

ከዚህ ቀደም በኢሎን መስክ እና ሳም አልትማን መካከል የነበረውን ክስ ዳኝተዋል። ለ20 ዓመታት የሠሩት ዳኛዋ "ቀጥተኛ እና አስተዋይ" መሆናቸው ይነገርላቸዋል።

በቅርቡ በኒው ሜክሲኮ በነበረ የፍርድ ሒደት ሜታ 942 ሚሊዮን ዶላር እንዲቀጣ ተወስኗል።

የአሜሪካ ግዛቶች ሜታ ማድረግ አለበት ካሏቸው ማሻሻያዎች የተወሰኑት እንዲተገበሩም ታዝዟል።

ዳኛ ብራየን ቢድሽይድ ባሳለፉት ውሳኔ መሠረት ከ18 ዓመት በታች ለሆኑ ተጠቃሚዎች የኢንስታግራም እና ፌስቡክ 'ላይክ' ማድረግ ማቆም ይኖርባቸዋል።

ታዳጊዎች እርቃን ምሥል መላክም ሆነ መቀበል እንዳይችሉ ተከልክሏል። በተጨማሪም መተግበሪያው ከተወሰነ ሰዓት ውጭ 'ኖቲፊኬሽን' እንዳይልክ ተወስኗል።

ዳኛው ሜታ አየር ከሚበክል "የማኅበረሰብ ጠንቅ" ጋር የሚመሳሰል ነው ብለዋል። ውሳኔውን የተቃወመው ሜታ ይግባኝ ብሏል።

ሜታ ለውጦችን እንዲተገብር የተላለፈው ውሳኔ ተፈጻሚ የሚሆነው በኒው ሜክሲኮ ሲሆን፤ የተቀሩት 30 ግዛቶች የከፈቱት ክስ ከዚህ የተለየ ነው።

እነዚህ ግዛቶች ከአሜሪካ ሕዝብ ሁለት ሦስተኛውን ይሸፍናሉ።

ሜታ ለውጦቹን ከተገበረ መተግበሪያው አሁን ካለው የተለየ ይሆናል። ለምሳሌ 'ላይክ' መቁጠር ፌስቡክ ከተመሠረተ ጊዜ አንስቶ የነበረ ነው።

የሰዎችን ምሥል፣ ጽሑፍ ወይም ሌሎችም ልጥፎች 'ላይክ' ማድረግ የመተግበሪያው መሠረታዊ ሥሪት ነው።

ሆኖም ግን 'ላይክ' በተለይም በታዳጊዎች ዘንድ አሉታዊ የሥነ ልቦና ጫና እያሳደረ መምጣቱ ይነገራል።

በያዝነው ዓመት ሜታን የከሰሰችው ኬይሊ በፍርድ ቤት እንደተናገረችው፣ በርካታ የዩቲዩብ እና ኢንስታግራም ገጾች በመክፈት 'ላይክ' በመቁጠር ተጠምዳ ነበር።

ስለ ራሷ ያላት አመለካከት እና ለራሷ የምትሰጠው ዋጋ "ከላይክ ጋር ተሳስሮ" እንደነበር ተናግራለች። ኬይሊ በዚህ ምክንያት በ10 ዓመቷ በድባቴ ተይዛለች።

'ላይክ' መቁጠር ታዳጊዎችን ወደ ድባቴ እንደሚያስገባ እና ችላ የመባል ስሜት እንደሚፈጥር ጥናቶች ያሳያሉ።

ሜታ ላይ የቀረበው ክስ እንደሚያመለክተው 'ላይክ' ወደ "ማኅበራዊ ንጽጽር" የሚያስገባ እና የሰዎችን ዋጋ የሚነሳ ነው።

ይህም የተባባሰ ብቸኛነት፣ ለሰውነት የተዛባ አመለካከት መያዝ እና አሉታዊ ስሜት ያስከትላል ተብሏል።

ሜታ ይሄንን የጥናት ውጤት እንደሚያውቅ እና በተቋሙ የተሠራ ምርምርም ተመሳሳይ ይዘት እንዳለው በክሱ ተጠቅሷል።