ኢራን ላለፉት ስድስት ወራት ከአሜሪካ ጋር እያdረገችው ባለው ጦርነት ምክንያት ዘግታው የቆየችውን የሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ ዳግም ለመክፈት
ቅድመ ሁኔታዎችን አስቀመጠች።
ወሳኙን የባሕር መተላለፊያ ለመክፈት በመካከለኛው ምሥራቅ የሚደረጉ ጦርነቶችን እንዲቆሙ ማድረግ ከቅድመ ሁኔታዎቿ መካከል አንዱ መሆኑን ገልጻለች።
የኢራን ጠቅላይ ብሔራዊ የፀጥታ ምክር ቤት ፀሐፊ ሞህሰን ሬዛኢ ከሊባኖሱ አል ማናር ቴሌቪዥን ጋር በነበራቸው ቃለ ምልልስ በባሕረ ሰላጤው ላይ ከአሜሪካ ጋር የሚደረግ ማንኛውም መግባባት በሊባኖስ፣ በጋዛ እና በሶሪያ ውስጥ የሚደረጉ ጦርነቶችን እና ወታደራዊ እንቅስቃሴዎችን ማቆምን ያካትታል ብለዋል።
በጋዛ ሰርጥ የተፈጠረው ግጭት መቆም እንዳለበት የተናገሩት የደኅንነት ኃላፊው፣ እስራኤል ከሊባኖስ እንድትወጣ እና በሶሪያ ላይ የሚሰነዘረውን ጥቃት እንድታቆም ጠይቀዋል።
ሬዛኢ በሆርሙዝ ወሽመጥ አካባቢ ያለው ችግር በቀጣናው ውስጥ ካለው እጅግ ሰፊ ግጭት መካከል አንዱ ነው ካሉ በኋላ ኢራን በአሜሪካ ላይ እንደገና እምነት ልትጥል የምትችለው፣ የገባችውን ቃል በተግባር ለማሳየት ያላትን ቁርጠኝነት ካረጋገጠች በኋላ ብቻ ነው ብለዋል።
ይሁን እንጂ ሁለቱ አገራት ዳግም ወደ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት መመለስ የሚቻሉ አይመስልም። ዎል ስትሪት ጆርናል ሐሙስ ዕለት እንደዘገበው የትራምፕ አስተዳደር በሰኔ ወር ከኢራን ጋር ወዳደረገው የመግባቢያ ስምምነት ለመመለስ ፍላጎት የለውም።
ጋዜጣው ጉዳዩን በቅርበት
የሚያውቁ ሰዎችን በመጥቀስ የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በሰኔ ወር የስምምነት ማዕቀፍ ላይ ፍላጎት እንደሌላቸው እና በምትኩ አስተዳደራቸው ኢራንን በኢኮኖሚያዊ ጫና ለማንበርከክ አንደሚችል እምነት አላቸው።
አሜሪካ ሰኞ ዕለት ከቴህራን ጋር የንግድ ግንኙነት ያላቸው አገራትን አስጠንቅቃ “ኢኮኖሚያዊ ጦርነት” መክፈቷን አስታውቃለች። ይህም የአሜሪካ ትኩረት ከወታደራዊ እርምጃ ወደ ኢኮኖሚያዊ ጫና መሸጋገሩን ያመለካተ ነው።
ኢራን መርከቦች በሆርሙዝ ወሽመጥ እንዲያልፉ “ጊዜያዊ እና የተወሰነ” መስመር የፈቀደች ሲሆን፣ ወደፊት የሚኖር የመርከቦች ፍሰት ከዋሽንግተን ጋር በሚደረጉ ግንኙነቶች ላይ የተመሠረተ ይሆናል ሲሉ ሬዛኢ ተናግረዋል።
በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ ኦማን እና ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ጊዜያዊ ደኅንነቱ የተጠበቀ የመርከቦች መተላለፊያ መስመር ለማቋቋም እንዲሁም ከዋና ዋና የነዳጅ ጫኝ መርከቦች መተላለፊያ መስመሮች ፈንጂዎችን ለማጽዳት ተወያይተዋል።
ይሁን እንጂ፣ የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ አዛዥ አድሚራል ብራድ ኩፐር ሐሙስ ዕለት በአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) የኤክስ ገጽ ላይ በቪዲዮ ባስተላለፉት መልዕክት የአሜሪካ ወታደሮች ፈንጂዎችን ከባሕር ወሽመጥ ላይ ማጽዳታቸውን ተናግረዋል።
ሴንትኮም ባለፉት በርካታ ወራት ውስጥ ወደ 1,500 የሚጠጉ የንግድ መርከቦችን እና 750 ሚሊዮን በርሜል ድፍድፍ ነዳጅ የጫኑ መርከቦች እንዲያልፉ ማገዙን ኩፐር ተናግረዋል።
ኩፐር አክለውም “ዛሬ፣ ዓለም አቀፍ የመርከብ መስመሮች ክፍት ናቸው፣ እናም ፍጥነቱ እየጨመረ ነው” ብለዋል።
ይሁን እንጂ፣ የቅርብ ጊዜ መረጃዎች እንደሚያሳዩት ማክሰኞ ዕለት ሆርሙዝን ያቋርጡት አምስት መርከቦች ብቻ ናቸው።
ይህ ደግሞ በየካቲት ወር ጦርነቱ ከመጀመሩ በፊት በዚህ ወሳኝ በሆነው ወሽመጥ በኩል በየቀኑ ሲያቋርጡ ከነበሩት በግምት 130 መርከቦች በጣም ያነሰ ነው።