ቀጥታ, በኢራን ጦርነት የተነሳ 400 መርከቦች በባሕረ ሰላጤው መቆማቸውን የመንግሥታቱ ድርጅት አስታወቀ

አርብ ዕለት ዓለም አቀፉ የባሕር ላይ ድርጀት (አይኤምኦ) የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ 400 ነዳጅ ጫኝ መርከቦች እና 6,000 ባሕረተኞች በባሕረ ሰላጤው ለስድስት ወራት መንቀሳቀስ ባለመቻላቸው መቆማቸውን አስታወቀ። የአይኤምኦ ኃላፊ አርሴኒዮ ዶሚንጌዝ “የተወሰኑ መርከቦች እና ሠራተኞቻው ባሕረ ሰላጤውን ማቋረጥ ቢችሉም፣ ግጭቱ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ 400 የሚሆኑ መርከቦች ከ6,000 ሠራተኞቻቸው ጋር አካባቢውን ያለምንም የደህንነት ስጋት ለቅቀው መውጣት አልቻሉም” ብለዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. በኪየቭ በደረሰ ጥቃት ቢያንስ 37 ሰዎች ሲገደሉ በመቶዎች የሚቆጠሩ ደግሞ ተፈናቀሉ

    ከዩክሬን ዋና ከተማ በስተምዕራብ በሚገኘው መጋዘን ውስጥ ተተኳሾች ተቀምጠው እንደነበር ለማጣራት ምርመራ ተጀምሯል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ከዩክሬን ዋና ከተማ በስተምዕራብ በሚገኘው መጋዘን ውስጥ ተተኳሾች ተቀምጠው እንደነበር ለማጣራት ምርመራ ተጀምሯል

    አርብ ዕለት በኪየቭ በሚገኝ መጋዘን ላይ ሩሲያ የድሮን ጥቃት ከፈጸመች በኋላ ፍንዳታ በመከሰቱ 37 ሰዎች ሲገደሉ ወደ 400 የሚጠጉ ደግሞ ከቤት ንብረታቸው ለቅቀው እንዲወጡ ተደረገ።

    ፕሬዝዳንት ቮሎዲሚር ዜሌንስኪ ፍንዳታው በአካባቢው በሚገኙ የመኖሪያ ሕንፃዎች እና በአረጋውያን የእንክብካቤ ማዕከል ላይ ጉዳት አድርሷል ብለዋል።

    በመጋዘኑ ውስጥ ተተኳሾች ተከማችተው እንደነበረ ለማወቅ ምርመራ ተጀምሯል።

    የአካባቢው አስተዳዳሪ ቲሙር ትካቼንኮ፣ ከቆሰሉት 42 ሰዎች መካከል አራት ሕጻናት እንደሚገኙበት ተናግረዋል።

    ቅዳሜ ማለዳ ላይ በቡቻ አውራጃ በሚገኘው ሥፍራ የተጎዱ ሰዎችን የመፈለግ እና የማዳን ሥራዎች እየተከናወኑ ነው።

    ዜሌንስኪ በኤክስ ገጻቸው ላይ "መመሪያዎቹ ግልጽ ናቸው። ተተኳሾችን በቤቶች ውስጥ ወይም የመኖሪያ ሕንፃዎች አቅራቢያ መቀመጥ የለባቸውም። [ከምርመራ በኋላ] ተገቢ ድምዳሜ ላይ እንደርሳለን" ሲሉ ጽፈዋል።

    ከ300 በላይ የድንገተኛ አደጋ ሠራተኞች ጥቃቱ ወደ ተፈጸመበት ማይላ መንደር መሰማራታቸውን ተናግረው በዚያም "የአረጋውያንና የአካል ጉዳተኞች የእንክብካቤ ማዕከል" ከተጎዱት ሕንጻዎች መካከል አንዱ ነው ብለዋል።

    “በግልጽ ቸልተኝነት በማሳየት የወንጀል ክስ ተከፍቷል” ሲሉ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ልጥፍ ላይ አጋርተዋል።

    የዩክሬን ዋና አቃቤ ሕግ ቢሮ በመኖሪያ ሕንፃዎች አቅራቢያ "ፈንጂዎችን እና ተቀጣጣይ ቁሳቁሶችን የማስቀመጥ እና የማከማቸት ሕጋዊነት" እየመረመረ መሆኑን አስታውቋል።

    “ይህንን ውሳኔ የወሰኑ ባለሥልጣናት ድርጊት” እንደሚጣራም ጨምሮ ገልጿል።

    የሩሲያ የመከላከያ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ ጦሩ በማይላ "ለኤፍፒ-1/ኤፍፒ-2 ረዥም ርቀት የሚጓዙ ሰው አልባ አውሮፕላኖች የሚያገለግሉ መለዋወጫዎች እና ማስተኮሻዎች" የተቀመጡበት "የተተኳሾች ማከማቻ መጋዘን" ዒላማ ማድረጉን ገልጿል።

  2. የኢራኑ ፕሬዚዳንት ትራምፕ ቀውስ መፍጠራቸውን እንዲያቆሙ በመጠየቅ ችግሮች በንግግር ይፈታሉ አሉ

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን

    የፎቶው ባለመብት, Anadolu

    የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን ቅዳሜ ዕለት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ተጨማሪ ቀውስ ከመፍጠር እንዲቆጠቡ አሳስበው፣ ችግሮች በውይይት እና የመግባቢያ ስምምነቱን ተግባራዊ በማድረግ ሊፈቱ እንደሚችሉ ተናገሩ።

    ፔዜሽኪያን በቴህራን በተካሄደ ሥነ ሥርዓት ላይ "በውይይቱ እና በመግባቢያ ሰነዱ መሠረት ከቀጠልን ችግሮቹን እንፈታለን እና መብቶቻችንን እናስጠብቃለን" ሲሉ መናገራቸውን ሜህር የዜና ኤጀንሲ ዘግቧል።

    "ትራምፕ ተጨማሪ ቀውስን ባይፈጥሩ እና እስራኤል አለመረጋጋትን ባትፈጥር እና ጠብ ባትጭር ለአገሪቱ፣ ለቀጣናው እና ለዓለም ጥቅም ነው" ሲሉ አክለዋል።

    ፔዜሽኪያን ኢራን ጦርነትን እንደማትደግፍ፤ ነገር ግን ለማንኛውም ጥቃት ብርቱ ምላሽ እንደምትሰጥ ተናግረዋል።

    “ጦርነትን አንወድም፤ ነገር ግን ለየትኛውም ጠብ አጫሪነት በጽናት ቆመን ራሳችንን እንከላከላለን” ሲሉ በንግግራቸው ላይ ጠቅሰዋል።

    በተጨማሪም "ግዛቱን ለመከላከል ቆርጦ የተባበረ አንድ አገር እጅ እንዲሰጥ የሚያስገድድ ኃይል" እንደሌለም ተናግረዋል።

    ቴህራን ችግሮችን በውይይት ለመፍታት እንደምትፈልግ ቢናገሩም፣ የኢራን ሕዝብ፣ ባለሥልጣናት እና የጦር አዛዦች ለዛቻ እና ጠበኝነት "በፍፁም እጅ እንደማይሰጡ" አፅንዖት ሰጥተዋል።

    ፕሬዝዳንቱ እስራኤል በሙስሊም አገሮች መካከል ክፍፍል ለመፍጠር ትፈልጋለች ሲሉም ከስሰዋል።

    አክለውም በሙስሊም አገሮች መካከል ያለው አንድነት እንዲህ ዓይነቱን ጥረት ሊያደናቅፍ እንደሚችልም ተናግረዋል።

    ፔዜሽኪያን ሕዝቡ እንዲረጋጋ እና ከመንግሥት ጋር እንዲተባበር ጥሪ አቅርበው፣ የኢራን ጠላቶች በጫና አገሪቱን እንደምትንበረከክ ማመን የለባቸውም ብለዋል።

    እስራኤል እና አሜሪካ የካቲት 21/2018 ዓ.ም. ኢራን ላይ ጦርነት የጀመሩት የአገሪቱን ከፍተኛ ባለሥልጣናትን እንዲሁም ቁልፍ የአመራር እና ወታደራዊ ማዕከላትን ዒላማ በማድረግ ነበር።

    ነገር ግን በጦርነት እና በድርድር ውስጥ ሳትበገር የቆየችው ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን በመዝጋት በአሜሪካ እና በአካባቢው አገራት እንዲሁም በዓለም ምጣኔ ሀብት ላይ ከባድ ተጽዕኖን ማሳደር ችላለች።

    በሰኔ ወር በኢራን እና አሜሪካ መካከል የሚካሄደውን ጦርነት በተኩስ አቁም ጋብ ለማድረግ ያስችላል የተባለ የመግባቢያ ስምምነት በፓኪስታን እና ኳታር አደራዳሪነት እንዲፈራረሙ ማድረግ ተችሎ ነበር።

    ​​​​​​​ነገር ግን በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ዘላቂ መፍትሄ ላይ ባለመደረሱ ዳግም ውጥረት አገርሽቷል።

  3. የቀድሞው የዋይት ሐውስ ባልደረባ የትራምፕ ንግግር ላይ በመወራረዱ 172 ሺህ ዶላር እንዲከፍል ተፈረደበት

    ዋይት ሐውስ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የቀድሞው የዋይት ሐውስ የጽሑፍ ማንበቢያ ማሽን ተቆጣጣሪ የትራምፕ ንግግር ላይ በመወራረዱ ከ172,000 ዶላር በላይ እንዲከፍል ተፈረደበት።

    ጋብሬኤል ፔሬዝ እአአ ከኅዳር 2025 እስከ የካቲት 2026 ድረስ ፕሬዚዳንት ትራምፕ በንግግራቸው ወቅት ምን ሊሉ እንደሚችሉ በአቋማሪ ድርጅቶች በኩል ተወራርዶ በርካታ ገንዘቦችን አሸንፏል።

    አቋማሪ ድርጅቶችን የሚቆጣጠረው መሥሪያ ቤት፣ ፔሬዝ ያገኘውን 107,539.02 ዶላር ትርፍ እንዲሁም ተጨማሪ ቅጣት 65,000 ዶላር እንዲከፍል ወስኖበታል።

    የጽሑፍ ማንበቢያ ወይንም ቴሌፕሮምፕተር በጽሑፍ የተዘጋጀ ንግግርን በስክሪን ላይ የሚያሳይ ማሽን ነው። ቴሌፕሮምፕተር ባለሥልጣናት ወረቀት ሳይዙ ስክሪኑን በመመልከት ንግግራቸውን ለታዳሚዎች እንዲያቀርቡ ያስችላል።

    ከአውሮፓውያኑ 2016 አንስቶ የዋይት ሐውስ ሠራተኛ የሆነው ጋብርኤል ፔሬዝ፣ በአሜሪካው ቤተ መንግሥት የሚገኘው እና ፕሬዝዳንቱን ጨምሮ የተለያዩ ባለሥልጣናት ለንግግራቸው የሚጠቀሙበት ቴሌፕሮምፕተር ተቆጣጣሪ ነው።

    ግለሰቡ ውርርዱን ሲያካሂድ የነበረው ‘ካልሺ’ በተባለው እና ሰዎች በዓለም የሚከናወኑ ኹነቶችን በተመለከተ በመገመት መወራረድ በሚያስችለው ድረ ገጽ ላይ ነበር።

    ካልሺ የዋይት ሐውሱ ሠራተኛ ያገኘውን ትርፍ ከማውጣቱ በፊት መወራረጃ አካውንቱ እንዲታገድ ማድረጉን በወቅቱ አስታውቋል።

    ዋይት ሐውስ በቀድሞ ሠራተኛው ላይ ስለተጣለው ቅጣት እስካሁን ድረስ ያለው ነገር የለም።

    አርብ ዕለት የቅጣት ውሳኔውን ይፋ ያደረገው ተቆጣጣሪ መሥሪያ ቤት፣ የትራምፕን ንግግር ቀድሞ ማወቁን ለውርርድ “ተገቢ ባልሆነ መንገድ" መጠቀም” እንዲሁም “የተሰጠውን ኃላፊነት እና የተጣለበትን እምነት መጣስ ነው” ብሏል።

    አክሎም የተጣለበት ቅጣት ዝቅ ያለው በምርመራ ወቅት ባደረገው ትብብር የተነሳ መሆኑን አብራርቷል።

    ፔሬዝ ለሦስት ዓመት ያህል ምንም ዓይነት ውርርድ ላይ እንዳይሳተፍም ታግዷል።

    የአቋማሪ ድርጅቱ ጠበቃ ቦቢ ዴኖልት ውሳኔውን አድንቀው “ማንም ሆነ ማን መመሪያዎቻችንን ወይም የፌደራል ሕግን ከጣሰ ቅጣት ይቀበላል ” ብለዋል።

  4. በኔፓል የጎርፍ አደጋ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ከ600 በላይ ደረሰ

    በኔፓል እና ቲቤት ድንበር ላይ በደረሰው የጎርፍ አደጋ የተጎዱ ሰዎችን ለማውጣት የሚደረገው ጥረት አራተኛ ቀኑን ይዟል

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, በኔፓል እና ቻይና ድንበር ላይ በደረሰው የጎርፍ አደጋ የሞቱ እና የተጎዱ ሰዎችን ለማውጣት የሚደረገው ጥረት አራተኛ ቀኑን ይዟል

    በኔፓል እና ቲቤት ድንበር ላይ በደረሰው የጎርፍ አደጋ የሞቱ ሰዎች ቁጥር 626 መድረሱን የአገሪቱ ብሔራዊ የአደጋ ቅነሳ እና አስተዳደር ባለሥልጣን አስታወቀ።

    ባለሥልጣኑ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጹ ላይ ባጋራው መረጃ መሠረት 2ሺህ 426 ሰዎች አሁንም ድረስ የደረሱበት እንደማይታወቅ ይፋ አድርጓል።

    ፖሊስ ቀደም ብሎ 616 ሰዎች መሞታቸውን ገልጾ የነበረ ቢሆንም የባለሥልጣኑ መረጃ የሟቾች ቁጥር በፍጥነት እየጨመረ መምጣቱን ያሳያል።

    የደረሱበት ያልታወቁ ሰዎች ቁጥርም ከነበረበት 1,924 በፍጥነት ጨምሯል።

    በጎርፍ አደጋው 517 የውጭ አገር ዜጎች የጠፉ ሲሆን ቤተሰቦች እና ወዳጅ ዘመዶች ከመንግሥት የሚወጡ መረጃዎችን በቅርበት እየተከታተሉ ነው።

    ኔፓል ከቻይና ጋር በምትዋሰንበት ድንበር አቅራቢያ በደረሰው የጎርፍ አደጋ የሞቱ እና የጠፉ ሰዎችን እየፈለገች ባለችበት አራተኛ ቀን ያጋጠመው የአየር ጠባይ በሂሊኮፕተር የሚደረግ ሃሰሳን አስተጓጉሏል።

    የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች እና ወታደራዊ ባለሥልጣናት ከረቡዕ ጀምሮ በአደጋው የተጎዱ እና የሞቱ ሰዎችን ለማውጣት እየሰሩ ነው።

    የተወሰኑ ከአደጋው የተረፉ ሰዎች ከጭቃ ውስጥ ማውጣት የተቻለ ሲሆን የሕይወት አድን ሠራተኞች የጠፉ ሰዎችን ለማግኘት የተለያዩ ሥፍራዎች ላይ ሃሰሳ እያደረጉ ነው።

    የኔፓል ጦር ቃል አቀባይ ብርጋዴር ጄነራል ራጃ ራም ባስኔት ቅዳሜ ማለዳ የአየር ሁኔታው እስኪሻሻል ድረስ በሂሊኮፕተር የሚደረግ ፍለጋ ለጊዜው መቆሙን ተናግረዋል።

  5. በኢራን ጦርነት የተነሳ 400 መርከቦች በባሕረ ሰላጤው ቆመው እንደሚገኙ የመንግሥታቱ ድርጅት አስታወቀ

    በሆርሙዝ ላእ የምትቀዝፍ መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በመካከለኛው ምሥራቅ ባለው ጦርነት 400 መርከቦች በባሕረ ሰላጤው መቆማቸውን የመንግሥታቱ ድርጅት የባሕር ኤጀንሲ አስታወቀ።

    አርብ ዕለት ዓለም አቀፉ የባሕር ላይ ድርጀት (አይኤምኦ) የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ 400 ነዳጅ ጫኝ መርከቦች እና 6,000 ባሕረተኞች በባሕረ ሰላጤው ለስድስት ወራት መንቀሳቀስ ባለመቻላቸው መቆማቸውን ገልጿል።

    የአይኤምኦ ኃላፊ አርሴኒዮ ዶሚንጌዝ “የተወሰኑ መርከቦች እና ሠራተኞቻቸው ባሕረ ሰላጤውን ማቋረጥ ቢችሉም፣ ግጭቱ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ 400 የሚሆኑ መርከቦች ከ6,000 ሠራተኞቻቸው ጋር አካባቢውን ያለምንም የደኅንነት ስጋት ለቅቀው መውጣት አልቻሉም” ብለዋል።

    የዓለም አንድ አምስተኛ ነዳጅ በሚተላለፍበት እና ወሳኝ በሆነው ሆርሙዝ ወሽመጥ ያለውን ሁኔታ “ያልተፈታ” ሲሉ ገልጸውታል።

    የመንግሥታቱ ድርጅት ኤጀንሲ የካቲት 21፣ 2018 ዓ.ም. የኢራን ጦርነት ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ በወሽመጡ በኩል የሚያልፉ መርከቦች ላይ 70 ጥቃቶች መፈጸማቸውን እና 19 ባሕረተኞች መሞታቸውን አረጋግጧል።

    ዶሚንጌዝ እንደገለጹት፣ ለነዳጅ እና ለማዳበሪያ የሚሆኑ ወሳኝ የአቅርቦት ሰንሰለቶች መስተጓጎል በዓለም ዙሪያ በሚገኙ ማኅበረሰቦች እና ኢኮኖሚዎች ላይ "ከባድ" መዘዞችን ያስከትላል።

    በተለይም "ከፍተኛ ስጋት እና እርግጠኛነት በጠፋበት ሁኔታ" ውስጥ ለሚኖሩ በሺዎች የሚቆጠሩ "ንፁኀን" ሁኔታው እጅግ አሳሳቢ መሆኑን ጠቁመዋል።

    ዶሚንጌዝ በወሽመጡ የሚደረግ የመርከብ እንቅስቃሴ ነፃነትን ወደነበረበት ለመመለስ፣ ከአባል አገራት እና ከመርከብ ትራንስፖርት ዘርፍ “አዲስ የፖለቲካ ቁርጠኝነት” እንዲኖር ጠይቀዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን በሰኔ ወር የመግባቢያ ስምምነት ተፈራርመው የመጨረሻውን የሰላም ስምምነት ላይ ለመድረስ ድርድር ማድረግ ጀምረው ነበር።

    ነገር ግን በኋላ ላይ በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚደረግ የመርከቦች እንቅስቃሴ ላይ መግባባት ላይ ባለመደረሱ ንግግሮቹ ተቋርጠዋል።

  6. የአሜሪካ ዲፕሎማቶች በመካከለኛው ምሥራቅ ወደሚገኙ ኤምባሲዎች መመለስ ጀመሩ

    በኩዌት የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ሰንደቅ ዓላማ ሲሰቀል

    የፎቶው ባለመብት, AP

    የምስሉ መግለጫ, በኩዌት የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ሰንደቅ ዓላማ ሲሰቀል

    የአሜሪካ ዲፕሎማቶች እና የተወሰኑ የቤተሰብ አባላቶቻቸው በመካከለኛው ምሥራቅ ወደሚገኙ ኤምባሲዎች መመለስ ጀመሩ።

    በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኙ ዲፕሎማቶች የኢራን ጦርነት በተጀመረ በመጀመርያዎቹ ሳምንታት ውስጥ ለቅቀው እንዲወጡ ተነግሯቸው ነበር።

    ምንም እንኳን ኤምባሲዎቹ በሙሉ አቅማቸው ወደ ሥራ ባይገቡም ከዚህ ሳምንት ጀምሮ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በሠራተኞቹ እና በእንቅስቃሴያቸው ላይ ጥሏቸው የነበሩ ገደቦችን ማንሳት ጀምሯል።

    ለውጦቹ የትራምፕ አስተዳደር በኢራን ላይ የያዘውን ፖሊሲ መለወጡን አያሳይም የተባለ ሲሆን፣ አሁን ከወታደራዊ ዘመቻ ይልቅ የኢኮኖሚ ጦርነት ማድረጉን እንደሚቀጥል ተጠቅሷል።

    የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በመካከለኛው ምሥራቅ በሚገኙ ኤምባሲዎች የሚሠሩ ዲፕሎማቶች እንዲመለሱ የወሰነው በዋናነት ከሰው ኃይል ፖሊሲ ጋር በተያያዙ ሕጋዊ ሁኔታዎች መሆኑ ተገልጿል።

    ሕጎቹ ዲፕሎማቶቹ ደመወዝና ለራሳቸውም ሆነ ለቤተሰቦቻቸው የሚሰጡ ጥቅማጥቅሞችን እያገኙ ከሥራ ቦታቸው ውጭ ሊቆዩ የሚችሉበትን ጊዜ የሚገድቡ ናቸው ተብሏል።

    የኢራን ጦርነት አርብ ዕለት ስድስተኛ ወሩን የያዘ ሲሆን በኳታር፣ ኩዌት እና ባሕሬን የሚገኙ ዲፕሎማቶች እና ቤተሰቦቻቸው እንደሚመለሱ ተነግሯል።

    በባሕሬን እና በኩዌት የሚገኙ ዲፕሎማቶች መውሰድ የሚችሉት ከ18 ዓመት በላይ የሆናቸውን የቤተሰብ አባላቶቻቸውን መሆኑም ተገልጿል።

    በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ፣ በእስራኤል የሚገኙ የአሜሪካ መንግሥት ሠራተኞች ቤተሰቦች በሙሉ እንዲሁም በሊባኖስ ከሚሠሩት ሠራተኞች ዕድሜያቸው ከ21 ዓመት በላይ የሆኑ ቤተሰቦቻቸው ወደ አገራቸው እንዲመለሱ ፈቃድ ተሰጥቷቸዋል።

    እነዚህ ኤምባሲዎች ኢራን አሜሪካ እና እስራኤል ለከፈቱባት ጦርነት የአጸፋ እርምጃ መውሰድ ስትጀምር ለቅቀው እንዲወጡ ትዕዛዝ የተሰጣቸው ናቸው።

    የኢራን ጦርነት እንደተጀመረ በሌሎች አምስት አገራት የሚገኙ የአሜሪካ ኤምባሲ ሠራተኞችም እንዲወጡ የተደረገ ሲሆን እነርሱም በቅርቡ እንዲመለሱ ሊደረግ ይችላል ተብሏል።

  7. በኔፓል የጎርፍ አደጋ የሟቾች ቁጥር 579 ሲደርስ፤ 2,000 የሚጠጉ ሰዎች የደረሱበት አልታወቀም

    የሚያለቅሱ እናት እና ልጅ ከሌሎች ሰዎች ጋር

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    ከትናንት በስቲያ በኔፓል በተከሰተው ድንገተኛ የጎርፍ አደጋ የሞቱ ሰዎች ቁጥር 579 መድረሱ ሲገለጽ፤ በሺዎች የሚቆጠሩ የደረሱበት አልታወቀም።

    የኔፓል የአደጋ ጊዜ ኤጀንሲ እንደገለጸው ከጠፉት ሰዎች መካከል ቢያንስ 517ቱ የውጭ ዜጎች ናቸው።

    ከኔፓል ጋር በምትዋሰነው የቻይናዋ ራስ ገዝ አስተዳደር ቲቤትም በአደጋው አምስት ሰዎች የሞቱ ሲሆን ከ550 በላይ የሚሆኑ መጥፋታቸውን የቻይና የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    ሁኔታዎች በፍጥነት የሚለዋወጡ በመሆኑ የተለያዩ ባለሥልጣናት የሚገልጹት ቁጥር የተለያየ ቢሆንም የሟቾች ቁጥር እየጨመረ ነው።

    አደጋው ከተከሰተ ከሁለት ቀናት በኋላም የነፍስ አድን ጥረቱ እንደቀጠለ ነው።

    የጠፉ ሰዎችን በተመለከተ የሚወጡ መረጃዎችን ወዳጅ ዘመዶቻቸው በጭንቀት እየጠበቁ ይገኛሉ።

    በቻይና እና ኔፓል ድንበር ላይ የተፈጠረው መጠኑ እየጨመረ ያለ ሐይቅ ፈንድቶ ሌላ ጎርፍ ሊያስከትል ይችላል በሚልም ተሰግቷል።

    በቲቤት የተሰማሩ የቻይና የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች፣ የሐይቁ ዳርቻዎች ተንዶ ድጋሚ የከፋ ጎርፍ ሊከሰት ይችል እንደሆነ ትናንት ጥናት ሲያደርጉ ውለዋል።

    በተፈጠረው ስጋት ምክንያትም በቲቤት የተሰማሩ የአደጋ ጊዜ ሰራተኞች ሥራቸውን እንዲያቋርጡ ተደርጓል።

    አስከፊው ድንገተኛ የጎርፍ አደጋ የተከሰተው ረቡዕ ዕለት በቲቤት በኩል ያለ የበረዶ ግግር መናዱን ተከትሎ ነው።

    አደጋው የተከሰተበት የኔፓል-ቲቤት ድንበር በየዓመቱ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ጎብኚዎችን ያስተናግዳል።

  8. በሱዳን መዲና ኻርቱም ለሁለት ዓመታት ተጥሎ የቆየው የሰዓት እላፊ ተነሳ

    ኻርቱም ከተማ ሰዎች ሲንቀሳቀሱ

    የፎቶው ባለመብት, Anadolu via Getty Images

    በሱዳን ጦር የሚመራው መንግሥት ከሁለት ዓመት በፊት በኻርቱም ላይ ተጥሎ የነበረውን የሰዓት እላፊ እና የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማንሳቱን የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    ባለሥልጣናቱ ይህንን እርምጃ የወሰዱት ጦሩ በተፈላሚው ፈጥኖ ደራሽ ኃይል (አርኤስኤፍ) ተይዛ የነበረችውን ከተማዋን መልሶ ከተቆጣጠረ ከ18 ወራት በኋላ ነው።

    ሆኖም ግጭቱ በግዛቷ ደቡባዊ እና ምዕራባዊ አካባቢዎችም እንደቀጠለ ሲሆን ጦርነቱ ወደ ሱዳን ድንበሮች እየተዛመተ መሆኑን የሚያሳዩ መረጃዎች አሉ።

    ከአራት ዓመት በፊት በሥልጣን ሽኩቻ ሰበብ በአገሪቱ በተቀሰቀሰው ጦርነት አምስት ሚሊዮን የሚጠጉ የኻርቱም ነዋሪዎች ለመፈናቀል ተዳርገው ነበር።

    ከመጋቢት ወር ጀምሮ ግን ግጭቱ በመቆሙ ተፈናቅለው ከነበሩት ውስጥ ከ2 ሚሊዮን በላይ ነዋሪዎች መመለሳቸውን ዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት (አይኦኤም) ገልጿል።

    አሁን ላይ የሰዓት እላፊው እንዲነሳ መደረጉም በከተማ ያለውን እንቅስቃሴ ወደ መደበኛ ሁኔታ ለመመለስ ያለመ ነው።

    መንግሥት በከተማዋ ያለውን ዋና አየር ማረፊያ ለተወሰኑ በረራዎች ክፍት ያደረገ ሲሆን የንግድ ተቋማት እና ኤምባሲዎችም እንዲመለሱ እያበረታታ ነው።

    ሆኖም ነዋሪዎች አሁንም ኑሯቸውን እንደገና ለማቋቋም ተቸግረዋል።

    አብዛኞቹ ነዋሪዎች ወደ ከተማዋ ሲመለሱ በርካታ ሕንፃዎች ወድመው እና ተዘርፈው ነው ያገኙት። ከዚህም በተጨማሪ አርኤስኤፍ ቢያስተባብልም በኤሌክትሪክ መሰረተ ልማት ላይ ፈፀመው በተባለው የድሮን ጥቃት የኃይል መቋረጥ አጋጥሟቸዋል።

    አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ቢነሳም ባለሥልጣናቱ የአርኤስኤፍ ታጣቂዎች ሰርገው ሊገቡ ይችላሉ የሚልም ስጋት አላቸው። በመሆኑም በግዛቷ የደኅንነት ፍተሻ መካሄዱ የሚቀጥል እንደሆነ እና በምሽት የሚጓዙ መንገደኞችም መታወቂያ መያዝ እንደሚኖርባቸው የሱዳን የዜና ወኪል ዘግቧል።

  9. የዓለማችን በዕድሜ ትንሹ ባህላዊ ንጉሥ በ34 ዓመታቸው አረፉ

    የዓለማችን በዕድሜ ትንሹ ንጉስ ቶሮ

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    በዓለም በዕድሜ ትንሹ ንጉሥ የነበሩት የኡጋንዳ ባህላዊ መሪ በ34 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸውን ጠቅላይ ሚኒስትራቸው አስታወቁ።

    ኦዮ ኒይምባ ካባማ ኢጉሩ ሩኪዲ አራተኛ የአባታቸውን ሞት ተከትሎ ነበር በአውሮፓውያኑ 1995 በሦስት ዓመታቸው የቶሮ ንጉሥ ሆነው የተሰየሙት።

    ይህም የዓለማችን በዕድሜ ትንሹ ንጉሥ እንዲሆኑ ያደረጋቸው ሲሆን፣ 18 ዓመት እስከሚሞላቸው ድረስ እናታቸው በተካተቱበት እና ሦስት አባላት ባሉት ምክር ቤት ንጉሣዊ ሥርዓቱ ሲመራ ነበር።

    የቶሮ ግዛት የንጉሡን ሞት መንስዔ አልገለጸም። ሆኖም የአገሪቷ መገናኛ ብዙኃን አንድ የኡጋንዳን መንግሥት ሚኒስትር ጠቅሶ እንደዘገበው ንጉሡ በጠና ታመው በአሜሪካ ህክምና ሲደረግላቸው ነበር።

    ቶሮ በምዕራብ ኡጋንዳ የሚገኝ እና ረዥም ታሪክ ባለው ጥንታዊ የባንቱ ባህላዊ መንግሥት የሚመራ ግዛት ነው።

    ኡጋንዳ በሕዝብ በተመረጠ ፕሬዝዳንት ብትመራም፣ ፖለቲካዊ ሥልጣን ባይኖራቸውም ተፅእኖ መፍጠር የሚችሉ በርካታ ባህላዊ መሪዎች አሏት።

    በዓለም የድንቃ ድንቅ መዝገብ ውስጥ የዓለማችን በዕድሜ ትንሹ ባህላዊ ንጉሥ በሚል ስማቸው የሰፈረው ኦዮ፣ ከ2 ሚሊዮን በላይ የሚገመት የቶሮን ሕዝብ ሲመሩ ነበር። ኦዮ በ19ኛው ክፍለ ዘመን የተመሠረተው ንጉሣዊ ሥርዓት 13ኛው ንጉሥ ነበሩ።

    ሕልፈታቸውን ያስታወቁት የቶሮ ጠቅላይ ሚኒስትር ካልቪን አርምስትሮንግ ሪዎማይር፣ የንጉሡ ህልፈት ለንጉሣውያን ቤተሰቦች እና ለቶሮ ሕዝብ “ትልቅ እጦት” ነው ብለዋል።

    “በዚህ ከባድ ወቅት የቶሮ ሕዝብ በአንድነት፣ በመረጋጋት እና በፀሎት እንዲቀጥል ጥሪ አቀርባለሁ” ሲሉም ንጉሣ በሰላም እንዲያርፉ ተመኝተዋል።

    የቶሮ ግዛት ንጉሡን ለመምረጥ በዘር የሚተላለፍ ንጉሣዊ ሥርዓትን ይከተላል። ኦዮ በይፋ ስላላገቡ ዘውዱን ማን ይረከባል የሚለው አይታወቅም። ሆኖም ጠቅላይ ሚኒስትራቸው “የዘውዱ ሽግግር የተረጋገጠ ነው” ብለዋል።

    ግርማዊነታቸው “ወራሽ የሆነ ልዑል ትተው ነው ያረፉት። ማንነቱ በተገቢው ጊዜ፣ በቶሮ መንግሥት ወግ እና ባህል መሠረት ይገለጻል” ሲሉ አስረድተዋል።

    ኦዮ በሕዝብ ዘንድ የተወደዱ እና በወጣቶች አቅም ማጎልበት፣ በትምህርት እና በአካባቢ ጥበቃ እንዲሁም በኤችአይቪ/ኤድስ ግንዛቤ ማስጨበጥ ሥራዎችን ሲያበረታቱ እንደነበር ዴይሊ ሞኒተር ጋዜጣ ዘግቧል።

  10. ሁሉም አገራት የአሜሪካን ማዕቀብ ከመተግበር እንዲቆጠቡ ኢራን አሳሰበች

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ

    የፎቶው ባለመብት, AFP

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር “የኢኮኖሚ ሽብር” ሲል የገለፀውን የአሜሪካን ማዕቀብ በማውገዝ፣ ሁሉም አገራት እና መንግሥታት ማዕቀቡን ተግባራዊ ከማድረግ እንዲቆጠቡ አሳሰበ።

    ሚኒስቴሩ በመግለጫው፣ አሜሪካ በኢራን ላይ የጣለችውን የአንድ ወገን ማዕቀብ በመተግበር መሳተፍ የአንድን አገር "ሕገ ወጥ ፈቃድ" በሉዓላዊ አገር ላይ በመጣል ሕጋዊ የሆነውን "የኢኮኖሚ እና የንግድ ግንኙነትን ለማወክ ከመተባበር" ጋር ተመሳሳይ ነው ብሏል።

    ይህም የተባበሩት መንግሥታት ቻርተር የሚያረጋግጠው ‘የሉዓላዊ አገራት እኩልነት’ መርኅ ጥሰት ላይ መሳተፍ እንደሆነ መግለጫው አስረድቷል።

    የአሜሪካ ማዕቀቦች "ሙሉ በሙሉ ሕገ ወጥ እና ኢ- ፍትሃዊ እንዲሁም የተባበሩት መንግሥታትን ቻርተር፣ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊነት ሕግን እና የሰብዓዊ መብቶችን" የሚጥስ እንደሆነም መግለጫው ጠቅሷል።

    በመሆኑም ሁሉም አገራት እና መንግሥታት ለእንደዚህ ዓይነት ማዕቀቦች ዕውቅና ከመስጠት እና ከማጽደቅ እንዲሁም ሕገ ወጥ እርምጃን ከመተግበር መቆጠብ እንዳለባቸው አሳስቧል።

    ሚኒስቴሩ ጨምሮም አሜሪካ ኢራንን በኢኮኖሚ ለማግለል የወጠነችው ዕቅድ “በውስጥ ጉዳዮች ጣልቃ መግባትን እና በአገራት መካከል የሚደረገውን ትብብር ማወክን” የሚከለክለውን የተባበሩት መንግሥታትን መርኅ የሚጥስ ነው ብሏል።

    ሚኒስቴሩ ይህን ያለው አሜሪካ ከኢራን ጋር የንግድ ግንኙነት ባላቸው ተቋማት፣ ባንኮች እና አገራት ላይ ጭምር ማዕቀቦችን በመጣል እንደምትቀጣ ካስታወቀች በኋላ ነው።

  11. ከአሜሪካ ጋር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትን መመለስ እንደሚቻል የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ገለፁ

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ከኳታሩ ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጋር ቴህራን ውስጥ ካደረጉት ንግግር በኋላ፣ ከአሜሪካ ጋር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትን ወደነበረበት መመለስ “የማይቻል አይደለም” ሲሉ ተናገሩ።

    አራግቺ ከኳታሩ ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሼኽ ሞሐመድ ቢን አብዱልራህማን ቢን ጃሲም አል ታኒ ጋር “ውጤታማ ውይይት” እንዳደረጉ በኤክስ ገጻቸው ላይ ተናግረዋል።

    “ዲፕሎማሲን ወደ ትክክለኛው መንገድ መመለስ የማይቻል አይደለም። ይህ የሚወሰነው አሜሪካ በአንድ ቀላል እውነታ ላይ በሚኖራት ግንዛቤ ነው፤ ጫና መፍጠር አይሰራም” ብለዋል።

    “አሜሪካ እምነትን መገንባት፣ በአክብሮት መናገር፣ መብቶቻችንን መቀበል እና የገባችውን ቃል መፈፀም አለባት” ሲሉ የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አክለዋል።

    በኢራን እና አሜሪካ መካከል ያለውን ውጥረት ለማርገብ ዶሃ እየሠራች ባለችበት ወቅት ነው ሼኽ ሞሐመድ ሐሙስ ዕለት በቴህራን ጉብኝት ያደረጉት።

    በጉብኝታቸውም ከኢራኑ ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን፣ ከአራግቺ፣ ከፓርላማ አፈጉባዔው ሞሐመድ ባገር ጋሊባፍ እና ከኢራን ጠቅላይ ብሔራዊ የደኅንነት ምክር ቤት ፀሐፊ ሞህሰን ረዛኢ ጋር ተነጋግረዋል።

    በአሜሪካ እና ኢራን መካከል የተጀመረውን ውይይት ማስቀጠል የሚቻልበትን ሁኔታ መፍጠር እንዲሁም በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ጊዜያዊ የጋራ የመርከብ መተላለፊያ መንገድ ማበጀት እና አካባቢውን ከፈንጂዎች እና ሌሎች መሣሪያዎች የማፅዳት ጥረቶች የተነጋገሩባቸው ጉዳዮች ናቸው።

    የአሜሪካ እና እስራኤልን ጥቃት ተከትሎ የካቲት ወር ላይ ጦርነቱ ከተቀሰቀሰ ወዲህ የኳታር የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በኢራን ጉብኝት ሲያደርጉ የአሁኑ የመጀመሪያቸው ነው።

  12. የሱዳን ጦር ከሁለት ዓመት በላይ በካርቱም ጥሎት የነበረውን የሰዓት እላፊ አነሳ

    የሱዳን ባንዲራ

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የሱዳን ጦር ከሁለት ዓመት በላይ በካርቱም ላይ ጥሎት የነበረውን የሰዓት እላፊ ማንሳቱን የአገሪቱ ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን ዘገበ።

    የጦሩ ባለሥልጣናት የሰዓት እላፊውን ያነሱት ከተማዋን ከፈጥኖ ደራሽ ኃይሉ ካስለቀቁ ከ18 ወራት በኋላ ነው።

    በሱዳን እየተካሄደ ያለው የእርስ በእርስ ጦርነት ከካርቱም ውጭ ባሉ የአገሪቱ ከተሞች እንደቀጠለ ነው።

    የአገሪቱ ጦር ካርቱምን ከአማጺያኑ ካስለቀቀ በኋላ ከሁለት ሚሊዮን በላይ ሰዎች ወደካርቱም ተመልሰው መደበኛ ሕይወታቸውን ቀጥለዋል።

    ነገር ግን በጦርነት ምክንያት በርካታ መሠረተ ልማቶች በመውደማቸው በተደጋጋሚ የኤሌትሪክ መቆራረጥ እንደሚያጋጥማቸው ይነገራል።

    የፈጥኖ ደራሹ ኃይሎች ወደ ከተማዋ ሰርገው እንዳይገቡ ለመከላከል የጦሩ አባላት በየጊዜው የቅኝት ስራ እንደሚሰሩ የአገሪተ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    በምሽት የሚንቀሳቀሱ የከተማዋ ነዋሪዎችም ማንነታቸውን የሚገልጽ መታወቂያ ይዘው እንዲንቀሳቀሱ አሳስበዋል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ ቻድ የሱዳን ጦር በድንበር አቅራቢያ በፈጸመው የአየር ድብደባ የአገሪቱ ጦር ላይ ጉዳት ማድረሱን ገልጻ ከስሳለች።

    የሱዳን ጦር የቻድ መንግሥት ክስን ውድቅ አድርጓል።

    የአሜሪካ መንግሥት የሱዳን ጦርነት ከአገሪቱ ድንበር ሊያልፍ ይችላል የሚል ስጋት እንዳለው ገልጿል።

  13. የአሜሪካ ጦር በአውሮፓ "ከፍተኛ የሚሳዔል መቃወሚያ እጥረት" እንደገጠመው ተዘገበ

    የሩሲያን ተምዘግዛጊ ባሌስቲክ ሚሳዔልን መትቶ መጣል በሚችለው ፓትሮይት ተብሎ በሚጠራው የሚሳዔል መቃወሚያ

    የፎቶው ባለመብት, AP

    የአሜሪካ መከላከያ በኢራን እያካሄደ ካለው ጦርነት ጋር በተያያዘ በአውሮፓ ከፍተኛ የሆነ ዘመናዊ የሚሳዔል መቃወሚያዎች እጥረት እንደገጠመው የፈረንሳዩ የዜና ወኪል ዘገበ።

    አሶሼትድ ፕሬስ የአሜሪካ መከላከያ ባለሥልጣናትን እና የኔቶ ኃላፊዎችን ጠቅሶ እንደዘገበው ጦሩ “እጅግ ወሳኝ በሆነ ደረጃ” ላይ የሚገኝ ዘመናዊ የሚሳኤል መቃወሚያ እጥረት አጋጥሞታል።

    ይህ ሁኔታ የኔቶ አባል አገራት ከሩሲያ ሊሰነዘር ለሚችል ጥቃት ተጋላጭ የሚያደርግ በመሆኑ ስጋት መፈጠሩን ጨምረው አስረድተዋል።

    የአሜሪካ መከላከያ ባለሥልጣናት እጥረቱ በይበልጥ የተፈጠረው የሩሲያን ተምዘግዛጊ ባሌስቲክ ሚሳዔልን መትቶ መጣል በሚችለው ፓትሮይት ተብሎ በሚጠራው የሚሳዔል መቃወሚያ ላይ ነው ብለዋል።

    የኔቶ ኃላፊዎች በአሜሪካ ጦር እና በአውሮፓ በሚገኙ የኔቶ አባል አገራት ዘንድ የፓትሮይት ሚሳዔል እጥረት መኖሩን አረጋግጠዋል።

    ስማቸው እንዳይገለጽ የጠየቁ ኃላፊዎች በአውሮፓ የሚገኘው የአሜሪካ ጦር “በእርግጠኝነት” ከሩሲያ ሊተኮስ የሚችል ባሌስቲክን የሚያከሽፍበት ፓትሮይት ሚሳዔል እጥረት አለበት ብለዋል።

    ኃላፊዎቹ ከሩሲያ ለሚሰነዘር ማንኛውንም የባሌስቲክ ሚሳዔል ጥቃት ለመከላከል ያለው አቅም “በጣም ውስን” መሆኑን ጨምረው ገልጸዋል።

    ምንም እንኳን በኔቶ አባል አገራት ላይ ሩሲያ የባለስቲክ ሚሳዔል ጥቃት ትፈጽማለች ተብሎ ባይጠበቅም የሲአይኤ ዳይሬክተር ጆን ራትክሊፍ በዚህ ሳምንት ወደ ሞስኮ ተጉዘው ሩሲያ ጥቃት እንዳትፈጽም ማስጠንቀቃቸውን ዎል ስትሪት ጆርናል ዘግቧል።

    ሐሙስ ዕለት የሲአይኤ ኃላፊ መልዕክቱን ለፑቲን አድርሰው እንደሆን የተጠየቁት ትራምፕ “በዚህ ጉዳይ ላይ አስተያየት መስጠት አልፈልግም፤ ነገር ግን ጥቃት አይፈጽሙም” ሲሉ በደፈናው መልሰዋል።

  14. ትራምፕ አሜሪካንን ከመሩ ፕሬዝዳንቶች ሁሉ የተለየሁ ነኝ አሉ

    ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, EPA

    አነጋጋሪ ጉዳዮችን በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ በማጋራት የሚታወቁት ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ራሳቸውን እስካሁን አሜሪካንን ከመሩ ፕሬዝዳንቶች ሁሉ የላቁ መሆናቸውን ገለጹ።

    የመጀመሪያዎቹን ጨምሮ በፈታኝ ሁኔታ ውስጥ አሜሪካንን የመሩ የ34 ፕሬዝዳንቶችን ምሥል በመደርደር የተለያዩ ደረጃዎችን የሰጡት ትራምፕ ራሳቸውን “ከሁሉም ያላቁ” አድርገው በማቅረብ መነጋገሪያ ሆነዋል።

    በትሩዝ ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ በአሜሪካ ፕሬዝዳንቶች ታሪክ ራሳቸውን “የታላቆች ታላቅ” በሚለው ደረጃ ላይ በማስቀመጥ ሌሎቹን በተለያዩ ደረጃዎች “ደካማ” እስከሚል ፈርጀው ከእሳቸው ስር አስቀምጠዋቸዋል።

    በርካቶቹን የአሜሪካ ቀደምት ፕሬዝዳንቶች ከዝርዝሩ ውስጥ ባለማካተትም ቦታ ነፍገዋቸዋል። ምናልባትም ያልተካተቱት “ደካማ” ከተባሉት በታች ያሏቸውን ሊሆን ይችላል።

    ከአውሮፓውያኑ 1789 አሜሪካ 47 ፕሬዝዳንቶች ተፈራርቀው የመሯት ሲሆን፣ በትራምፕ የደረጃ ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት ግን 34ቱ ብቻ ናቸው። የዓለማችን የዲሞክራሲ ተምሳሌት የምትባለውን አገር እስካሁን ሴት ፕሬዝዳንት አልመራቻትም።

    ትራምፕ ከንጽጽር ያቀረቧቸውን ቀደምት ፕሬዝዳንቶች በስድስት ክፍል የመደቧቸው ሲሆን፣ ራሳቸውን “የታላላቆች ታላቅ”፣ እርሳቸውን የሚከተሉትን ደግሞ “ታላቅ”፣ ከዚያም “ለታላቅነት የቀረቡ”፣ “መካከለኛ”፣ “ከመካከለኛ በታች” እና ደካሞች” ብለዋቸዋል።

    “ደካማ” ከሚለው ምድብ ስር ያካተቷቸው ከእሳቸው የቀደሙትን ባራካ ኦባማ እና ጆ ባይደንን እንዲሁም ጂሚ ካርተር፣ ዋረን ሃርዲንግ እና ኡሊሴስ ግራንት ይገኙበታል።

    የትራምፕ ዝርዝር

    የፎቶው ባለመብት, @realDonaldTrump

    የምስሉ መግለጫ, የትራምፕ ዝርዝር
  15. ኢራን የሆርሙዝን የባህር ወሽመጥ ዳግም ለመክፈት ቅድመ ሁኔታዎችን አስቀመጠች

    በቴህራን ጎዳናዎች ላእ የሚንቀሳቀሱ ሰዎች

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ኢራን ላለፉት ስድስት ወራት ከአሜሪካ ጋር እያdረገችው ባለው ጦርነት ምክንያት ዘግታው የቆየችውን የሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ ዳግም ለመክፈት ቅድመ ሁኔታዎችን አስቀመጠች።

    ወሳኙን የባሕር መተላለፊያ ለመክፈት በመካከለኛው ምሥራቅ የሚደረጉ ጦርነቶችን እንዲቆሙ ማድረግ ከቅድመ ሁኔታዎቿ መካከል አንዱ መሆኑን ገልጻለች።

    የኢራን ጠቅላይ ብሔራዊ የፀጥታ ምክር ቤት ፀሐፊ ሞህሰን ሬዛኢ ከሊባኖሱ አል ማናር ቴሌቪዥን ጋር በነበራቸው ቃለ ምልልስ በባሕረ ሰላጤው ላይ ከአሜሪካ ጋር የሚደረግ ማንኛውም መግባባት በሊባኖስ፣ በጋዛ እና በሶሪያ ውስጥ የሚደረጉ ጦርነቶችን እና ወታደራዊ እንቅስቃሴዎችን ማቆምን ያካትታል ብለዋል።

    በጋዛ ሰርጥ የተፈጠረው ግጭት መቆም እንዳለበት የተናገሩት የደኅንነት ኃላፊው፣ እስራኤል ከሊባኖስ እንድትወጣ እና በሶሪያ ላይ የሚሰነዘረውን ጥቃት እንድታቆም ጠይቀዋል።

    ሬዛኢ በሆርሙዝ ወሽመጥ አካባቢ ያለው ችግር በቀጣናው ውስጥ ካለው እጅግ ሰፊ ግጭት መካከል አንዱ ነው ካሉ በኋላ ኢራን በአሜሪካ ላይ እንደገና እምነት ልትጥል የምትችለው፣ የገባችውን ቃል በተግባር ለማሳየት ያላትን ቁርጠኝነት ካረጋገጠች በኋላ ብቻ ነው ብለዋል።

    ይሁን እንጂ ሁለቱ አገራት ዳግም ወደ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት መመለስ የሚቻሉ አይመስልም። ዎል ስትሪት ጆርናል ሐሙስ ዕለት እንደዘገበው የትራምፕ አስተዳደር በሰኔ ወር ከኢራን ጋር ወዳደረገው የመግባቢያ ስምምነት ለመመለስ ፍላጎት የለውም።

    ጋዜጣው ጉዳዩን በቅርበት የሚያውቁ ሰዎችን በመጥቀስ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በሰኔ ወር የስምምነት ማዕቀፍ ላይ ፍላጎት እንደሌላቸው እና በምትኩ አስተዳደራቸው ኢራንን በኢኮኖሚያዊ ጫና ለማንበርከክ አንደሚችል እምነት አላቸው።

    አሜሪካ ሰኞ ዕለት ከቴህራን ጋር የንግድ ግንኙነት ያላቸው አገራትን አስጠንቅቃ “ኢኮኖሚያዊ ጦርነት” መክፈቷን አስታውቃለች። ይህም የአሜሪካ ትኩረት ከወታደራዊ እርምጃ ወደ ኢኮኖሚያዊ ጫና መሸጋገሩን ያመለካተ ነው።

    ኢራን መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ እንዲያልፉ “ጊዜያዊ እና የተወሰነ” መስመር የፈቀደች ሲሆን፣ ወደፊት የሚኖር የመርከቦች ፍሰት ከዋሽንግተን ጋር በሚደረጉ ግንኙነቶች ላይ የተመሠረተ ይሆናል ሲሉ ሬዛኢ ተናግረዋል።

    በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ ኦማን እና ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ጊዜያዊ ደኅንነቱ የተጠበቀ የመርከቦች መተላለፊያ መስመር ለማቋቋም እንዲሁም ከዋና ዋና የነዳጅ ጫኝ መርከቦች መተላለፊያ መስመሮች ፈንጂዎችን ለማጽዳት ተወያይተዋል።

    ይሁን እንጂ፣ የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ አዛዥ አድሚራል ብራድ ኩፐር ሐሙስ ዕለት በአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) የኤክስ ገጽ ላይ በቪዲዮ ባስተላለፉት መልዕክት የአሜሪካ ወታደሮች ፈንጂዎችን ከባሕር ወሽመጥ ላይ ማጽዳታቸውን ተናግረዋል።

    ሴንትኮም ባለፉት በርካታ ወራት ውስጥ ወደ 1,500 የሚጠጉ የንግድ መርከቦችን እና 750 ሚሊዮን በርሜል ድፍድፍ ነዳጅ የጫኑ መርከቦች እንዲያልፉ ማገዙን ኩፐር ተናግረዋል።

    ኩፐር አክለውም “ዛሬ፣ ዓለም አቀፍ የመርከብ መስመሮች ክፍት ናቸው፣ እናም ፍጥነቱ እየጨመረ ነው” ብለዋል።

    ይሁን እንጂ፣ የቅርብ ጊዜ መረጃዎች እንደሚያሳዩት ማክሰኞ ዕለት ሆርሙዝን ያቋርጡት አምስት መርከቦች ብቻ ናቸው።

    ይህ ደግሞ በየካቲት ወር ጦርነቱ ከመጀመሩ በፊት በዚህ ወሳኝ በሆነው ወሽመጥ በኩል በየቀኑ ሲያቋርጡ ከነበሩት በግምት 130 መርከቦች በጣም ያነሰ ነው።

  16. ከኢራን ጋር ውጥረትን ለመቀነስ የሚያስችል ውይይት አድርገናል- ኳታር

    የኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣናት ከኳታር ልዑካን ጋር ሲወያዩ

    የፎቶው ባለመብት, Mehr

    የኳታሩ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከኢራን ባለሥልጣናት ጋር ውጥረትን መቀነስ የሚያስቸል ውይይት ማድረጋቸው ተገለጸ።

    የኳታር ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ ዛሬ በቴህራን የደረሰው የኳታር ልዑካን ቡድን ከአባስ አራጋቺ ጋር “ውጥረትን በሚቀንስ እና ለንግግር ምቹ ሁኔታን በሚፈጥሩ” ጉዳዮች ዙሪያ መወያየቱን አስታውቋል።

    ሚኒስቴሩ በመግለጫው ላይ ኢራን እና ኳታር ከሆርሙዝ ወሽመጥ ፈንጂዎችን ለማጽዳት የሚያስችል "የጋራ ፕሮጀክት" ተግባራዊ ለማድረግ በሚደረስ ስምምነት፣ እንዲሁም "ውጥረትን ለመቀነስ እና ለውይይት ተስማሚ ሁኔታዎችን ለመፍጠር ስለሚደረጉ ጥረቶች" ተወያይተዋል ብሏል።

    የኢራን የዜና ወኪል ታስኒም በበኩሉ የኢራን ፓርላማ አፈ-ጉባኤ እና ዋና ተደራዳሪ መሐመድ ባጌር ጋሊባፍ በቴህራን ከኳታር ጠቅላይ ሚኒስትር ጋር ባደረጉት ውይይት፣ በቀጣናው ያለውን ውጥረት የማርገብ አስፈላጊነት ላይ አጽንኦት ሰጥተው መናገራቸውን ዘግቧል።

    የኳታር የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ፣ የሁለቱ ሚኒስትሮች ውይይት "በቀጣናው የታዩ አዳዲስ ክስተቶችን፣ እንዲሁም ውጥረትን ለመቀነስ እና የክልሉን ደህንነትና መረጋጋት ለማጠናከር በሚረዱ ውይይቶች ላይ ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠር የተደረጉ ጥረቶችን" እንደገመገመ ተገልጿል።

    የኳታር ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሞሃመድ ቢን አብዱልራህማን ቢን ጃሲም አል ታኒ፣ ወደ ቴህራን በመጓዝ፣ ከኢራን ፓርላማ አፈ-ጉባኤ እና ዋና ተደራዳሪ ሞሃመድ ባጌር ጋሊባፍ እንዲሁም ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ጋር ተገናኝተዋል።

    ከፍተኛ የኳታር ልዑካን ቡድን ወደ ቴህራን ያመራው የፓኪስታን የጦር ኃይሎች ዋና አዛዥ ጄኔራል አሲም ሙኒር በኢራን ከተገኙ ከሁለት ቀናት በኋላ ነው።

  17. በኔፓል ድንገተኛ የጎርፍ አደጋ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ከ300 በላይ መድረሱ ተገለጸ

    ባለሙያዎች በወንዞች ውስጥ በተከማቹ ፍርስራሾች የተነሳ “ሁለተኛ እና ሦስተኛ ዙር” የጎርፍ አደጋ ሊኖር ይችላል ሲሉ ፍርሃታቸውን ገልጸዋል።

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ባለሙያዎች በወንዞች ውስጥ በተከማቹ ፍርስራሾች የተነሳ “ሁለተኛ እና ሦስተኛ ዙር” የጎርፍ አደጋ ሊኖር ይችላል ሲሉ ፍርሃታቸውን ገልጸዋል።

    የኔፓል ፖሊስ አገሪቱን ከቲቤት ጋር በሚያዋስናት ድንበር አካባቢ የሚገኙ መንደሮችን ጠራርጎ በወሰደው ድንገተኛው የጎርፍ አደጋ የሞቱት ሰዎች ቁጥር 332 መድረሱን ይፋ አደረገ።

    ፖሊስ አብዛኞቹ ሟቾች የውጭ አገር ዜጎች መሆናቸውን አስታውቆ ከ900 በላይ ሰዎች የደረሱበት አለመታወቁን ገልጿል።

    በቲቤት ሦስት ሰዎች መሞታቸው እና ቢያንስ 558 ሰዎች የደረሱበት አለመታወቁን የቻይና ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።

    ነገር ግን ያሉበት ያልታወቁ ሰዎች ቁጥር የኔፓል ፖሊስ ይፋ ያደረገው መረጃ ውስጥ ስለመካተቱ የታወቀ ነገር የለም።

    ከኔፓል የወጡ የተረጋገጡ ቪዲዮዎች፣ በጎርፉ ድልድይ ተሰብሮ ሲወሰድ፣ ብዙ ፎቆች ያሉት ህንጻ ሲወድቅ እና በርካታ ህንጻዎች ያሉት ከተማ ሲወድም አሳይተዋል።

    ከዚህ ቀደም በአካባቢው ተራራ በመውጣት ልምድ ያለው ግለሰብ ለቢቢሲ የደረሰው አደጋ ምን ያህል “አውዳሚ” እና “ድንገተኛ” እንደነበር ማመን እንዳልቻለ ገልጿል።

    ከቴክሳስ ቤተሰቦቻቸው ወደ አካባቢው የተጓዙ ሁለት እህትማማቾች “እንወዳቸዋለን ወደ ቤታቸው በሰላም ይመለሱ” ሲሉ መልክማ ምኞታቸውን ገልጸዋል።

    ድንገተኛ የጎርፍ አደጋው በምን ምክንያት እንደተከሰተ የሚያስረዱ መረጃዎች ቀስ በቀስ መወጣት ጀምሯል።

    ባለሙያዎች ድንገተኛ የጎረፍ አደጋው የተከሰተው “የግግር በረዶ መናድ እና የፍርስራሾች መከተል” ነው ሲሉ ይፋ አድርገዋል።

    ባለሙያዎቹ በወንዞች ውስጥ በተከማቹ ፍርስራሾች የተነሳ “ሁለተኛ እና ሦስተኛ ዙር” የጎርፍ አደጋ ሊኖር ይችላል ሲሉ ፍርሃታቸውን ገልጸዋል።

    የአሜሪካ ጂኦሎጂካል ሰርቬይ በኔፓል እና ቲቤት ድንበር አቅራቢያ ድንገተኛ ጎርፍ የተከሰተው “በግግር በረዶ ናዳ” የተነሳ መሆኑን ገልጿል።

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካ ጂኦሎጂካል ሰርቬይ በኔፓል እና ቲቤት ድንበር አቅራቢያ ድንገተኛ ጎርፍ የተከሰተው “በግግር በረዶ ናዳ” የተነሳ መሆኑን ገልጿል።
  18. ሁለት የጀርመን አየር ማረፊያ ሠራተኞች “በአውሮፕላን በመጣ ወባ” ምክንያት ሕይወታቸው አለፈ

    የጀርመን አየር ማረፊያ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በጀርመን ፍራንክፈርት አየር ማረፊያ በተከሰተ ያልተለመደ የወባ ወረርሽኝ ስድስት ሠራተኞች ተይዘው፣ ሁለቱ ሕይወታቸው አለፈ።

    በሽታውን ያስተላለፉት የወባ ትንኞች በርካታ ተጓዦችን በማስተናገድ በጀርመን ቀዳሚ ወደሆነው አየር ማረፊያ የገቡት በአውሮፕላን ነው ተብሎ እንደሚታመን የጀርመን የሕብረተሰብ ጤና ባለሥልጣናት ተናግረዋል። ሐምሌ ለመጀመሪያ ጊዜ በታወቀው በዚህ ክስተት ምክንያት ወረረሽኝ ተፈጥሯል።

    አየር ማረፊያውን የሚያስተዳድረው ‘ፍራፖርት’ ቃል አቀባይ ለቢቢሲ እንደተናገሩት፣ በበሽታው ምክንያት አንድ ሠራተኛ ሞቷል። የአገሪቱ የሕብረተሰብ ጤና ባለሥልጣናት ደግሞ ረቡዕ ዕለት በበሽታው የተያዙ ሁለት ግለሰቦች ሕይወት ማለፉን አስታውቀዋል።

    አየር ማረፊያ ውስጥ መረብ የተጠመደ ሲሆን የተያዙት ወባ ትንኞችን ዝርያ እና መነሻ ለማወቅ የላብራቶሪ ምርመራ ይደረጋል ተብሏል።

    የፍራፖርት ቃል አቀባይ “ለሁሉም ሠራተኞች አጠቃላይ መረጃ ሰጥተናል፤ የትኛውንም ምልክቶች ከተመለከቱ ሐኪም እንዲያማክሩ እናበረታታቸዋለን” ሲሉ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    የፍራንክፈርት የጤና ቢሮ ወረርሽኙን እየመረመረው መሆኑ ተገልጿል።

    በአየር መንገዱ የተለያዩ የሥራ መስኮች እና ቦታዎች የሚሰሩ ሠራተኞች በበሽታው መያዛቸውን ቢቢሲ ተገንዝቧል።

    ባለሥልጣናት፣ ሠራተኞቹ በሽታው የያዛቸው በአንድ ትንኝ ይሁን በስድስት የተለያዩ የወባ ትንኞች ለመለየት የደም ናሙና ወስደው እየመረመሩ ነው።

    ረቡዕ ዕለት የፍራንክፈርት የሕብረሰተብ ጤና ባለሥልጣናት ለመገናኛ ብዙኃን በላኩት ደብዳቤ፣ በበሽታው ከተያዙት ሰዎች ውስጥ ሁለቱ መሞታቸውን ገልጸዋል። ክስተቱ በከተማዋ ነዋሪዎች ላይ የሚፈጥረው ስጋት “እጅግ አነስተኛ” መሆኑንም አመልክተዋል።

  19. ትራምፕ የኢራኑ ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻሜኒ ሞተዋል መባሉን እንደማያምኑ ተናገሩ

    ፕሬዝዳንት ትርምፕ እና የኢራኑ መሪ ሞጅታባ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ፕሬዝዳንት ትርምፕ እና የኢራኑ መሪ ሞጅታባ

    የአባታቸውን መገደል ተከትሎ የኢራን ጠቅላይ መሪ የሆኑት ሞጅታባ ኻሜኒ ያሉበት ሁኔታ አለመታወቁን ተከትሎ ሞተዋል እየተባለ የሚናፈሰውን ወሬ እንደማያምኑ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ተናገሩ።

    በቀጥታ በተደረገ የስልክ ቃለ ምልልስ ላይ ሞጅታባ “ሞቷል ብዬ አላስብም” ያሉት ፕሬዝዳንት ትራምፕ፣ ኢራኑ መሪ ከባድ ጉዳት እንደደረሰባቸው ግን ጠቁመዋል።

    “የሰውነቱ ግራ ክፍል፣ እጁ፣ እግሩ ሁሉ በጣም ከባድ ጉዳት ደርሶበታል። ግን ሞቷል ብዬ አላስብም” ብለዋል።

    ሞጅታባ ሞተው ከሆነ ኢራን ባለሥልጣናት የሚያደርጉት ሁሌ በሕይወት እንዳሉ የማስመሰል ነው፤ ነገር ግን በወሳኝ ጉዳዮች ላይ እንደሚያማክሯቸው እና ውሳኔያቸውን እንደሚቀበሉ ትራምፕ ጠቅሰዋል።

    ጨምረውም ከአሜሪካ ጋር ድርድር ሲያደርጉ የነበሩት የቴህራን ተደራዳሪዎች ተቀባይነት የሌላቸው መሆናቸውን በመግለጽ፣ ኢራን ውስጥ ማንኛውም ነገር የሚከሰትበት ዕድል እንዳለ ተናግረዋል።

    ከኢራን ጋር የሚደረገውን ጦርነት ስለማሸነፍ ያላቸውን ተስፋ በተመለከተ የተጠየቁት ትራምፕ፣ “ያለን የገንዘብ አቅም ከፍተኛ ነው፤ እናም ይህ ወደ ታላቅ ድል ይመራናል” ብለዋል።

    የአሜሪካ ገንዘብ ሚኒስቴር በዚህ ሳምንት በኢራን ላይ ያለውን ማዕቀብ ለማጠናከር አዲስ ዘመቻ መጀመሩን አስታውቋል።

    ኢራን ላይ መጠነ ሰፊ የምጣኔ ሀብት ጫና በመፍጠር መንግሥቱን ለመጣል የተለያዩ እርምጃዎች እንደሚወሰዱ ተነግሯል።

    አሜሪካ በወታደራዊ እርምጃ ይልቅ፣ ኢራን ላይ የምጣኔ ሀብት ዘመቻን ወደማጠናከር አዘንብላለች። ከቴህራን ጋር የንግድ ግንኙነት ያላቸው አገራት ትስስራቸውን ለማቋረጥ ፈቃደኛ ካልሆኑ ኢኮኖሚያዊ ቅጣቶች እንደሚጠብቋቸው አስጠንቅቃለች።

  20. አሜሪካ ተጨማሪ የጦር መርከብ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ልታሰማራ ነው

    ዩኤስኤስ ቴዎድሮስ ሩዝቬልት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, ዩኤስኤስ ቴዎድሮስ ሩዝቬልት

    ከኢራን ጋር ፍጥጫ ውስጥ የምትገኘው አሜሪካ አምስት ሺህ የሠራዊት አባላትን የሚይዘውን ግዙፉን የባሕር ኃይል አውሮፕላን ተሸካሚ መርከብ ዩኤስኤስ ቴዎዶር ሩዝቬልትን በተጨማሪነት ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ልታሰማራ ነው።

    የአሜሪካ ባለሥልጣናት እንዳስታወቁት ግዙፉ የጦር መርከብ በሚቀጥሉት ሳምንታት ወደ አካባቢው የሚያቀና ሲሆን፣ ቢያንስ ለሰባት ወራት መካከለኛው ምሥራቅ ውስጥ ተሰማርቶ ይቆያል።

    ለወራት በዘለቀው ከኢራን ጋር በሚካሄደው ጦርነት ጫና ውስጥ የገባው እና ዓለም አቀፍ ተልዕኮ ያለበት የአሜሪካ ባሕር ኃይል በፋርስ ባሕረ ሰላጤ ተሰማርተው ከነበሩ አባላቱ ጋር በተያያዘ ባለፉት ሳምንታት ትችቶች ሲቀርቡበት ነበር።

    በመካከለኛው ምሥራቅ ከተቀመጠለት የጊዜ ገደብ በላይ 250 ቀናት የቆዩት የዩኤስኤስ አብረሃም ሊንከን የጦር መርከብ አባላት ጉዳይ በአሜሪካ ባለሥልጣናት ላይ ወቀሳ አስከትሏል።

    የተራዘመው የባሕር ኃይል አባላቱ ስምሪት በአእምሮ ጤናቸው ላይ ችግር መፍጠሩ እንዲሁም የአቅርቦት እጥረት አጋጥሞት እንደነበር ተገልጿል። በዚህ የተነሳም እራስን የማጥፋት ሙከራ እንደነበር ተዘግቧል።

    ይህንንም ተከትሎ ዩኤስኤስ ጆርጅ ዋሽንግተን የተባለ የጦር መርከብ የሊንከንን ቦታ ተክቶ በባሕረ ሰላጤው ተሰማርቷል።