ማራዶና “በእግዜር እጅ” ግብ ያስቆጠረባት ኳስ ከ3 ሚሊዮን ዶላር በላይ ተሸጠች

የፎቶው ባለመብት, PA Media
ዲያጎ ማራዶና እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር በ1986ቱ የዓለም ዋንጫ በእጁ ግብ ያስቆጠረባት ኳስ በጨረታ 3.3 ሚሊዮን ዶላር ተሸጠች።
ከጨዋታው በኋላ ማራዶና ለጋዜጠኞች “በጥቂቱ በማራዶና ጭንቅላት እና በጥቂቱ በእግዜር እጅ” ግብ ማስቆጠሩን ተናግሮ ነበር።
ማራዶና በዚያው የዓለም ዋንጫ ላይ ከበረኛው ውጪ አምስት የእንግሊዝ ተጫዋቾችን አልፎ “የክፍለ ዘመኑ ግብ” የተባለለትን ጎል አስቆጥሯል።
ቅዳሜ ዕለት በዩናይትድ ስቴትስ ለጨረታ የቀረበው ኳስ 10 ሚሊዮን ዶላር ያወጣል ተብሎ ቢጠበቅም በ3.3 ሚሊዮን ዶላር ተሸጧል።
አጫራቹ ማይክ ፕሮቬንዛሌ ከጨረታው በፊት ለሮይተርስ የዜና ወኪል “ይህ ልዩ የሆነ ዕቃ ነው። እስካሁን ከተገኙት እጅግ አስፈላጊ የእግር ኳስ ዕቃዎች አንዱ ሊሆን ይችላል” ብለዋል።
የ1986ቱን የዓለም ዋንጫ የዳኙት ቱኒዚያዊው አሊ ቢን ናስር ኳሱን ከጨዋታው በኋላ በመውሰድ ከሦስት አስርት ዓመታት በላይ ጠብቀው አቆይተውታል።
እአአ በ2023 በጨዋታው ላይ ጥቅም ላይ የዋለ ብቸኛው ኳስ መሆኑን በፊርማቸው ያረጋገጡ ሲሆን ገለልተኛ አጣሪዎችም እውነት መሆኑን መስክረዋል።
ቢን ናስር እአአ በ2022 ኳሱን 2.37 ሚሊዮን ዶላር ሸጠውታል።
እአአ በ2023 አዲሱ የኳሱ ባለቤት ለጨረታ ቢያቀርበውም የታሰበለትን ያህል ዋጋ ባለማውጣቱ ሳይሸጥ ቀርቷል።
በዚሁ ጨዋታ ላይ ማራዶና የለበሰው ቲ ሸርት እአአ በ2022 በ7.1 ሚሊዮን ፓውንድ ተሸጧል።



