ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከሳዑዲ ጋር የተደረሰውን የኒውክሌር ስምምነት ለምክር ቤት አቀረቡ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ከሳዑዲ አረቢያ ጋር የተደረሰውን የሰላማዊ ኒውክሌር ትብብር ስምምነት እንዲገመገም ለአሜሪካ ኮንግረስ አስተላለፈ።
ለኮንግረስ መቅረቡ፣ አገሪቱ ከሳዑዲ ጋር የተፈራረመችው የኒውክሌር ስምምነት በአሜሪካ የአውቶሚክ ኢነርጂ ሕግ መሠረት የሚገመገምበት ሂደት እንዲጀመር ያደርጋል።
በስምምነቱ መሠረት ሳዑዲ አረቢያ ለሰላማዊ አገልግሎት ለሚውለው የኒውክሌር ፕሮግራሟ የሚውል ዩራኒየም እንድታበለጽግ ይፈቀድላታል።
ሆኖም አንድ የአሜሪካ አስተዳደር ባለሥልጣን የምክር ቤቱን ዜናዎች ለሚከታተለው ‘ዘ ሂል’ ለተባለ የመገናኛ ብዙኃን እንደተናገሩት፣ ዶናልድ ትራምፕ ስምምነቱን ከፈረሙ በኋላ ያካተቱት ቅድመ ሁኔታ አሁንም በሥራ ላይ ይገኛል።
ባለሥልጣኑ እንዳሉት፣ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት አቋም አሁንም አልተቀየረም። ስምምነቱ ተግባራዊ የሚሆነው ሳዑዲ አረቢያ የአብርሃም ስምምነትን ተቀብላ ከእስራኤል ጋር ግንኙነቷን በማሻሻል መደበኛ ሁኔታ ላይ ካደረሰች በኋላ ብቻ መሆኑን ገልጸል።
ይህ አሜሪካ ከሳዑዲ ጋር የደረሰችው ስምምነት በመካከለኛው ምሥራቅ የኒውክሌር ፉክክር እንዲፋጠን ያደርጋል የሚል ስጋትን ፈጥሯል።
በተለይም አሜሪካ ባለፈው አንድ ዓመት ውስጥ በኢራን ላይ እየወሰደች ያለው ወታደራዊ እርምጃ ዋና ዓላማ “ኢራን የኒውክሌር መሣሪያ እንዳትታጠቅ ማስቆም እና በቀጣናው የኒውክሌር ፉክክርን መከላከል” መሆኑን ስትገልጽ መቆየቷ፣ ይህ ጉዳይ ይበልጥ ትኩረት እንዲስብ አድርጓል።
በዓለም ላይ ዋነኛ ነዳጅ አምራች ከሆኑ አገራት መካከል አንዷ የሆነችው ሳዑዲ አረቢያ፣ የተለያዩ መስኮች በማዘመን ከነዳጅ ጥገኝነት ነጻ ለመሆን በምታደርገው ጥረት የኒውክሌር ኃይል ማመንጫን ለመገንባት ጥረት እያደረገች ነው።



















