ቀጥታ, ኢራን የሆርሙዝን የባህር ወሽመጥ ዳግም ለመክፈት ቅድመ ሁኔታዎችን አስቀመጠች

ኢራን ላለፉት ስድስት ወራት ከአሜሪካ ጋር እያdረገችው ባለው ጦርነት ምክንያት ዘግታው የቆየችውን የሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ ዳግም ለመክፈት ቅድመ ሁኔታዎችን አስቀመጠች። ወሳኙን የባሕር መተላለፊያ ለመክፈት በመካከለኛው ምሥራቅ የሚደረጉ ጦርነቶችን እንዲቆሙ ማድረግ ከቅድመ ሁኔታዎቿ መካከል አንዱ መሆኑን ገልጻለች።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. በኔፓል የጎርፍ አደጋ የሟቾች ቁጥር 579 ሲደርስ፤ 2,000 የሚጠጉ ሰዎች የደረሱበት አልታወቀም

    ከትናንት በስቲያ በኔፓል በተከሰተው ድንገተኛ የጎርፍ አደጋ የሞቱ ሰዎች ቁጥር 579 መድረሱ ሲገለጽ፤ በሺዎች የሚቆጠሩ የደረሱበት አልታወቀም።

    የኔፓል የአደጋ ጊዜ ኤጀንሲ እንደገለጸው ከጠፉት ሰዎች መካከል ቢያንስ 517ቱ የውጭ ዜጎች ናቸው።

    ከኔፓል ጋር በምትዋሰነው የቻይናዋ ራስ ገዝ አስተዳደር ቲቤትም በአደጋው አምስት ሰዎች የሞቱ ሲሆን ከ550 በላይ የሚሆኑ መጥፋታቸውን የቻይና የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    ሁኔታዎች በፍጥነት የሚለዋወጡ በመሆኑ የተለያዩ ባለሥልጣናት የሚገልጹት ቁጥር የተለያየ ቢሆንም የሟቾች ቁጥር እየጨመረ ነው።

    አደጋው ከተከሰተ ከሁለት ቀናት በኋላም የነፍስ አድን ጥረቱ እንደቀጠለ ነው።

    የጠፉ ሰዎችን በተመለከተ የሚወጡ መረጃዎችን ወዳጅ ዘመዶቻቸው በጭንቀት እየጠበቁ ይገኛሉ።

    በቻይና እና ኔፓል ድንበር ላይ የተፈጠረው መጠኑ እየጨመረ ያለ ሐይቅ ፈንድቶ ሌላ ጎርፍ ሊያስከትል ይችላል በሚልም ተሰግቷል።

    በቲቤት የተሰማሩ የቻይና የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች፣ የሐይቁ ዳርቻዎች ተንዶ ድጋሚ የከፋ ጎርፍ ሊከሰት ይችል እንደሆነ ትናንት ጥናት ሲያደርጉ ውለዋል።

    በተፈጠረው ስጋት ምክንያትም በቲቤት የተሰማሩ የአደጋ ጊዜ ሰራተኞች ሥራቸውን እንዲያቋርጡ ተደርጓል።

    አስከፊው ድንገተኛ የጎርፍ አደጋ የተከሰተው ረቡዕ ዕለት በቲቤት በኩል ያለ የበረዶ ግግር መናዱን ተከትሎ ነው።

    አደጋው የተከሰተበት የኔፓል-ቲቤት ድንበር በየዓመቱ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ጎብኚዎችን ያስተናግዳል።

  2. በሱዳን መዲና ኻርቱም ለሁለት ዓመታት ተጥሎ የቆየው የሰዓት እላፊ ተነሳ

    በሱዳን ጦር የሚመራው መንግሥት ከሁለት ዓመት በፊት በኻርቱም ላይ ተጥሎ የነበረውን የሰዓት እላፊ እና የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማንሳቱን የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    ባለሥልጣናቱ ይህንን እርምጃ የወሰዱት ጦሩ በተፈላሚው ፈጥኖ ደራሽ ኃይል (አርኤስኤፍ) ተይዛ የነበረችውን ከተማዋን መልሶ ከተቆጣጠረ ከ18 ወራት በኋላ ነው።

    ሆኖም ግጭቱ በግዛቷ ደቡባዊ እና ምዕራባዊ አካባቢዎችም እንደቀጠለ ሲሆን ጦርነቱ ወደ ሱዳን ድንበሮች እየተዛመተ መሆኑን የሚያሳዩ መረጃዎች አሉ።

    ከአራት ዓመት በፊት በሥልጣን ሽኩቻ ሰበብ በአገሪቱ በተቀሰቀሰው ጦርነት አምስት ሚሊዮን የሚጠጉ የኻርቱም ነዋሪዎች ለመፈናቀል ተዳርገው ነበር።

    ከመጋቢት ወር ጀምሮ ግን ግጭቱ በመቆሙ ተፈናቅለው ከነበሩት ውስጥ ከ2 ሚሊዮን በላይ ነዋሪዎች መመለሳቸውን ዓለም አቀፉ የስደተኞች ድርጅት (አይኦኤም) ገልጿል።

    አሁን ላይ የሰዓት እላፊው እንዲነሳ መደረጉም በከተማ ያለውን እንቅስቃሴ ወደ መደበኛ ሁኔታ ለመመለስ ያለመ ነው።

    መንግሥት በከተማዋ ያለውን ዋና አየር ማረፊያ ለተወሰኑ በረራዎች ክፍት ያደረገ ሲሆን የንግድ ተቋማት እና ኤምባሲዎችም እንዲመለሱ እያበረታታ ነው።

    ሆኖም ነዋሪዎች አሁንም ኑሯቸውን እንደገና ለማቋቋም ተቸግረዋል።

    አብዛኞቹ ነዋሪዎች ወደ ከተማዋ ሲመለሱ በርካታ ሕንፃዎች ወድመው እና ተዘርፈው ነው ያገኙት። ከዚህም በተጨማሪ አርኤስኤፍ ቢያስተባብልም በኤሌክትሪክ መሰረተ ልማት ላይ ፈፀመው በተባለው የድሮን ጥቃት የኃይል መቋረጥ አጋጥሟቸዋል።

    አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ቢነሳም ባለሥልጣናቱ የአርኤስኤፍ ታጣቂዎች ሰርገው ሊገቡ ይችላሉ የሚልም ስጋት አላቸው። በመሆኑም በግዛቷ የደኅንነት ፍተሻ መካሄዱ የሚቀጥል እንደሆነ እና በምሽት የሚጓዙ መንገደኞችም መታወቂያ መያዝ እንደሚኖርባቸው የሱዳን የዜና ወኪል ዘግቧል።

  3. የዓለማችን በዕድሜ ትንሹ ባህላዊ ንጉሥ በ34 ዓመታቸው አረፉ

    በዓለም በዕድሜ ትንሹ ንጉሥ የነበሩት የኡጋንዳ ባህላዊ መሪ በ34 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት መለየታቸውን ጠቅላይ ሚኒስትራቸው አስታወቁ።

    ኦዮ ኒይምባ ካባማ ኢጉሩ ሩኪዲ አራተኛ የአባታቸውን ሞት ተከትሎ ነበር በአውሮፓውያኑ 1995 በሦስት ዓመታቸው የቶሮ ንጉሥ ሆነው የተሰየሙት።

    ይህም የዓለማችን በዕድሜ ትንሹ ንጉሥ እንዲሆኑ ያደረጋቸው ሲሆን፣ 18 ዓመት እስከሚሞላቸው ድረስ እናታቸው በተካተቱበት እና ሦስት አባላት ባሉት ምክር ቤት ንጉሣዊ ሥርዓቱ ሲመራ ነበር።

    የቶሮ ግዛት የንጉሡን ሞት መንስዔ አልገለጸም። ሆኖም የአገሪቷ መገናኛ ብዙኃን አንድ የኡጋንዳን መንግሥት ሚኒስትር ጠቅሶ እንደዘገበው ንጉሡ በጠና ታመው በአሜሪካ ህክምና ሲደረግላቸው ነበር።

    ቶሮ በምዕራብ ኡጋንዳ የሚገኝ እና ረዥም ታሪክ ባለው ጥንታዊ የባንቱ ባህላዊ መንግሥት የሚመራ ግዛት ነው።

    ኡጋንዳ በሕዝብ በተመረጠ ፕሬዝዳንት ብትመራም፣ ፖለቲካዊ ሥልጣን ባይኖራቸውም ተፅእኖ መፍጠር የሚችሉ በርካታ ባህላዊ መሪዎች አሏት።

    በዓለም የድንቃ ድንቅ መዝገብ ውስጥ የዓለማችን በዕድሜ ትንሹ ባህላዊ ንጉሥ በሚል ስማቸው የሰፈረው ኦዮ፣ ከ2 ሚሊዮን በላይ የሚገመት የቶሮን ሕዝብ ሲመሩ ነበር። ኦዮ በ19ኛው ክፍለ ዘመን የተመሠረተው ንጉሣዊ ሥርዓት 13ኛው ንጉሥ ነበሩ።

    ሕልፈታቸውን ያስታወቁት የቶሮ ጠቅላይ ሚኒስትር ካልቪን አርምስትሮንግ ሪዎማይር፣ የንጉሡ ህልፈት ለንጉሣውያን ቤተሰቦች እና ለቶሮ ሕዝብ “ትልቅ እጦት” ነው ብለዋል።

    “በዚህ ከባድ ወቅት የቶሮ ሕዝብ በአንድነት፣ በመረጋጋት እና በፀሎት እንዲቀጥል ጥሪ አቀርባለሁ” ሲሉም ንጉሣ በሰላም እንዲያርፉ ተመኝተዋል።

    የቶሮ ግዛት ንጉሡን ለመምረጥ በዘር የሚተላለፍ ንጉሣዊ ሥርዓትን ይከተላል። ኦዮ በይፋ ስላላገቡ ዘውዱን ማን ይረከባል የሚለው አይታወቅም። ሆኖም ጠቅላይ ሚኒስትራቸው “የዘውዱ ሽግግር የተረጋገጠ ነው” ብለዋል።

    ግርማዊነታቸው “ወራሽ የሆነ ልዑል ትተው ነው ያረፉት። ማንነቱ በተገቢው ጊዜ፣ በቶሮ መንግሥት ወግ እና ባህል መሠረት ይገለጻል” ሲሉ አስረድተዋል።

    ኦዮ በሕዝብ ዘንድ የተወደዱ እና በወጣቶች አቅም ማጎልበት፣ በትምህርት እና በአካባቢ ጥበቃ እንዲሁም በኤችአይቪ/ኤድስ ግንዛቤ ማስጨበጥ ሥራዎችን ሲያበረታቱ እንደነበር ዴይሊ ሞኒተር ጋዜጣ ዘግቧል።

  4. ሁሉም አገራት የአሜሪካን ማዕቀብ ከመተግበር እንዲቆጠቡ ኢራን አሳሰበች

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር “የኢኮኖሚ ሽብር” ሲል የገለፀውን የአሜሪካን ማዕቀብ በማውገዝ፣ ሁሉም አገራት እና መንግሥታት ማዕቀቡን ተግባራዊ ከማድረግ እንዲቆጠቡ አሳሰበ።

    ሚኒስቴሩ በመግለጫው፣ አሜሪካ በኢራን ላይ የጣለችውን የአንድ ወገን ማዕቀብ በመተግበር መሳተፍ የአንድን አገር "ሕገ ወጥ ፈቃድ" በሉዓላዊ አገር ላይ በመጣል ሕጋዊ የሆነውን "የኢኮኖሚ እና የንግድ ግንኙነትን ለማወክ ከመተባበር" ጋር ተመሳሳይ ነው ብሏል።

    ይህም የተባበሩት መንግሥታት ቻርተር የሚያረጋግጠው ‘የሉዓላዊ አገራት እኩልነት’ መርኅ ጥሰት ላይ መሳተፍ እንደሆነ መግለጫው አስረድቷል።

    የአሜሪካ ማዕቀቦች "ሙሉ በሙሉ ሕገ ወጥ እና ኢ- ፍትሃዊ እንዲሁም የተባበሩት መንግሥታትን ቻርተር፣ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊነት ሕግን እና የሰብዓዊ መብቶችን" የሚጥስ እንደሆነም መግለጫው ጠቅሷል።

    በመሆኑም ሁሉም አገራት እና መንግሥታት ለእንደዚህ ዓይነት ማዕቀቦች ዕውቅና ከመስጠት እና ከማጽደቅ እንዲሁም ሕገ ወጥ እርምጃን ከመተግበር መቆጠብ እንዳለባቸው አሳስቧል።

    ሚኒስቴሩ ጨምሮም አሜሪካ ኢራንን በኢኮኖሚ ለማግለል የወጠነችው ዕቅድ “በውስጥ ጉዳዮች ጣልቃ መግባትን እና በአገራት መካከል የሚደረገውን ትብብር ማወክን” የሚከለክለውን የተባበሩት መንግሥታትን መርኅ የሚጥስ ነው ብሏል።

    ሚኒስቴሩ ይህን ያለው አሜሪካ ከኢራን ጋር የንግድ ግንኙነት ባላቸው ተቋማት፣ ባንኮች እና አገራት ላይ ጭምር ማዕቀቦችን በመጣል እንደምትቀጣ ካስታወቀች በኋላ ነው።

  5. ከአሜሪካ ጋር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትን መመለስ እንደሚቻል የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ገለፁ

    የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ከኳታሩ ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጋር ቴህራን ውስጥ ካደረጉት ንግግር በኋላ፣ ከአሜሪካ ጋር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትን ወደነበረበት መመለስ “የማይቻል አይደለም” ሲሉ ተናገሩ።

    አራግቺ ከኳታሩ ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሼኽ ሞሐመድ ቢን አብዱልራህማን ቢን ጃሲም አል ታኒ ጋር “ውጤታማ ውይይት” እንዳደረጉ በኤክስ ገጻቸው ላይ ተናግረዋል።

    “ዲፕሎማሲን ወደ ትክክለኛው መንገድ መመለስ የማይቻል አይደለም። ይህ የሚወሰነው አሜሪካ በአንድ ቀላል እውነታ ላይ በሚኖራት ግንዛቤ ነው፤ ጫና መፍጠር አይሰራም” ብለዋል።

    “አሜሪካ እምነትን መገንባት፣ በአክብሮት መናገር፣ መብቶቻችንን መቀበል እና የገባችውን ቃል መፈፀም አለባት” ሲሉ የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አክለዋል።

    በኢራን እና አሜሪካ መካከል ያለውን ውጥረት ለማርገብ ዶሃ እየሠራች ባለችበት ወቅት ነው ሼኽ ሞሐመድ ሐሙስ ዕለት በቴህራን ጉብኝት ያደረጉት።

    በጉብኝታቸውም ከኢራኑ ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን፣ ከአራግቺ፣ ከፓርላማ አፈጉባዔው ሞሐመድ ባገር ጋሊባፍ እና ከኢራን ጠቅላይ ብሔራዊ የደኅንነት ምክር ቤት ፀሐፊ ሞህሰን ረዛኢ ጋር ተነጋግረዋል።

    በአሜሪካ እና ኢራን መካከል የተጀመረውን ውይይት ማስቀጠል የሚቻልበትን ሁኔታ መፍጠር እንዲሁም በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ጊዜያዊ የጋራ የመርከብ መተላለፊያ መንገድ ማበጀት እና አካባቢውን ከፈንጂዎች እና ሌሎች መሣሪያዎች የማፅዳት ጥረቶች የተነጋገሩባቸው ጉዳዮች ናቸው።

    የአሜሪካ እና እስራኤልን ጥቃት ተከትሎ የካቲት ወር ላይ ጦርነቱ ከተቀሰቀሰ ወዲህ የኳታር የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በኢራን ጉብኝት ሲያደርጉ የአሁኑ የመጀመሪያቸው ነው።

  6. የሱዳን ጦር ከሁለት ዓመት በላይ በካርቱም ጥሎት የነበረውን የሰዓት እላፊ አነሳ

    የሱዳን ጦር ከሁለት ዓመት በላይ በካርቱም ላይ ጥሎት የነበረውን የሰዓት እላፊ ማንሳቱን የአገሪቱ ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን ዘገበ።

    የጦሩ ባለሥልጣናት የሰዓት እላፊውን ያነሱት ከተማዋን ከፈጥኖ ደራሽ ኃይሉ ካስለቀቁ ከ18 ወራት በኋላ ነው።

    በሱዳን እየተካሄደ ያለው የእርስ በእርስ ጦርነት ከካርቱም ውጭ ባሉ የአገሪቱ ከተሞች እንደቀጠለ ነው።

    የአገሪቱ ጦር ካርቱምን ከአማጺያኑ ካስለቀቀ በኋላ ከሁለት ሚሊዮን በላይ ሰዎች ወደካርቱም ተመልሰው መደበኛ ሕይወታቸውን ቀጥለዋል።

    ነገር ግን በጦርነት ምክንያት በርካታ መሠረተ ልማቶች በመውደማቸው በተደጋጋሚ የኤሌትሪክ መቆራረጥ እንደሚያጋጥማቸው ይነገራል።

    የፈጥኖ ደራሹ ኃይሎች ወደ ከተማዋ ሰርገው እንዳይገቡ ለመከላከል የጦሩ አባላት በየጊዜው የቅኝት ስራ እንደሚሰሩ የአገሪተ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    በምሽት የሚንቀሳቀሱ የከተማዋ ነዋሪዎችም ማንነታቸውን የሚገልጽ መታወቂያ ይዘው እንዲንቀሳቀሱ አሳስበዋል።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ ቻድ የሱዳን ጦር በድንበር አቅራቢያ በፈጸመው የአየር ድብደባ የአገሪቱ ጦር ላይ ጉዳት ማድረሱን ገልጻ ከስሳለች።

    የሱዳን ጦር የቻድ መንግሥት ክስን ውድቅ አድርጓል።

    የአሜሪካ መንግሥት የሱዳን ጦርነት ከአገሪቱ ድንበር ሊያልፍ ይችላል የሚል ስጋት እንዳለው ገልጿል።

  7. የአሜሪካ ጦር በአውሮፓ "ከፍተኛ የሚሳዔል መቃወሚያ እጥረት" እንደገጠመው ተዘገበ

    የአሜሪካ መከላከያ በኢራን እያካሄደ ካለው ጦርነት ጋር በተያያዘ በአውሮፓ ከፍተኛ የሆነ ዘመናዊ የሚሳዔል መቃወሚያዎች እጥረት እንደገጠመው የፈረንሳዩ የዜና ወኪል ዘገበ።

    አሶሼትድ ፕሬስ የአሜሪካ መከላከያ ባለሥልጣናትን እና የኔቶ ኃላፊዎችን ጠቅሶ እንደዘገበው ጦሩ “እጅግ ወሳኝ በሆነ ደረጃ” ላይ የሚገኝ ዘመናዊ የሚሳኤል መቃወሚያ እጥረት አጋጥሞታል።

    ይህ ሁኔታ የኔቶ አባል አገራት ከሩሲያ ሊሰነዘር ለሚችል ጥቃት ተጋላጭ የሚያደርግ በመሆኑ ስጋት መፈጠሩን ጨምረው አስረድተዋል።

    የአሜሪካ መከላከያ ባለሥልጣናት እጥረቱ በይበልጥ የተፈጠረው የሩሲያን ተምዘግዛጊ ባሌስቲክ ሚሳዔልን መትቶ መጣል በሚችለው ፓትሮይት ተብሎ በሚጠራው የሚሳዔል መቃወሚያ ላይ ነው ብለዋል።

    የኔቶ ኃላፊዎች በአሜሪካ ጦር እና በአውሮፓ በሚገኙ የኔቶ አባል አገራት ዘንድ የፓትሮይት ሚሳዔል እጥረት መኖሩን አረጋግጠዋል።

    ስማቸው እንዳይገለጽ የጠየቁ ኃላፊዎች በአውሮፓ የሚገኘው የአሜሪካ ጦር “በእርግጠኝነት” ከሩሲያ ሊተኮስ የሚችል ባሌስቲክን የሚያከሽፍበት ፓትሮይት ሚሳዔል እጥረት አለበት ብለዋል።

    ኃላፊዎቹ ከሩሲያ ለሚሰነዘር ማንኛውንም የባሌስቲክ ሚሳዔል ጥቃት ለመከላከል ያለው አቅም “በጣም ውስን” መሆኑን ጨምረው ገልጸዋል።

    ምንም እንኳን በኔቶ አባል አገራት ላይ ሩሲያ የባለስቲክ ሚሳዔል ጥቃት ትፈጽማለች ተብሎ ባይጠበቅም የሲአይኤ ዳይሬክተር ጆን ራትክሊፍ በዚህ ሳምንት ወደ ሞስኮ ተጉዘው ሩሲያ ጥቃት እንዳትፈጽም ማስጠንቀቃቸውን ዎል ስትሪት ጆርናል ዘግቧል።

    ሐሙስ ዕለት የሲአይኤ ኃላፊ መልዕክቱን ለፑቲን አድርሰው እንደሆን የተጠየቁት ትራምፕ “በዚህ ጉዳይ ላይ አስተያየት መስጠት አልፈልግም፤ ነገር ግን ጥቃት አይፈጽሙም” ሲሉ በደፈናው መልሰዋል።

  8. ትራምፕ አሜሪካንን ከመሩ ፕሬዝዳንቶች ሁሉ የተለየሁ ነኝ አሉ

    አነጋጋሪ ጉዳዮችን በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ በማጋራት የሚታወቁት ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ራሳቸውን እስካሁን አሜሪካንን ከመሩ ፕሬዝዳንቶች ሁሉ የላቁ መሆናቸውን ገለጹ።

    የመጀመሪያዎቹን ጨምሮ በፈታኝ ሁኔታ ውስጥ አሜሪካንን የመሩ የ34 ፕሬዝዳንቶችን ምሥል በመደርደር የተለያዩ ደረጃዎችን የሰጡት ትራምፕ ራሳቸውን “ከሁሉም ያላቁ” አድርገው በማቅረብ መነጋገሪያ ሆነዋል።

    በትሩዝ ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ በአሜሪካ ፕሬዝዳንቶች ታሪክ ራሳቸውን “የታላቆች ታላቅ” በሚለው ደረጃ ላይ በማስቀመጥ ሌሎቹን በተለያዩ ደረጃዎች “ደካማ” እስከሚል ፈርጀው ከእሳቸው ስር አስቀምጠዋቸዋል።

    በርካቶቹን የአሜሪካ ቀደምት ፕሬዝዳንቶች ከዝርዝሩ ውስጥ ባለማካተትም ቦታ ነፍገዋቸዋል። ምናልባትም ያልተካተቱት “ደካማ” ከተባሉት በታች ያሏቸውን ሊሆን ይችላል።

    ከአውሮፓውያኑ 1789 አሜሪካ 47 ፕሬዝዳንቶች ተፈራርቀው የመሯት ሲሆን፣ በትራምፕ የደረጃ ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት ግን 34ቱ ብቻ ናቸው። የዓለማችን የዲሞክራሲ ተምሳሌት የምትባለውን አገር እስካሁን ሴት ፕሬዝዳንት አልመራቻትም።

    ትራምፕ ከንጽጽር ያቀረቧቸውን ቀደምት ፕሬዝዳንቶች በስድስት ክፍል የመደቧቸው ሲሆን፣ ራሳቸውን “የታላላቆች ታላቅ”፣ እርሳቸውን የሚከተሉትን ደግሞ “ታላቅ”፣ ከዚያም “ለታላቅነት የቀረቡ”፣ “መካከለኛ”፣ “ከመካከለኛ በታች” እና ደካሞች” ብለዋቸዋል።

    “ደካማ” ከሚለው ምድብ ስር ያካተቷቸው ከእሳቸው የቀደሙትን ባራካ ኦባማ እና ጆ ባይደንን እንዲሁም ጂሚ ካርተር፣ ዋረን ሃርዲንግ እና ኡሊሴስ ግራንት ይገኙበታል።

  9. ኢራን የሆርሙዝን የባህር ወሽመጥ ዳግም ለመክፈት ቅድመ ሁኔታዎችን አስቀመጠች

    ኢራን ላለፉት ስድስት ወራት ከአሜሪካ ጋር እያdረገችው ባለው ጦርነት ምክንያት ዘግታው የቆየችውን የሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ ዳግም ለመክፈት ቅድመ ሁኔታዎችን አስቀመጠች።

    ወሳኙን የባሕር መተላለፊያ ለመክፈት በመካከለኛው ምሥራቅ የሚደረጉ ጦርነቶችን እንዲቆሙ ማድረግ ከቅድመ ሁኔታዎቿ መካከል አንዱ መሆኑን ገልጻለች።

    የኢራን ጠቅላይ ብሔራዊ የፀጥታ ምክር ቤት ፀሐፊ ሞህሰን ሬዛኢ ከሊባኖሱ አል ማናር ቴሌቪዥን ጋር በነበራቸው ቃለ ምልልስ በባሕረ ሰላጤው ላይ ከአሜሪካ ጋር የሚደረግ ማንኛውም መግባባት በሊባኖስ፣ በጋዛ እና በሶሪያ ውስጥ የሚደረጉ ጦርነቶችን እና ወታደራዊ እንቅስቃሴዎችን ማቆምን ያካትታል ብለዋል።

    በጋዛ ሰርጥ የተፈጠረው ግጭት መቆም እንዳለበት የተናገሩት የደኅንነት ኃላፊው፣ እስራኤል ከሊባኖስ እንድትወጣ እና በሶሪያ ላይ የሚሰነዘረውን ጥቃት እንድታቆም ጠይቀዋል።

    ሬዛኢ በሆርሙዝ ወሽመጥ አካባቢ ያለው ችግር በቀጣናው ውስጥ ካለው እጅግ ሰፊ ግጭት መካከል አንዱ ነው ካሉ በኋላ ኢራን በአሜሪካ ላይ እንደገና እምነት ልትጥል የምትችለው፣ የገባችውን ቃል በተግባር ለማሳየት ያላትን ቁርጠኝነት ካረጋገጠች በኋላ ብቻ ነው ብለዋል።

    ይሁን እንጂ ሁለቱ አገራት ዳግም ወደ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት መመለስ የሚቻሉ አይመስልም። ዎል ስትሪት ጆርናል ሐሙስ ዕለት እንደዘገበው የትራምፕ አስተዳደር በሰኔ ወር ከኢራን ጋር ወዳደረገው የመግባቢያ ስምምነት ለመመለስ ፍላጎት የለውም።

    ጋዜጣው ጉዳዩን በቅርበት የሚያውቁ ሰዎችን በመጥቀስ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በሰኔ ወር የስምምነት ማዕቀፍ ላይ ፍላጎት እንደሌላቸው እና በምትኩ አስተዳደራቸው ኢራንን በኢኮኖሚያዊ ጫና ለማንበርከክ አንደሚችል እምነት አላቸው።

    አሜሪካ ሰኞ ዕለት ከቴህራን ጋር የንግድ ግንኙነት ያላቸው አገራትን አስጠንቅቃ “ኢኮኖሚያዊ ጦርነት” መክፈቷን አስታውቃለች። ይህም የአሜሪካ ትኩረት ከወታደራዊ እርምጃ ወደ ኢኮኖሚያዊ ጫና መሸጋገሩን ያመለካተ ነው።

    ኢራን መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ እንዲያልፉ “ጊዜያዊ እና የተወሰነ” መስመር የፈቀደች ሲሆን፣ ወደፊት የሚኖር የመርከቦች ፍሰት ከዋሽንግተን ጋር በሚደረጉ ግንኙነቶች ላይ የተመሠረተ ይሆናል ሲሉ ሬዛኢ ተናግረዋል።

    በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ ኦማን እና ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ጊዜያዊ ደኅንነቱ የተጠበቀ የመርከቦች መተላለፊያ መስመር ለማቋቋም እንዲሁም ከዋና ዋና የነዳጅ ጫኝ መርከቦች መተላለፊያ መስመሮች ፈንጂዎችን ለማጽዳት ተወያይተዋል።

    ይሁን እንጂ፣ የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ አዛዥ አድሚራል ብራድ ኩፐር ሐሙስ ዕለት በአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) የኤክስ ገጽ ላይ በቪዲዮ ባስተላለፉት መልዕክት የአሜሪካ ወታደሮች ፈንጂዎችን ከባሕር ወሽመጥ ላይ ማጽዳታቸውን ተናግረዋል።

    ሴንትኮም ባለፉት በርካታ ወራት ውስጥ ወደ 1,500 የሚጠጉ የንግድ መርከቦችን እና 750 ሚሊዮን በርሜል ድፍድፍ ነዳጅ የጫኑ መርከቦች እንዲያልፉ ማገዙን ኩፐር ተናግረዋል።

    ኩፐር አክለውም “ዛሬ፣ ዓለም አቀፍ የመርከብ መስመሮች ክፍት ናቸው፣ እናም ፍጥነቱ እየጨመረ ነው” ብለዋል።

    ይሁን እንጂ፣ የቅርብ ጊዜ መረጃዎች እንደሚያሳዩት ማክሰኞ ዕለት ሆርሙዝን ያቋርጡት አምስት መርከቦች ብቻ ናቸው።

    ይህ ደግሞ በየካቲት ወር ጦርነቱ ከመጀመሩ በፊት በዚህ ወሳኝ በሆነው ወሽመጥ በኩል በየቀኑ ሲያቋርጡ ከነበሩት በግምት 130 መርከቦች በጣም ያነሰ ነው።

  10. ከኢራን ጋር ውጥረትን ለመቀነስ የሚያስችል ውይይት አድርገናል- ኳታር

    የኳታሩ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ከኢራን ባለሥልጣናት ጋር ውጥረትን መቀነስ የሚያስቸል ውይይት ማድረጋቸው ተገለጸ።

    የኳታር ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ ዛሬ በቴህራን የደረሰው የኳታር ልዑካን ቡድን ከአባስ አራጋቺ ጋር “ውጥረትን በሚቀንስ እና ለንግግር ምቹ ሁኔታን በሚፈጥሩ” ጉዳዮች ዙሪያ መወያየቱን አስታውቋል።

    ሚኒስቴሩ በመግለጫው ላይ ኢራን እና ኳታር ከሆርሙዝ ወሽመጥ ፈንጂዎችን ለማጽዳት የሚያስችል "የጋራ ፕሮጀክት" ተግባራዊ ለማድረግ በሚደረስ ስምምነት፣ እንዲሁም "ውጥረትን ለመቀነስ እና ለውይይት ተስማሚ ሁኔታዎችን ለመፍጠር ስለሚደረጉ ጥረቶች" ተወያይተዋል ብሏል።

    የኢራን የዜና ወኪል ታስኒም በበኩሉ የኢራን ፓርላማ አፈ-ጉባኤ እና ዋና ተደራዳሪ መሐመድ ባጌር ጋሊባፍ በቴህራን ከኳታር ጠቅላይ ሚኒስትር ጋር ባደረጉት ውይይት፣ በቀጣናው ያለውን ውጥረት የማርገብ አስፈላጊነት ላይ አጽንኦት ሰጥተው መናገራቸውን ዘግቧል።

    የኳታር የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ፣ የሁለቱ ሚኒስትሮች ውይይት "በቀጣናው የታዩ አዳዲስ ክስተቶችን፣ እንዲሁም ውጥረትን ለመቀነስ እና የክልሉን ደህንነትና መረጋጋት ለማጠናከር በሚረዱ ውይይቶች ላይ ምቹ ሁኔታዎችን ለመፍጠር የተደረጉ ጥረቶችን" እንደገመገመ ተገልጿል።

    የኳታር ጠቅላይ ሚኒስትር እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሞሃመድ ቢን አብዱልራህማን ቢን ጃሲም አል ታኒ፣ ወደ ቴህራን በመጓዝ፣ ከኢራን ፓርላማ አፈ-ጉባኤ እና ዋና ተደራዳሪ ሞሃመድ ባጌር ጋሊባፍ እንዲሁም ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ጋር ተገናኝተዋል።

    ከፍተኛ የኳታር ልዑካን ቡድን ወደ ቴህራን ያመራው የፓኪስታን የጦር ኃይሎች ዋና አዛዥ ጄኔራል አሲም ሙኒር በኢራን ከተገኙ ከሁለት ቀናት በኋላ ነው።

  11. በኔፓል ድንገተኛ የጎርፍ አደጋ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ከ300 በላይ መድረሱ ተገለጸ

    የኔፓል ፖሊስ አገሪቱን ከቲቤት ጋር በሚያዋስናት ድንበር አካባቢ የሚገኙ መንደሮችን ጠራርጎ በወሰደው ድንገተኛው የጎርፍ አደጋ የሞቱት ሰዎች ቁጥር 332 መድረሱን ይፋ አደረገ።

    ፖሊስ አብዛኞቹ ሟቾች የውጭ አገር ዜጎች መሆናቸውን አስታውቆ ከ900 በላይ ሰዎች የደረሱበት አለመታወቁን ገልጿል።

    በቲቤት ሦስት ሰዎች መሞታቸው እና ቢያንስ 558 ሰዎች የደረሱበት አለመታወቁን የቻይና ብሔራዊ መገናኛ ብዙኃን ዘግቧል።

    ነገር ግን ያሉበት ያልታወቁ ሰዎች ቁጥር የኔፓል ፖሊስ ይፋ ያደረገው መረጃ ውስጥ ስለመካተቱ የታወቀ ነገር የለም።

    ከኔፓል የወጡ የተረጋገጡ ቪዲዮዎች፣ በጎርፉ ድልድይ ተሰብሮ ሲወሰድ፣ ብዙ ፎቆች ያሉት ህንጻ ሲወድቅ እና በርካታ ህንጻዎች ያሉት ከተማ ሲወድም አሳይተዋል።

    ከዚህ ቀደም በአካባቢው ተራራ በመውጣት ልምድ ያለው ግለሰብ ለቢቢሲ የደረሰው አደጋ ምን ያህል “አውዳሚ” እና “ድንገተኛ” እንደነበር ማመን እንዳልቻለ ገልጿል።

    ከቴክሳስ ቤተሰቦቻቸው ወደ አካባቢው የተጓዙ ሁለት እህትማማቾች “እንወዳቸዋለን ወደ ቤታቸው በሰላም ይመለሱ” ሲሉ መልክማ ምኞታቸውን ገልጸዋል።

    ድንገተኛ የጎርፍ አደጋው በምን ምክንያት እንደተከሰተ የሚያስረዱ መረጃዎች ቀስ በቀስ መወጣት ጀምሯል።

    ባለሙያዎች ድንገተኛ የጎረፍ አደጋው የተከሰተው “የግግር በረዶ መናድ እና የፍርስራሾች መከተል” ነው ሲሉ ይፋ አድርገዋል።

    ባለሙያዎቹ በወንዞች ውስጥ በተከማቹ ፍርስራሾች የተነሳ “ሁለተኛ እና ሦስተኛ ዙር” የጎርፍ አደጋ ሊኖር ይችላል ሲሉ ፍርሃታቸውን ገልጸዋል።

  12. ሁለት የጀርመን አየር ማረፊያ ሠራተኞች “በአውሮፕላን በመጣ ወባ” ምክንያት ሕይወታቸው አለፈ

    በጀርመን ፍራንክፈርት አየር ማረፊያ በተከሰተ ያልተለመደ የወባ ወረርሽኝ ስድስት ሠራተኞች ተይዘው፣ ሁለቱ ሕይወታቸው አለፈ።

    በሽታውን ያስተላለፉት የወባ ትንኞች በርካታ ተጓዦችን በማስተናገድ በጀርመን ቀዳሚ ወደሆነው አየር ማረፊያ የገቡት በአውሮፕላን ነው ተብሎ እንደሚታመን የጀርመን የሕብረተሰብ ጤና ባለሥልጣናት ተናግረዋል። ሐምሌ ለመጀመሪያ ጊዜ በታወቀው በዚህ ክስተት ምክንያት ወረረሽኝ ተፈጥሯል።

    አየር ማረፊያውን የሚያስተዳድረው ‘ፍራፖርት’ ቃል አቀባይ ለቢቢሲ እንደተናገሩት፣ በበሽታው ምክንያት አንድ ሠራተኛ ሞቷል። የአገሪቱ የሕብረተሰብ ጤና ባለሥልጣናት ደግሞ ረቡዕ ዕለት በበሽታው የተያዙ ሁለት ግለሰቦች ሕይወት ማለፉን አስታውቀዋል።

    አየር ማረፊያ ውስጥ መረብ የተጠመደ ሲሆን የተያዙት ወባ ትንኞችን ዝርያ እና መነሻ ለማወቅ የላብራቶሪ ምርመራ ይደረጋል ተብሏል።

    የፍራፖርት ቃል አቀባይ “ለሁሉም ሠራተኞች አጠቃላይ መረጃ ሰጥተናል፤ የትኛውንም ምልክቶች ከተመለከቱ ሐኪም እንዲያማክሩ እናበረታታቸዋለን” ሲሉ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    የፍራንክፈርት የጤና ቢሮ ወረርሽኙን እየመረመረው መሆኑ ተገልጿል።

    በአየር መንገዱ የተለያዩ የሥራ መስኮች እና ቦታዎች የሚሰሩ ሠራተኞች በበሽታው መያዛቸውን ቢቢሲ ተገንዝቧል።

    ባለሥልጣናት፣ ሠራተኞቹ በሽታው የያዛቸው በአንድ ትንኝ ይሁን በስድስት የተለያዩ የወባ ትንኞች ለመለየት የደም ናሙና ወስደው እየመረመሩ ነው።

    ረቡዕ ዕለት የፍራንክፈርት የሕብረሰተብ ጤና ባለሥልጣናት ለመገናኛ ብዙኃን በላኩት ደብዳቤ፣ በበሽታው ከተያዙት ሰዎች ውስጥ ሁለቱ መሞታቸውን ገልጸዋል። ክስተቱ በከተማዋ ነዋሪዎች ላይ የሚፈጥረው ስጋት “እጅግ አነስተኛ” መሆኑንም አመልክተዋል።

  13. ትራምፕ የኢራኑ ጠቅላይ መሪ ሞጅታባ ኻሜኒ ሞተዋል መባሉን እንደማያምኑ ተናገሩ

    የአባታቸውን መገደል ተከትሎ የኢራን ጠቅላይ መሪ የሆኑት ሞጅታባ ኻሜኒ ያሉበት ሁኔታ አለመታወቁን ተከትሎ ሞተዋል እየተባለ የሚናፈሰውን ወሬ እንደማያምኑ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ተናገሩ።

    በቀጥታ በተደረገ የስልክ ቃለ ምልልስ ላይ ሞጅታባ “ሞቷል ብዬ አላስብም” ያሉት ፕሬዝዳንት ትራምፕ፣ ኢራኑ መሪ ከባድ ጉዳት እንደደረሰባቸው ግን ጠቁመዋል።

    “የሰውነቱ ግራ ክፍል፣ እጁ፣ እግሩ ሁሉ በጣም ከባድ ጉዳት ደርሶበታል። ግን ሞቷል ብዬ አላስብም” ብለዋል።

    ሞጅታባ ሞተው ከሆነ ኢራን ባለሥልጣናት የሚያደርጉት ሁሌ በሕይወት እንዳሉ የማስመሰል ነው፤ ነገር ግን በወሳኝ ጉዳዮች ላይ እንደሚያማክሯቸው እና ውሳኔያቸውን እንደሚቀበሉ ትራምፕ ጠቅሰዋል።

    ጨምረውም ከአሜሪካ ጋር ድርድር ሲያደርጉ የነበሩት የቴህራን ተደራዳሪዎች ተቀባይነት የሌላቸው መሆናቸውን በመግለጽ፣ ኢራን ውስጥ ማንኛውም ነገር የሚከሰትበት ዕድል እንዳለ ተናግረዋል።

    ከኢራን ጋር የሚደረገውን ጦርነት ስለማሸነፍ ያላቸውን ተስፋ በተመለከተ የተጠየቁት ትራምፕ፣ “ያለን የገንዘብ አቅም ከፍተኛ ነው፤ እናም ይህ ወደ ታላቅ ድል ይመራናል” ብለዋል።

    የአሜሪካ ገንዘብ ሚኒስቴር በዚህ ሳምንት በኢራን ላይ ያለውን ማዕቀብ ለማጠናከር አዲስ ዘመቻ መጀመሩን አስታውቋል።

    ኢራን ላይ መጠነ ሰፊ የምጣኔ ሀብት ጫና በመፍጠር መንግሥቱን ለመጣል የተለያዩ እርምጃዎች እንደሚወሰዱ ተነግሯል።

    አሜሪካ በወታደራዊ እርምጃ ይልቅ፣ ኢራን ላይ የምጣኔ ሀብት ዘመቻን ወደማጠናከር አዘንብላለች። ከቴህራን ጋር የንግድ ግንኙነት ያላቸው አገራት ትስስራቸውን ለማቋረጥ ፈቃደኛ ካልሆኑ ኢኮኖሚያዊ ቅጣቶች እንደሚጠብቋቸው አስጠንቅቃለች።

  14. አሜሪካ ተጨማሪ የጦር መርከብ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ልታሰማራ ነው

    ከኢራን ጋር ፍጥጫ ውስጥ የምትገኘው አሜሪካ አምስት ሺህ የሠራዊት አባላትን የሚይዘውን ግዙፉን የባሕር ኃይል አውሮፕላን ተሸካሚ መርከብ ዩኤስኤስ ቴዎዶር ሩዝቬልትን በተጨማሪነት ወደ መካከለኛው ምሥራቅ ልታሰማራ ነው።

    የአሜሪካ ባለሥልጣናት እንዳስታወቁት ግዙፉ የጦር መርከብ በሚቀጥሉት ሳምንታት ወደ አካባቢው የሚያቀና ሲሆን፣ ቢያንስ ለሰባት ወራት መካከለኛው ምሥራቅ ውስጥ ተሰማርቶ ይቆያል።

    ለወራት በዘለቀው ከኢራን ጋር በሚካሄደው ጦርነት ጫና ውስጥ የገባው እና ዓለም አቀፍ ተልዕኮ ያለበት የአሜሪካ ባሕር ኃይል በፋርስ ባሕረ ሰላጤ ተሰማርተው ከነበሩ አባላቱ ጋር በተያያዘ ባለፉት ሳምንታት ትችቶች ሲቀርቡበት ነበር።

    በመካከለኛው ምሥራቅ ከተቀመጠለት የጊዜ ገደብ በላይ 250 ቀናት የቆዩት የዩኤስኤስ አብረሃም ሊንከን የጦር መርከብ አባላት ጉዳይ በአሜሪካ ባለሥልጣናት ላይ ወቀሳ አስከትሏል።

    የተራዘመው የባሕር ኃይል አባላቱ ስምሪት በአእምሮ ጤናቸው ላይ ችግር መፍጠሩ እንዲሁም የአቅርቦት እጥረት አጋጥሞት እንደነበር ተገልጿል። በዚህ የተነሳም እራስን የማጥፋት ሙከራ እንደነበር ተዘግቧል።

    ይህንንም ተከትሎ ዩኤስኤስ ጆርጅ ዋሽንግተን የተባለ የጦር መርከብ የሊንከንን ቦታ ተክቶ በባሕረ ሰላጤው ተሰማርቷል።

  15. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ከሳዑዲ ጋር የተደረሰውን የኒውክሌር ስምምነት ለምክር ቤት አቀረቡ

    የዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ከሳዑዲ አረቢያ ጋር የተደረሰውን የሰላማዊ ኒውክሌር ትብብር ስምምነት እንዲገመገም ለአሜሪካ ኮንግረስ አስተላለፈ።

    ለኮንግረስ መቅረቡ፣ አገሪቱ ከሳዑዲ ጋር የተፈራረመችው የኒውክሌር ስምምነት በአሜሪካ የአውቶሚክ ኢነርጂ ሕግ መሠረት የሚገመገምበት ሂደት እንዲጀመር ያደርጋል።

    በስምምነቱ መሠረት ሳዑዲ አረቢያ ለሰላማዊ አገልግሎት ለሚውለው የኒውክሌር ፕሮግራሟ የሚውል ዩራኒየም እንድታበለጽግ ይፈቀድላታል።

    ሆኖም አንድ የአሜሪካ አስተዳደር ባለሥልጣን የምክር ቤቱን ዜናዎች ለሚከታተለው ‘ዘ ሂል’ ለተባለ የመገናኛ ብዙኃን እንደተናገሩት፣ ዶናልድ ትራምፕ ስምምነቱን ከፈረሙ በኋላ ያካተቱት ቅድመ ሁኔታ አሁንም በሥራ ላይ ይገኛል።

    ባለሥልጣኑ እንዳሉት፣ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት አቋም አሁንም አልተቀየረም። ስምምነቱ ተግባራዊ የሚሆነው ሳዑዲ አረቢያ የአብርሃም ስምምነትን ተቀብላ ከእስራኤል ጋር ግንኙነቷን በማሻሻል መደበኛ ሁኔታ ላይ ካደረሰች በኋላ ብቻ መሆኑን ገልጸል።

    ይህ አሜሪካ ከሳዑዲ ጋር የደረሰችው ስምምነት በመካከለኛው ምሥራቅ የኒውክሌር ፉክክር እንዲፋጠን ያደርጋል የሚል ስጋትን ፈጥሯል።

    በተለይም አሜሪካ ባለፈው አንድ ዓመት ውስጥ በኢራን ላይ እየወሰደች ያለው ወታደራዊ እርምጃ ዋና ዓላማ “ኢራን የኒውክሌር መሣሪያ እንዳትታጠቅ ማስቆም እና በቀጣናው የኒውክሌር ፉክክርን መከላከል” መሆኑን ስትገልጽ መቆየቷ፣ ይህ ጉዳይ ይበልጥ ትኩረት እንዲስብ አድርጓል።

    በዓለም ላይ ዋነኛ ነዳጅ አምራች ከሆኑ አገራት መካከል አንዷ የሆነችው ሳዑዲ አረቢያ፣ የተለያዩ መስኮች በማዘመን ከነዳጅ ጥገኝነት ነጻ ለመሆን በምታደርገው ጥረት የኒውክሌር ኃይል ማመንጫን ለመገንባት ጥረት እያደረገች ነው።

  16. ሜታ ‘ፌስቡክ እና ኢንስታግራም ሕጻናትን ጎድተዋል’ በሚል ለቀረበበት ክስ 18 ቢሊዮን ዶላር ለመክፈል ተስማማ

    ግዙፉ የማኅበራዊ ሚዲያ ኩባንያ ሜታ በፌስቡክ እና በኢንስታግራም ምክንያት በአሜሪካ ግዛቶች የቀረበበትን ከሕፃናት ደኅንነት ጋር የተያያዘ ክስ ለመፍታት ስምምነት ላይ ደረሰ።

    በስምምነቱ መሠረት የቴክኖሎጂ ኩባንያው ለአሜሪካ 48 ስቴቶች፣ ለኮሎምቢያ ዲስትሪክት እና ለሦስት የአሜሪካ ግዛቶች እስከ 18 ቢሊዮን ዶላር የሚደርስ ገንዘብ እንደሚከፍል አስታውቋል።

    ክፍያው የሚፈጸመው በ10 ዓመት ውስጥ እንደሚሆንም ገልጿል።

    በተጨማሪም ኩባንያው ፌስቡክ እና ኢንስታግራም መተግበሪያዎቹን የሚጠቀሙ ታዳጊዎች ማኅበራዊ ሚዲያዎቹ ላይ የሚቆዩበት ዕለታዊ ገደብ ማበጀት እና በምሽት ሰዓት እንዳይጠቀሙ ማገድን ጨምሮ የተለያዩ አሠራሮችን ለመተግበር ይገደዳል።

    ሜታ ይህንን ስምምነት ቢፈጽምም፣ የሠራው ስህተት እንደሌለ በመግለጽ አስተባብሏል።

    ኩባንያው ክስ የተመሠረተበት በአሜሪካ በርካታ የፌዴራል እና የግዛቶችን የሕፃናት የግል መረጃ ጥበቃ ሕጎችን ጥሷል በሚል ነበር።

    ክሱን የከፈቱት የአሜሪካ ግዛቶች ሜታ የማኅበራዊ ሚዲያ መድረኮቹን “ወጣቶች እና ታዳጊዎችን ለመሳብ እና በመጨረሻም ለማጥመድ” ተጠቅሟል በማለት ወንጅለዋል።

    የማኅበራዊ ሚዲያ መድረኮቹ “በአሜሪካ ወጣቶች አእምሯዊ እና አካላዊ ሁኔታ” ላይ ያደረሱትን ጉዳት ችላ እንዳለ በመጥቀስም ከስሰዋል።

    ስምምነቱ ይፋ ከተደረገ በኋላ፣ የኮሎምቢያ ዲስትሪክት ዐቃቤ ሕግ ብሪያን ሽዋልብ “ታላቅ የሕብረተሰብ ጤና ድል” ሲሉ ጠርተውታል።

    “ሜታ ለመተግበር የሚገደዳቸው የደኅንነት ገጽታዎች ወጣቶች ኢንስታግራም እና ፌስቡክን የሚጠቀሙበትን መንገድ ላይ ከመሠረቱ እና በአፋጣኝ ይለውጠዋል” ብለዋል።

    በስምምነቱ መሠረት ሜታ መተግበሪያዎቹ ላይ ማስተዋወቅ ካለበት አዲስ አሠራሮች አንዱ ሕጻናት በትምህርት ሰዓት የማኅበራዊ ሚዲያ መድረኮቹን እንዳይጠቀሙ መገደብ ነው።

    ጠንካራ የወላጅ ቁጥጥር ሥርዓትን መተግበር እንዲሁም ከ18 ዓመት በታች በሆኑ ተጠቃሚዎች ላይ ጥብቅ የዕድሜ ማረጋገጫ ዘዴ መከተልም ከአዲሶቹ አሠራሮች መካከል ይሆናሉ።

    ሜታ ባወጣው መግለጫ ቲክቶክ እና ዩቲዩብም ታዳጊ በሆኑ ተጠቃሚዎቻቸው ላይ ይህንን ዓይነት አሠራሮች መተግበር አለባቸው ብሏል።

  17. የትራምፕን የመጨረሻ ልጅ ሕይወት የሚያሰጋ ቪዲዮ በኢራን ሚዲያ መውጣቱን አሜሪካ አረጋገጠች

    የባሮን ትራምፕን ሕይወት የሚያሰጋ ቪዲዮ በኢራን መገናኛ ብዙኃን መተላለፉን የአሜሪካ ደህንነት መሥሪያ ቤት አስታወቀ።

    የፕሬዝደንት ዶናልድ ትራምፕ የመጨረሻ ልጅ የሆነውን ባሮን ትራምፕን ሕይወት የሚያሰጋ የሚመስል ቪዲዮ የኢራን መንግሥት በሚቆጣጠረው መገናኛ ብዙኃን መተላለፉን እንደሚያውቅ አረጋግጧል።

    አገልግሎቱ ይህን ያሳወቀው፣ ኢራን የባሮንን እንቅስቃሴ እየተከታተለች እንደሆነ እና በእርሱ ላይ ለሚወሰድ እርምጃ ድጋፍ ለሚያደርግ አካል የ10 ሚሊዮን ዶላር የገንዘብ ሽልማት መቅረቡን የሚገልፅ ቪዲዮ በኢራኑ መገናኛ ብዙኃን መለቀቁን ተከትሎ ነው።

    “የአሜሪካ ደህንነት መሥሪያ ቤት ስለ ቪዲዮው ያውቃል፤ በእኛ ጥበቃ ለሚደረግላቸው ሰዎች ስጋት ሊሆን ይችላል ተብሎ የሚታሰብን ማንኛውንም ነገር ይመረምራል” ሲሉ የአገልግሎቱ ቃል አቀባይ ኔት ሄሪንግ በሰጡት መግለጫ ተናግረዋል።

    አያይዘውም “ለአሠራር ደህንነት ሲባል ከጥበቃ ሥራ ጋር የተያያዙ የመረጃ ጉዳዮችን አናብራራም” ብለዋል።

    አሜሪካ የኢራኑን መንፈሳዊ መሪ አያቶላ አሊ ኻሜኒን ከገደለች ወዲህ፥ የኢራን መገናኛ ብዙኃን ፕሬዝደንቱን እና የቤተሰባቸውን አባላት የሚያሰጉ ይዘቶችን በተደጋጋሚ አሰራጭተዋል። ኻሜኒ የተገደሉት አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ በጋራ የከፈቱት ጦርነት መጀመሪያ ላይ ነው።

    የአሜሪካ ምሥጢራዊ አገልግሎት በባሮን ትራምፕ ላይ በኢራን ሚዲያ ስለተላለፈው ስጋት እንደሚያውቅ ሲኤንኤን ቀደም ሲል ዘግቦ ነበር።

  18. ኔታንያሁ ከኢራን መሪዎች ጋር ዲፕሎማሲያዊ ስምምነት መድረስ አይቻልም አሉ

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ከኢራን መሪዎች ጋር ዲፕሎማሲያዊ ስምምነት ላይ መድረስ አይቻልም ሲሉ ተናገሩ።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ፕሬዝዳንት ትራምፕ በቴህራን ላይ የጣሉትን የኢኮኖሚ ማዕቀብ አሞካሽተዋል።

    ቤንያሚን ኔታንያሁ በቅርቡ ከአሜሪካው ፕሬዝዳንት ጋር በተገናኙበት ወቅት ከኢራን ጋር ዲፕሎማሲያዊ መፍትሄ ሊኖር ይችል እንደሆን አንስተው መነጋገራቸውን ጨምረው ገልጸዋል።

    ነገር ግን “በኢራን ካለው ቡድን ጋር ስምምነት ላይ መድረስ ይቻላል የሚለው ላይ ጥርጣሬ አለኝ። ከእነዚህ አረመኔዎች ጋር ምንም ዓይነት ስምምነት ላይ መድረስ አይቻልም” በማለት ተናግረዋል።

    ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በኢራን እና በአሜሪካ መካከል የሰላም ስምምነት እንዲፈረም ቁልፍ የአሸማጋይነት ሚና የምትጫወተው ፓኪስታን ሁለቱን ወገኖች ወደ ድርድር ጠረጴዛ ለማምጣት የምታደርገው ጥረት ቀጥሏል።

  19. ስለሆርሙዝ ወሽመጥ ልናውቃቸው የሚገቡ ነጥቦች

    አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ላይ ጦርነት ከከፈቱ በኋላ ኢራን ከፍተኛ መጠን ያለው ነዳጅ እና ጋዝ ከፋርስ ባሕረ ሰላጤው አገራት ወደ ቀሪው ዓለም የሚተላለፍበትን የሆርሙዝ ወሽመጥን በተደጋጋሚ ዘግታለች።

    በዚህም ምክንያት ባለፉት ወራት በዓለም ገበያ ላይ የነዳጅ ዋጋ ከፍተኛ ጭማሪ በማሳየቱ በአገራት እና በሕዝባቸው ምጣኔ ሀብት ላይ ጫና ተፈጥሯል።

    የሆርሙዝ ወሽመጥ 20 በመቶ የሚሆነውን የዓለም የነዳጅ ፍጆታን ለማጓጓዝ የሚንቀሳቀሱ ግዙፍ መርከቦችን የሚያስተናግድ ሲሆን፣ በኢራን እና በኦማን መካከል ያለ ወሳኝ መተላለፊያ ነው።

    ከጦርነቱ መቀስቀስ በኋላ ግን ኢራን ወሽመጡ የሉዓላዊ ግዛቷ አካል መሆኑን እና በዚያ በኩል የሚተላለፉ መርከቦች ክፍያ እንዲፈጽሙ የሚያስገድድ ሕግ አውጥታለች።

    ነገር ግን አሜሪካ ይህንን ውሳኔ በመቃወም የባሕር መተላለፊያውን በጦር መርከቦቿ በመቆጣጠር ከኢራን የሚነሱ እና ወደ ኢራን የሚያቀኑ መርከቦች ላይ ዕገዳ ጥላለች።

    እስካሁን በተደረጉት ድርድሮች ላይም የሆርሙዝ ወሽመጥ መከፈት እና ነጻ የባሕር ላይ መተላለፊያ እንዲሆን የማድረጉ ጉዳይ ከዋነኛ ነጥቦች መካከል አንዱ ነው።

  20. በፓኪስታን ሆስፒታል ውስጥ በተነሳ እሳት ቢያንስ 14 ጨቅላ ሕጻናት ሞቱ

    ረቡዕ ማለዳ በፓኪስታን በሚገኝ የመንግሥት ሆስፒታል በጨቅላ ሕጻናት ክፍል በተቀሰቀሰ እሳት ቢያንስ 14 ሕጻናት መሞታቸውን የሆስፒታሉ ኃላፊዎች ተናገሩ።

    የሆስፒታሉ ባለሥልጣናት እሳቱ በተቀሰቀሰበት ወቅት በክፍሉ ውስጥ ቢያንስ 15 ሕጻናት ነበሩ ብለዋል።

    የእሳት አደጋው የተከሰተው በኢዝላማባድ በሚገኘው ፓኪስታን የሕክምና ሳይንስ ተቋም ሲሆን በአገሪቱ ውስጥ ካሉት ትላልቅ የሕዝብ ሆስፒታሎች መካከል አንዱ ነው።

    ባለሥልጣናቱ አንድ ሕጻንን ማትረፍ መቻሉን ሲናገሩ የአገሪቱ ጤና ሚኒስትር ሙስጣፋ ካማል 14 ሕጻናቶች መሞታቸውን አረጋግጠዋል።

    ሞሐማድ ሳሚ የተባለች እናት እሳቱ በተነሳበት ወቅት ልጇ በሕጻናት ጽኑ ሕሙማን ክፍል ክትትል እየተደረገለት አንደነበር ተናግራለች።

    “ምን ማለት እንዳለብኝ እና ማንን መውቀስ እንዳለብኝ አላውቅም” ያለችው እናቲቱ “ልጄን አጥቻለሁ” ስትል በእንባ ታጅባ ለመገናኛ ብዙኃን ተናግራለች።

    የሆስፒታሉ አስተዳደር አስፈላጊው ሰነድ ከተሟላ በኋላ የሕጻናቱን አስከሬን ለወላጆቻቸው እንደሚያስረክብ አስታውቋል።

    የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች እሳቱ ማለዳ 12፡45 ላይ በማዋለጃ ክፍል የሚገኘው የአየር ማቀዝቀዣ በመፈንዳቱ መቀስቀሱን ተናግረዋል።

    የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች በፍጥነት በቦታው በመድረስ እሳቱን ማጥፋታቸውን እና ሕይወት አድን ስራ መጀመራቸውን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    የፓኪስታን አገር ውስጥ ሚኒስትር ሞሺን ናቅቪ እና ጠቅላይ ሚኒስትር ሼህባዝ ሻሪፍ የተሰማቸውን ሐዘን ገልጸዋል።

    ሻሪፍ “ሕጻናት በሞቱበት አደጋ የማይተካ ሕይወት አጥተናል” በማለት አስቸኳይ ምርምራ እንዲደረግ ጠይቀዋል።

    ፕሬዚዳንት አሲፍ አሊ ዛርዳሪ ልጆቻቸውን ላጡ ቤተሰቦች መጽናናትን ተመኝተው “ልብ የሚሰብር እና የማይተካ እጦት” ብለውታል።

    ዛርዳሪ ለእሳት አደጋው ተጠያቂ የሚሆኑ ግለሰቦች በፍጥነት እንዲለዩ እና በሕግ መሠረት ተጠያቂ እንዲሆኑ አሳስበዋል።

    ሆስፒታሉም የእሳት አደጋ ሲከሰት ሊወስዳቸው የሚገባ የጥንቃቄ እርምጃዎች በአግባቡ መቀመጣቸውን እንዲያረጋግጥ አዝዘዋል።

    ሆስፒታሉ ሥራ የጀመረው እአአ በ1985 ሲሆን በርካታ የቀዶ ሕክምና ክፍሎች ስፔሻሊስት ክሊኒኮችን ያቀፈ ነው።

    1,200 አልጋዎችን እና 5,000 የተመላላሽ ታካሚዎችን የመያዝ አቅም ያለው እህ ሆስፒታል ለህፃናት ልዩ እንክብካቤ እና ለጤና ባለሙያዎች ስልጠና ይሰጣል።