ቀጥታ, አሜሪካ በኢራን ወደቦች ላይ የጣለችውን እገዳ ላልተወሰነ ጊዜ ልታራዝም እንደምትችል አስታወቀች

አሜሪካ ሐሙስ ዕለት በኢራን ወደቦች ላይ የጣለችውን እገዳ ላልተወሰነ ጊዜ በማራዘም የምጣኔ ሃብት ጫናውን ልታጠናክር አንደምትችል ተናገረች። አሜሪካ ይህንን ያለችው በሁለቱ አገራት መካከል ይደረጋል ተብሎ የሚጠበቀው ድርድር ባለመሳካቱ ውጥረት ባየለበት እና የዓለም የነዳጅ ዘይት አቅርቦት እየቀነሰ በመጣበት ወቅት ነው። የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር የሆኑት ፒት ሄግሴት ለጋዜጠኞች ጦሩ በኢራን ላይ የተጣለውን እገዳ ለማስቀጠል በቀጣናው መቆየት የሚያስችል አቅም አለው ብለዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. በጃፓን በተከሰተ ከዚህ ቀደም “ታይቶ የማይታወቅ” ከባድ ዝናብ ምክንያት ስምንት ሰዎች ሞቱ

    በምሥራቃዊ ጃፓን ያጋጠመ ከባድ ዝናብ ቢያንስ የስምንት ሰዎች ሕይወት እንዲያልፍ እና በሺህዎች የሚቆጠሩ ተጓዦች በረራ እንዲስተጓጎል አደረገ።

    ባለሥልጣናት ከዚህ በፊት "ታይቶ የማይታወቅ" ሲሉ የገለጹት ይህ ከባድ ዝናብ፣ ቺባ ግዛት ውስጥ በሚገኙ ከ20,000 በላይ መኖሪያ ቤቶች የኤሌክትሪል ኃይል እንዲቋረጥ ምክንያት ሆኗል።

    የቺባ ግዛት አስተዳዳሪ ቶሺሂቶ ኩማጋይ "ይህ ሁኔታ በጃፓን ታሪካዊ የአየር ሁኔታ እንኳ ሲታይ እጅግ ያልተለመደ ነው" ሲሉ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

    “ከዚህ ቀደም ለበርካታ የተፈጥሮ አደጋዎች ምላሽ ሰጥቻለሁ፤ እንደዚህ አይነት ሁኔታ ግን አጋጥሞኝ አያውቅም" ሲሉም አክለዋል።

    የጃፓን ሚቲዮሮሎጂ ኤጀንሲም “ከዚህ ቀደም ታይቶ የማይታወቅ ከባድ ዝናብ” እንደሚሆን አስቀድሞ ተንብዮ ነበር።

    በዚህ ከፍተኛ ዝናብ ምክንያት ቢያንስ ስምንት ሰዎች መሞታቸውን የጃፓን መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    ከሞቱት መካከል አንዷ በጎርፍ በተሸፈነ መንገድ ላይ ሳለች መኪናዋ ውስጥ ውሃ ገብቶ ሕይወቷ ማለፉን ባለሥልጣናት ተናግረዋል። ሁለት ሰዎች ደግሞ መንገድ ላይ ወድቀው ሕይወታቸው እንዳለፈ ተገልጿል።

    የአካባቢው ባለሥልጣናት ሐሙስ ዕለት በአገሪቱ ከፍተኛ የሆነውን ‘ደረጃ አምስት’ የአደጋ ማስጠንቀቂያ ሰጥተው ነበር። ዛሬ አርብ ይህ ማስጠንቀቂያ ወደ ደረጃ አራት ዝቅ ቢደረግም፣ መሬት መንሸራተት እና ጎርፍ ሊፈጠር ይችላል የሚለው ስጋት አሁንም ቀጥሏል።

    ይህ ከፍተኛ ዝናብ የተከሰተው በዚህ ሳምንት ጃፓን እና ጎረቤት አገራት ውስጥ ተከታታይ አውሎ ነፋሶች ከታዩ በኋላ ነው። የሚቲዮሮሎጂ ባለሙያዎች በዚህ ወቅት ባልተመደ መጠን የሚንቀሳቀስ አውሎንፋስ (ታይፉን) እንደሚከሰት ተንብየው ነበር።

    አሁኑ ከፍተኛ ዝናብ፣ ወደ አገሪቱ ምሥራቃዊ ክፍል የነፈሰው ሞቃት እና እርጥበታማ አየር ከላይ ካለው ቀዝቃዛ አየር ጋር መቀላቀሉ በፈጠረው ከፍተኛ የሆነው የአየር ሁኔታ መዛባት የተከሰተ መሆኑን የጃፓን ሚቲዮሮሎጂ ኤጀንሲ አስታውቋል።

  2. አሜሪካ ከ40 በላይ አገራት ቻይና የተጣለባትን ታሪፍ እንድታመልጥ እያገዙ ነው ስትል ከሰሰች

    ቻይና ወደ አሜሪካ የምትልካቸው ምርቶች ላይ የተጣለውን ታሪፍ ለማለፍ ስትል፣ ምርቶቿን አሜሪካ ዝቅተኛ ቀረጥ በጣለችባቸው አገራት በኩል አድርጋ እያስገባች መሆኑን ዋይት ሀውስ ገለጸ።

    ከ40 በላይ በላይ አገራትም ቻይና አሜሪካን ታሪፍ እንዳታመልጥ እገዛ እያደረጉ ነው ሲል ከስሷል።

    ዋይት ሀውስ ባወጣው ሪፖርት ከዘረዘራቸው አገራት መካከል ካናዳ፣ ህንድ፣ ሜክሲኮ፣ ጃፓን እና ደቡብ ኮሪያ ይገኙበታል። ጎረቤት አገር ኬንያ እና ሞሮኮም ዝርዝሩ ውስጥ ተካትተዋል።

    የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር እንደሚከስሰው ከሆነ፣ እነዚህ አገራት ቻይና ለአሜሪካ መክፈል የነበረባትን በቢሊዮን ዶላሮች የሚቆጠር የታሪፍ ክፍያ እንድታመልጥ አግዘዋል።

    ቻይና ምርቶቿን ወደ ሦስተኛ አገራት ከላከች በኋላ፣ የተመረቱበት ትክክለኛ ስፍራ ተሸፍኖ በድጋሚ እንዲታሸጉ አድርጋለች ሲል ዋይት ሀውስ ከስሷል።

    የዋይት ሀውስ የንግድ አማካሪ ፒተር ናቫሮ፣ ይህ አካሄድ “የአሜሪካውያንን የሥራ ዕድል እና በቢሊዮን [ዶላር] የሚቆጠር ገቢ” እንዳሳጣ ገልጸዋል።

    በዋሽንግተን የሚገኘው የቻይና ኤምባሲ ቃል አቀባይ ግን “በንግድ ጦርነት ውስጥ አሸናፊ የለም” ሲሉ ክሱን አጣጥለዋል። አሜሪካ የወሰደችውን የታሪፍ እርምጃ እንዲሁም የመንግሥት ኃይልን በመጠቀም የቻይና ኩባንያዎች ዒላማ መደረጋቸውን ተቃውመዋል።

    “ድንበር ተሻጋሪ ምርቶችን በተመለከተ የሚወሰዱ የተናጠል እርምጃዎች ወይም ስምምነቶች የሦስተኛ አካላትን ጥቅሞች ዒላማ ማድረግ ወይም መጎዳት የለባቸውም” ብለዋል።

    ቢቢሲ በዚህ ተግባር ለተከሰሱት የካናዳ፣ ህንድ፣ ሜክሲኮ፣ ጃፓን፣ ደቡብ ኮሪያ እና የሌሎች የንግድ አጋሮችን የአሜሪካ ኤምባሲዎች ጥያቄ አቅርቧል።

    ይህ ሪፖርት ይፋ የሆነው አሜሪካ እና ቻይና ተከታታይ የማዕቀብ እርምጃዎችን አንዳቸው በሌላኛቸው ላይ በጣሉበት ወቅት ነው። ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና የቻይናው መሪ ዢ ጂንፒንግም በዋሽንግተን ሊገናኙ ሳምንታት ቀርተውታል።

    የዋይት ሀውስ ሪፖርት እንደሚያሳየው 30 ቢሊዮን ዶላር እስከ 300 ቢሊዮን ዶላር እንደሚያወጡ የሚገመቱ ምርቶች ከፍተኛ ታሪፍ ከተጣለባቸው አገራት ተነስተው ዝቅተኛ የአሜሪካ ቀረጥ ባለባቸው አገራት በኩል አልፈው አሜሪካ ገብተዋል።

    “ትራንስሺፕመንት” በመባል የሚታወቀው ይህ አካሄድ፣ ከአንድ አገር የተነሱ ምርቶች በሌላ አገር በኩል ወደ መጨረሻ መዳረሻቸው የሚገቡበት ነው።

  3. የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ ብሪታኒያን ‘እስላማዊ ሪፐብሊክ’ ማለታቸው አነጋጋሪ ሆነ

    የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታኒያሁ ብሪታኒያን ‘እስላማዊ ሪፐብሊክ’ ብለው መጥራታቸው አነጋጋሪ ሆኗል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከአገራቸው ጦር ሠራዊት ፖድካስት ጋር በነበራቸው ቃለ ምልልስ፣ ቀደምት የብሪታኒያ መሪዎች የእስራኤል አጋር እንደነበሩ እና ይህ ሁኔታ አሁን መቀየሩን ባነሱበት ጊዜ ነው አነጋጋሪውን አስተያየት የሰነዘሩት።

    እስራኤል በጋዛ፣ በሊባኖስ እና በኢራን ጦርነት ወቅት ባካሄደቻቸው ዘመቻዎች የተነሳ ብሪታኒያን ጨምሮ በአውሮፓ አገራት ተቃውሞ ሲሰነዘርባት ቆይቷል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ በስድስቱ ቀን ጦርነት ወቅት የቀድሞው የብሪታኒያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዊኒስተን ቸርችል ልጆች ወደ እስራኤል ሄደው ጦርነቱን እስራኤልን በሚደግፍ ሁኔታ መዘገባቸውን አንስተዋል።

    “ያንን [ድጋፍ] አሁን ለመግኘት ሞክር፣ ልታገኝ የምትችለው የብሪታኒያ እስላማዊ ሪፐብሊክን ነው” በማለት እየሳቁ ሲናገሩ ተደምጠዋል።

    ይህ የኔታኒያሁ ንግግር መነጋገሪያ መሆኑን ተከትሎ ቃል አቀባያቸው አገላለጹን ተከላክለው ምላሽ ሰጥተዋል።

    የጠቅላይ ሚኒስትሩን አስተያየት ተከትሎ የፖድካስቱ አስተናጋጅ ከብሪታኒያ በተጨማሪ አጠቃላዩ አውሮፓ በእስራኤል ላይ ተመሳሳይ አቋም እያራመደ መሆኑን ጠቅሶ ላቀረበላቸው ጥያቄ ተጨማሪ ሃሳብ ሰንዝረዋል።

    ኔታኒያሁ ሃሳባቸውን የበለጠ በማጠናከር “አዎ፤ ነገር ግን አንድ ሰው እንዳለው ኒውክሌር ጦር መሳሪያ የታጠቀች የመጀመሪያዋ እስላማዊ ሪፐብሊክ የምትሆነው ብሪታኒያ እስላማዊ ሪፐብሊክ ናት” በማለት መልሰዋል።

    በብሪታኒያ እና በእስራኤል መካከል ያለው ግንኙነት እየሻከረ ሲሆን አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር አንዲ በርንሃም ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ የበለጠ ሊበላሽ እንደሚችል ሲነገር ቆይቷል።

    በርንሃም ብሪታኒያ መካከለኛው ምሥራቅን በተመለከተ አዲስ አካሄድን እንደምትከተል ተናግረዋል። በእስራኤላዊ ግለሰቦች እና ተቋማት እንዲሁም ህገወጥ ሰፋሪዎች ላይ ማዕቀብ እንደሚጥሉ “በእስራኤል መንግሥት ላይ ጫና እንደሚያሳድሩ” ገልጸዋል።

  4. አሜሪካ ተተኪ አውሮፕላን ጫኝ ግዙፍ መርከብ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ አሰማራች

    በአውሮፕላን ተሸካሚ መርከቦች ላይ ከ250 ቀናት በላይ የቆዩ የአሜሪካ ጦር አባላት የአአምሮ ጤና ሁኔታ ስጋት ከፈጠረ ወዲህ በፓሲፊክ ውቅያኖስ ላይ የሚገኝ አውሮፕላን ተሸካሚ መርከብ፣ ዩኤስኤስ ጆርጅ ዋሺንግተን ወደ መካከለኛው ምሥራቅ መጓዝ ጀመረ።

    በመካከለኛው ምሥራቅ ለረዥም ጊዜ የቆየው ዩኤስኤስ አብራሃም ሊንከን አውሮፕላን ጫኝ መርከብ የአቅርቦት እጥረት እንደገጠመው ተዘግቧል።

    አዲስ የተሰማራው መርከብ ለወራት የቆየውን ሊንከን የተሰኘውን መርከብ ተክቶ አሜሪካ በኢራን ላይ የምታካሄደውን የአየር ድብደባ ያግዛል።

    በመርከቡ ላይ የሚገኙ ባሕረተኞች ከ260 ቀናት በላይ መቆየታቸውን በመጥቀስ የሕግ አውጪዎች ስጋታቸውን እየገለጹ ነው።

    በርካታ ዲሞክራት የሕግ አውጪዎች ፔንታገን ተጠያቂ እንዲሆን እና ትራምፕ ጦርነቱን እንዲቋጩ ግፊት እያደረጉ ነው።

    የመከላከያ ሚኒስትሩ ፒት ሄግሴት ዘገባው ያለውን እውነታ “ሙሉ በሙሉ አይወክልም” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።

    ሄግሴት አክለውም የአሜሪካ ባሕር ኃይል በኢራን ወደቦች ላይ የጣለውን እገዳ “ላልተወሰነ ጊዜ” እንደሚቀጥል ተናግረዋል።

    ዩኤስኤስ ጆርጅ ዋሺንግተን በቬትናም ከሚገኘው ዳ ናንግ ወደብ ባለፈው ሳምንት መንቀሳቀሷን ባሕር ኃይሉ አስታውቋል።

    መርከቧ በሲንጋፖር በኩል ስታልፍ የታየች ሲሆን ማላካ ወሽመጥ መድረሷም ተዘግቧል።

  5. ዓለም አቀፍ የባህር ላይ መከላከያ ጥምረት ለመመስረት አስራ አምስት አገሮች ስምምነት መፈረማቸው ተገለፀ

    አስራ አምስት አገሮች ዓለም አቀፍ የባህር መከላከያ ጥምረት ለመመስረት የተዘጋጀውን ሰነድ መፈረማቸውን የሳዑዲ አረቢያ መከላከያ ሚኒስቴር አስታወቀ።

    "የጋራ መግለጫውን የፈረሙ አገሮች ቁጥር 15 ደርሷል፤ 13 አገሮች ደግሞ ብሔራዊ ሂደቶችን አጠናቅቀው እና የጥምረቱን ቻርተር ፈርመው በይፋ መቀላቀላቸውን አስታውቀዋል" ሲል ሚኒስቴሩ ሐሙስ ዕለት በኤክስ ላይ ባወጣው መግለጫ ይፋ አድርጓል።

    ይህ መግለጫ የወጣው ሐሙስ ዕለት በጂዳ ከተካሄደው የጥምረቱ ዕቅድ አውጪዎች ሦስተኛ ስብሰባ በኋላ ነው።

    "ይህ ጥምረት ወደ ተቋማዊ እና የስራ እንቅስቃሴ ደረጃ መሸጋገሩን የሚያመለክት ሲሆን የተቀሩት አገሮች ደግሞ ጥምረቱን ለመቀላቀል የሚያስፈልጉትን ብሔራዊ ሂደቶች እያጠናቀቁ ነው” ሲል የሳዑዲ መግለጫ አክሏል።

    ጥምረቱ በሳዑዲ የሚመራ ሲሆን፣ ፓኪስታን የምክትልነቱን ቦታ እንደምትይዝ ተገልጿል።

    ሳዑዲ አረቢያ እና ሌሎች 13 አገሮች በባብ አል-ማንዳብ ወሽመጥ፣ በቀይ ባህር እና በኤደን ባሕረ ሰላጤ ውስጥ ያለውን የመርከቦች እንቅስቃሴ ነፃነት፣ ዓለም አቀፍ ንግድ እና የኃይል አቅርቦት መስመሮችን ለመጠበቅ ያለመ ባለብዙ አገር የባህር መከላከያ ጥምረት መቋቋሙን በዚህ ዓመት ሐምሌ 30 ነበር ያስታወቁት።

  6. የኢራን ጦርነት ቻይና የምትሸጣቸውን በኤሌትሪክ የሚሠሩ የከባድ መኪናዎች ቁጥር ጨምሯል ተባለ

    የኢራን ጦርነት ከተቀሰቀሰ እና የነዳጅ ዋጋ ንረት ከተከሰተ ወዲህ ቻይና ወደ ሌሎች የእስያ አገራት የምትልካቸው የኤሌትሪክ ከባድ መኪናዎች ቁጥር እንዲሁም የአገር ውስጥ ሽያጭ በከፍተኛ ደረጃ ማደጉ ተገለጸ።

    ቻይና በኤሌትሪክ የሚሠሩ ቀላል እና ከባድ የጭነት መኪናዎች በፍጥነት እያመረተች ለገበያ የምታቀርብ ሲሆን ሌሎች የእርሷን ፈለግ ለመከተል እየሞከሩ ነው።

    የካቲት 21/2018 ዓ.ም. እስራኤል እና አሜሪካ በጥምረት ኢራን ላይ ጦርነት ካወጁ ወዲህ ቻይና ወደ ውጭ የምትልከው በኤሌትሪክ የሚሠሩ የጭነት መኪናዎች ቁጥር በእጥፍ አድጓል።

    ደቡብ እና ደቡብ ምሥራቅ እስያ አገራት ከመካከለኛው ምሥራቅ በሚመጣ ነዳጅ ላይ ጥገኛ ናቸው።

    ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን መዝጋቷን ተከትሎ በናፍያ ዋጋ ላይ ከፍተኛ ጭማሪ ታይቷል።

    ይህም ለቻይና የኤሌትሪክ መኪናዎች ትልቅ ገበያ መፍጠሩን 'ግሎባል ፔትሮል ፕራይስስ ዶት ኮም' ዘግቧል።

    የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት ከተጀመረ ወዲህ በሲሪላንካ የናፍጣ ዋጋ በ48 በመቶ ሲጨምር በፊሊፒንስ ደግሞ 57 በመቶ ከፍ ብሏል።

    የቻይና መንግሥት ይፋ ባደረገው መረጃ ከኢራን ጦርነት ወዲህ በአገሪቱ የነዳጅ ዋጋ ላይ የ15 በመቶ ጭማሪ ታይቷል።

    የዓለማችን ግንባር ቀደም በኤሌትሪክ የሚሰሩ የጭነት መኪናዎች አምራች በሆነው ሳኒ ውስጥ ዓለም አቀፍ የገባያ ጥናት ባለሙያ የሆኑት ዣኦቲንግ ዩኡ “ጦርነቱ አዳዲስ ገበያዎችን ከፍቷል” ሲሉ ተናግረዋል።

  7. በማሊ መፈንቅለ መንግሥት ለማካሄድ አሲሯል በሚል 20 ዓመት የተፈረደበት ፈረንሳዊ ምህረት ተደረገለት

    በምዕራብ አፍሪካዊቷ አገር ማሊ መፈንቅለ መንግሥት ለማካሄድ አሲሯል ተብሎ የ20 ዓመት አስር ተፈርዶበት የነበረው ፈረንሳዊ ሐሙስ ዕለት ፕሬዚዳንታዊ ምህረት እንደተደረገለት ተገለጸ።

    ያን ቬዚሊየር የተባለው ፈረንሳዊ ባለፈው ዓመት “ከፈረንሳይ የደህንነት መስሪያ ቤት ተልዕኮ በመቀበል” የማሊን መንግሥት ለመጣል ከበርካታ ጦር ጄነራሎች እና ወታደሮች ጋር አሲሯል ተብሎ ተከስሶ ነበር።

    ማሊ የፍርድ ውሳኔውን እንድትቀለብስ ያደረጋት ምን እንደሆነ አልታወቀም።

    የፈረንሳይ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከዚህ ቀደም ቬዚሊየር የአገሪቱ ሰላይ ነው መባሉ “መሠረተ ቢስ” ብሎ ከማሊ መንግሥት ጋር እየተነጋገረ መሆኑን ገልጾ ነበር።

    የማሊ መንግሥት በፌስ ቡክ ላይ ባሰፈረው መልዕክት “ይህ ምህረት የመከላከያ መብቶች ሁሉ በተከበሩበት የፍርድ ሂደት ውስጥ በተሰጠ ውሳኔ የተረጋገጡትን እውነታዎች የማይንድ ወይም በጥያቄ ውስጥ የማያስገባ፣ ግለሰቡ ከማሊ በአስቸኳይ እንዲወጣ ከማድረግ ጋር አብሮ የሚከናወን ነው” ብሏል።

    ማሊ የፈረንሳይ ቅኝ ግዛት የነበረች ሲሆን እአአ ከ2012 ጀምሮ በእስላማዊ ታጣቂዎች የተነሳ የደህንነት ቀውስ ውስጥ ገብታለች።

    ፕሬዚዳንት አሲም ጎይታ እአአ በ2021 መፈንቅለ መንግሥት አካሂደው ሥልጣን የተቆጣጠሩ ሲሆን እርሳቸው ፕሬዚዳንት ከሆኑ በኋላም የጂሃዲስቶች ጥቃት ጨምሯል።

    ባለፈው ዓመት ፈረንሳዊው በቁጥጥር ሥር በዋለበት ወቅት የማሊ የደህንነት ሚኒስትር ጄኔራል ዳውድ አሊ መሐመዳይን “የማሊ የጸጥታ ኃይሎች አካል” የሆኑ ግለሰቦች “የሪፐብሊኩን ተቋማት ለማወክ በመፈለጋቸው” በቁጥጥር ሥር ውለዋል ብለው ነበር።

    ሚኒስትሩ አክለውም "እነዚህ ወታደሮችና ሲቪሎች" "የውጭ አገራትን እርዳታ" እንዳገኙ ገልጸዋል።

    ቬዚሊየር በማሊ የፖለቲካ መሪዎችን፣ የሲቪል ማኅበረሰብን እና የጦር አባላትን በማሰባሰብ "የፈረንሳይ የስለላ አገልግሎትን ወክሎ" እርምጃ መውሰዱን ሚኒስትሩ ተናግረዋል።

    በማሊ ያለው የፖለቲካ ውጥረትና የጸጥታ ቀውስ ተባብሷል።

  8. አሜሪካ በኢራን ወደቦች ላይ የጣለችውን እገዳ ላልተወሰነ ጊዜ ልታራዝም እንደምትችል አስታወቀች

    አሜሪካ ሐሙስ ዕለት በኢራን ወደቦች ላይ የጣለችውን እገዳ ላልተወሰነ ጊዜ በማራዘም የምጣኔ ሃብት ጫናውን ልታጠናክር አንደምትችል ተናገረች።

    አሜሪካ ይህንን ያለችው በሁለቱ አገራት መካከል ይደረጋል ተብሎ የሚጠበቀው ድርድር ባለመሳካቱ ውጥረት ባየለበት እና የዓለም የነዳጅ ዘይት አቅርቦት እየቀነሰ በመጣበት ወቅት ነው።

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር የሆኑት ፒት ሄግሴት ለጋዜጠኞች፣ ጦሩ በኢራን ላይ የተጣለውን እገዳ ለማስቀጠል በቀጣናው መቆየት የሚያስችል አቅም አለው ብለዋል።

    በኢራን ወደቦች ላይ የተጣለው እገዳ አገሪቱ ላይ የምጣኔ ሃብት ጫና እየፈጠረ ነው።

    "የአሜሪካ የባህር ኃይል እንደዚህ ዓይነት የእግድ እርምጃን ላልተወሰነ ጊዜ ማስቀጠል ይችላል፤ ምክንያቱም ቀደም ሲል እንዳደረግነው ሁሉ መርከቦችን እየቀያየርን ማስገባትና ማስወጣታችንን እንቀጥላለን" ሲሉ ሄግሴት ወደ ፓናማ ባደረጉት ጉዞ ወቅት ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

    የገንዘብ ሚኒስትሩ ስኮት ቤሴንት ደግሞ አገራቸው በኢራን ኢኮኖሚ ላይ ተጨማሪ ጉዳት ለማድረስ ማቀዷን ይፋ አድርገዋል።

    “በሚቀጥለው ሳምንት ለሚሰጡ ተጨማሪ መግለጫዎች ተዘጋጁ። ምክንያቱም በአንድ አገር ላይ በሚደረግ የኢኮኖሚ ማግለል ታሪክ ውስጥ ታይቶ የማይታወቅ ዓይነት እርምጃዎችን ልንወስድ ነው” ሲሉ ከኒውስማክስ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ወቅት ተናግረዋል።

    በሰኔ ወር በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የተፈረመው የመግባቢያ ሰነድ ከፈረሰ ወዲህ ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን ዳግም በመዝጋት አሜሪካ ላይ ጫና ለመፍጠር እየሞከረች ነው።

    ጦርነቱ ከጀመረበት የካቲት ወር አንስቶ ወሽመጡን ለማቋረጥ የሚሞክሩ መርከቦች ላይ ጥቃት የምትፈጽመው ቴህራን የዓለም የነዳጅ ዋጋ ከፍ እንዲል አስተዋጽኦ አድርጋለች።

    ሐሙስ ዕለት ምሽት የአቡዳቢ ብሔራዊ የነዳጅ ኩባንያ ንብረት የሆኑ ሁለት ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ጥቃት እንደደረሰባቸው የዩኤኢ ብሔራዊ ዜና ኤጀንሲ ዋም ዘግቧል።

    የዩናይትድ አረብ ኤሜሬትስ መንግሥት የኢራንን ጥቃት አውግዟል።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ጦርነቱን በፍጥነት እንዲቋጩ ከአገር ውስጥ ከፍተኛ ግፊት እየደረሰባቸው ነው።

    ትራምፕ፣ አሜሪካ በባህር ወሽመጡ ላይ "ሙሉ ቁጥጥር" እንዳላት በተደጋጋሚ የገለጹ ሲሆን፣ ኢራን ይህንን አስተባብላለች።

    ቴሀራን ያስቀመጠቻቸው ቅድመ ሁኔታዎች እስኪሟሉ ድረስ ወሽመጡ ዳግም እንዲከፈት እንደማትፈቅድ አስታውቃለች።

    ከቅድመ ሁኔታዎቹ መካከል የኢኮኖሚ ማዕቀቦችን ማንሳት እና የታገዱ የኢራን ሃብቶችን መልቀቅ ይገኙበታል።

    ማክሰኞ ዕለት በወሽመጡ በኩል ያለፉ መርከቦች ስምንት ብቻ ናቸው። ከጦርነቱ በፊት ግን በሆርሙዝ በኩል በቀን ከ130 እስከ 140 መርከቦች ያልፉ ነበር።

    አሜሪካ በሰኔ ወር አጋማሽ ላይ በኢራን ወደቦች ላይ ጥላ የነበረውን እገዳ አንስታ የነበረ ቢሆንም ጦርነቱ ዳግም ማገርሸቱን ተከትሎ በአገሪቱ ላይ የምጣኔ ሃብት ጫና ለማሳደር በሚል ዳግም ወደ ወደቡ የሚደረግ እንቅስቃሴን አግዳለች።

    ዋሺንግተን ቀድመ ሲል ኢራን እና ኦማን በወሽመጡ አስተዳደር ላይ የሚስማሙ ከሆነ እገዳውን አነሳለሁ ብላ ነበር።

  9. አዲስ ጦርነት ከተቀሰቀሰ ኢራን የበለጠ ምላሽ በመስጠት የተራዘመ ጦርነት እንደምታካሂድ አስታወቀች

    ከፍተኛ የኢራን ወታደራዊ ባለሥልጣናት አሜሪካ ሌላ ዙር ጥቃት በአገራቸው ላይ የምትከፍት ከሆነ ከባድ ጥቃት በመሰንዘር ለተራዘመ ጦርነት እየተዘጋጁ መሆናቸውን ተናገሩ።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ከፍተኛ ባለሥልጣን ራሱል ሳናኢ-ራድ ከአሜሪካ ጋር አዲስ ጦርነት የሚቀሰቀስ ከሆነ ቴህራን “ከዚህ በፊት ከነበረው በጠነከረ ሁኔታ” ምላሽ እንደምትሰጥ አስታውቀዋል።

    ፋርስ የተባለው የኢራን ዜና ወኪል እንደዘገበው የአብዮታዊ ዘቡ ጠቅላይ አዛዥ ፖለቲካዊ ርዕዮተ ዓለም ጉዳዮች መኮንን የሆኑት ባለሥልጣን "ጠላት በአገር ውስጥ ክፍፍልን በመፍጠር እና የኢኮኖሚ ጫና በማሳደር ተቃውሞዎችን መፍጠር እንደሚችል በማሰብ ጥረት እያደረገ ነው” ብለዋል።

    በተጨማሪም የኢራን ሠራዊት ምክትል ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም አሊሬዛ ሼክ በበኩላቸው የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ “ለተራዘመ ጦርነት” እና ቀጣይነት ላለው ዘመቻ ዝግጁ መሆኗን ተናግረዋል።

    እንዲሁም የኢራን የጦርነት መርኅ ግልጽ ከሆነው የመከላከል አቋም ወደ “ጥቃትን ቀድሞ ማስቀረት እና ማጥቃት” መሸጋገሩን እንዲሁም የበለጠ ሚሳዔል እና ድሮን የማምረት አቅምን ቀጣይነት ላለው ዘመቻ ወሳኝ መሆኑን አመልክተዋል።

    በሳምንታት ውስጥ ይጠናቀቃል የተባለው አሜሪካ በኢራን ላይ የከፈተችው ጦርነት ሞቅ ቀዝቀዝ እያለ ወራትን ያስቆጠረ ሲሆን፣ በድርድር እንዲያበቃ ለማድረግ ጥረት እየተደረገ ነው።

  10. ኢራን አሜሪካ በሆርሙዝ ላይ ሙሉ ቁጥጥር አለኝ ማለቷን “መሠረተ ቢስ” ስትል አጣጣለች

    ኢራን ሐሙስ ዕለት አሜሪካን የሆርሙዝ ወሽመጥን ሙሉ በሙሉ ተቆጣጥሬያለሁ ማለቷን “መሠረተ ቢስ ውሸት” ስትል ውድቅ አደረገች።

    የዓለም አንድ አምስተኛ ነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ የሚተላለፍበት ይህ ቁልፍ የውሃ መስመር በቴህራን ቁጥጥር ስር እንደሆነም ጨምራ አስታውቃለች።

    የኢራን ጦር አዛዥ በአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ኢሪብ ላይ በተላለፈ መግለጫቸው “አሜሪካ በሆርሙዝ ወሽመጥ መርከቦች ማለፋቸውን በሚመለከት የምትናገረው ውሸት የአገሪቱ ጦር አቅም ማጣቱን እና ግራ መጋባቱን የሚያንጸባርቅ፣ ሐሰት እና መሠረተ ቢስ ነው” ብለዋል።

    “የሆርሙዝ ወሽመጥ እንደበፊቱ ሁሉ በኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ሙሉ አስተዳደርና ቁጥጥር ስር ሆኖ ይቀጥላል” ሲሉ የጦሩ ቃል አቀባይ ተናግረዋል።

    ቃል አቀባዩ አክለውም “ማንኛውም የንግድ መርከብ ወይም የነዳጅ ማመላለሻ መርከብ የኢራን ጠንካራ የጦር ኃይል ፈቃድ እና ቁጥጥር ሳይኖር የባህር ወሽመጥን በሰላም አያልፍም ወይም አይችልም” ብለዋል።

  11. ሴቶችን ወደ መኖሪያ ቤታቸው በማምጣት የተከሰሱት የፈረንሳይ አምባሳደር የሥነ ምግባር እርምጃ ሊወሰድባቸው ነው

    ፈረንሳይ የሥነ-ምግባር ጉድለት ፈጽመዋል የሚል ክስ በቀረበባቸው የማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ከፍተኛ ዲፕሎማቷ ላይ የማጣራት እርምጃ ጀምራለች።

    በአምባሳደሩ ላይ የቀረበው ክስ በርካታ ሴቶችን ወደ መኖሪያ ቤታቸው በማምጣት ከተወሰኑት ጋር ወሲብ ፈጽመዋል የሚል ነው።

    አምባሳደር ብሩኖ ፉሼ እአአ ከጥር 2024 እስከዚህ ዓመት መጋቢት ወር ድረስ ባለው ጊዜ ውስጥ ፈጽመዋል ተብለው የቀረቡባቸው ክሶች ከደኅንነት ጉዳዮች ጥሰት ጋር ሊያያዙ ይችላሉ በሚል ነው የፈረንሳይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ምርመራ የጀመረው።

    አንድ የፈረንሳይ ዲፕሎማት ለቢቢሲ እንደገለፁት፥ ክሱን ተከትሎ ሚኒስቴሩ በአምባሳደሩ ላይ አስተዳደራዊ እርምጃ ለመውሰድም በሂደት ላይ ነው።

    ቢቢሲ በባንጉ የሚገኘውን የፈረንሳይ ኤምባሲ አስተያየት ጠይቋል። በፉሼ ላይ የተጀመረው የዲሲፕሊን ሂደት ምንን እንደሚያካትት እና እስከምን ድረስ እንደሚቀጥል እስካሁን የታወቀ ነገር የለም።

    ከፈረንሳይ መገናኛ ብዙኃን በተገኙ ዘገባዎች ከሆነ፣ ፉሼ በዋና ከተማዋ ባንጉ በሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው ውስጥ 30 የሚጠጉ ሴቶችን ጋብዘዋል ተብሏል።

    አንዳንዶቹ ሴቶች ሌሊቱን ሙሉ በዚያው አድረዋል መባሉ የደህንነት ስጋቶችን አስነስቷል።

    ዕድሜያቸው 65 ዓመት የሆኑት ፉሼ፣ ከ2023 ወዲህ በባንጉ የአገራቸው ዋና ዲፕሎማት በመሆን እያገለገሉ ይገኛሉ።

    እርሳቸው ፈፀሙ የተባለው የሥነ-ምግባር ጉድለት ይፋ የሆነው፣ ፈረንሳይ እና ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ተበላሽቶ የነበረውን ግንኙነታቸውን ለማሻሻል እየሰሩ ባሉበት ወቅት ነው።

  12. ተመራማሪዎች በቀላሉ የሚበሰብስ ፕላስቲክ መሥራታቸውን አስታወቁ

    በለንደን የሚገኙ ተመራማሪዎቸ በዓለማቸን የመጀመሪያው የሆነ በቀላሉ የሚበሰብስ ፊኛ መሥራታቸውን አስታወቁ።

    የኢምፔሪያል ኮሌጅ ለንደን ተመራማሪዎች የተለመደው ፊኛ ለመበስበስ እና ጎጂ ኬሚካሎችን ለመልቀቅ ዓመታት እንደሚፈጅበት ተናግረዋል።

    ነገር ግን አሁን የሠሩት ፊኛ በቀላሉ በዘጠኝ ወር ውስጥ መበስበስ እንደሚችል ገልጸዋል።

    ለምርምሩ ድጋፍ ያደረጉት ከድግሶች ተርፈው የሚጣሉ ፊኛዎች በውቅያኖስ እና በባሕር ውስጥ የሚኖሩ ፍጥረታት ላይ የሚያደርሰውን አሉታዊ ተጽዕኖ ለመቀነስ ፍላጎት ያለው ቡድን ነው ተብሏል።

    ይህ አዲሱ ፊኛ ‘ባዮሉን’ የሚል ስያሜ የተሰጠው ሲሆን፣ ከመደበኛው ፊኛ ጋር ዋጋው ተመሳሳይ መሆኑ ተገልጿል።

    ተመራማሪዎቹ አክለው ፊኛው በቀላሉ እንደሚፈነዳ አስረድተዋል።

    በኢምፔሪያል ኮሌጅ ተመራማሪ እና የሦስተኛ ዲግሪ ተማሪ የሆነችው ጁሊያና ከሚንግ “መደበኛው ፊኛዎች ጠንካራ እና ተለጣጭ እንዲሆኑ ተደርገው ነው የሚመረቱት” ብላለች።

    “ነገር ግን ይህ በቀላሉ እንዳይበሰብሱ እና አካባቢን የሚበክል መርዛማ ኬሚካሎችን እንዲለቅቁ ያደርጋል” ሲሉ አስረድተዋል።

    “የእኛ ፊኛ ግን በቀላሉ የሚበሰብሱ፣ ያለ ምንም ተጨማሪ ኬሚካል የሚመረቱ በመሆናቸው በቀላሉ ይበሰብሳሉ” ብላለች።

    ከፍተኛ ድግሶችን በማዘጋጀት የምትታወቀው ሻርለት ሜሊያ በዝነኛ ሰዎች እና ተጽዕኖ ፈጣሪዎች የተነሳ “በፊኛ የሚታጀቡ” ድግሶች እየተበራከቱ መጥተዋል ትላለች።

    ሜሊያ እነዚህ ፊኛዎች በአካባቢ ላይ የሚያደርሰው ጉዳት እንደሚያሰጋት ትናገራለች።

    ሜሊያ አሁን ተመራማሪዎቹ በቀላሉ የሚበሰብስ ፊኛ ለመሥራት የተጠቀሙበት ቁስ ለሌሎችም የፕላስቲክ ምርቶች ላይ መጠቀም እንደሚቻል ያላትን ተስፋ ገልጻለች።

  13. ዩክሬን በጥቁር ባሕር ወደብ ላይ በፈጸመችው ጥቃት የሩሲያን ዋነኛ ኤክስፖርት ጣቢያ መታች

    ዩክሬን በሩሲያ ኖቮሮሲይስክ ወደብ በፈጸመቻቸው “ግዙፍ” የድሮን እና ሚሳዔል ጥቃቶች ሁለት ዋነኛ የጥራጥሬ መላኪያ ጣቢያዎች ጉዳት እንደደረሰባቸው እና የመጨረሻው ትልቁ የሩሲያ የባሕር ኃይል ሰፈር መመታቱ ተገለጸ።

    ዩክሬን ሌሊቱን በፈጸመቻቸው ጥቃቶች የስምንት ዓመት ልጅን ጨምሮ ሦስት ሰዎች ሲገደሉ፣ 24 ሰዎች ጉዳት እንደደረሰባቸው የአካባቢው ባለሥልጣናት ተናግረዋል።

    የዩክሬን ፕሬዝዳንት ቭሎድሚር ዜሌንስኪ አገሪቱ ጦር የሩሲያን ጦር ሰፈር ለማጥቃት በካሄደው “ልዩ ኦፕሬሽን” ሮኬቶች፣ ጄት እና የባሕር ድሮኖችን ማስወንጨፉን ተናግረዋል። የእህል ጣቢያዎች ስለመመታታቸው ግን አልጠቀሱም።

    የዩክሬን ጦር ኋላ ላይ ባወጣው መረጃ፣ አራት የሩሲያ የጦር መርከቦች መመታታቸውን ገልጿል። ሩሲያ ስለዚህ ጥቃት አስተያየት አልሰጠችም።

    ፕሬዝዳንት ዜሌንስኪ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፣ “የሩሲያ ጥቃት እስከቀጠለ ድረስ ወራሪ መርከቦች እና እነርሱን የሚደግፉ መሠረተ ልማቶች በሙሉ ደኅንነታቸው የተጠበቀ አይሆንም” ብለዋል።

    አብዛኛው የሩሲያ የጥቁር ባሕር መርከቦች የሚገኙት ከአገሪቱ ትልቅ ወደቦች አንዱ በሆነው ኖቮሮሲይስክ ነው። በዚህ ወደብ የሰፈሩት መርከቦቹ ከዚህ ቀደም በሩሲያ ወረራ በተያዘው ክሪሚያ የነበሩ ሲሆን በዚያ የሚገኘው ወደብ ለዩክሬን ጥቃቶች በእጅጉ የተጋለጠ ነው።

    ረቡዕ ምሽት ጥቃት በተፈጸመበት ስፍራ የሚገኘው ዋነኛ የጥራጥሬ ንግድ ኩባንያ፣ የእህል መላኪያ ጣቢያው እንደተመታ ‘ታስ’ ለተባለው የሩሲያ ዜና ወኪል አረጋግጧል። ሌላ ኩባንያም ተመሳሳይ ጉዳት ማጋጠሙን ለሮይተርስ ተናግሯል።

    የኤክስፖርት ጭነቶችን ጉዞ ባልቲክ እና ካስፒያን ባሕሮች ላይ ወደሚገኙ ወደቦች እንዲሁም ወደ የምድር የጉዞ መስመሮች ለማዘዋር እየተሰራ መሆኑን የሩሲያ የግብርና ሚኒስቴር አስታውቋል።

    በዩክሬን ጥቃት መፈጸሙን ያልጠቀሰው ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ፣ ለውጡን የሚያደርገው ቢሆንም “ወቅታዊ የሎጂስቲክስ ገደቦችን ግምት ውስጥ በማስገባት” መሆኑን ገልጿል።

  14. ኢራን ከአሜሪካ ጋር ተደርሶ የነበረውን ጊዜያዊ የሰላም ስምምነት ለመመለስ የተጀመረ ሂደት እንደሌለ ገለጸች

    በባሕረ ሰላጤው የሚደረገውን ጦርነት የሚያስቆም ስምምነት ላይ እንዲደርሱ የሚደረገውን ጥረት በተመለከተ አሜሪካ እና ኢራን የገቡበት መፋጠጥ አሁንም መቀጠሉን የቴህራን ከፍተኛ ባለሥልጣን ለሮይተርስ ተናገሩ።

    እንደ ባለሥልጣኑ ገለጻ፣ ባለፈው ሰኔ ላይ ተደርሶ የነበረው ጊዜያዊ የሰላም ስምምነት ለማስነሳት እና ለስምምነቱ ትግበራ የጊዜ ሰሌዳ ለማስቀመጥ የሚደረገው ጥረት ላይ የታየ መሻሻል የለም።

    ማክሰኞ ዕለት በቀጠናው ይጓዙ የነበሩ መርከቦች ላይ የተፈጸመውን ጥቃት ተከትሎ፣ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በድጋሚ የኢራን መሪዎች ላይ ቁጣቸውን ገልጸዋል። ይህ ክስተትም ሁለቱ አገራት ስምምነት ላይ ይደርሳሉ የሚለውን ተስፋ ይበልጥ አደጋ ውስጥ ጥሎታል።

    ሰኔ ላይ የተፈረመው ስምምነት፣ “በሁሉም ግንባሮች የሚካሄዱ ወታደራዊ እንቅስቃሴዎች ወዲያውኑ እና በዘላቂነት እንዲቆሙ” የሚያደርግ ነበር። ይሁን እንጂ ስምምነቱ ከተፈረመ ከሳምንታት በኋላ ሁለቱ አገራት አንዳቸው በሌላቸው ላይ ጥቃት መፈጸመው ጀምረዋል።

    ይህንን ተከትሎም ፕሬዝዳንት ትራምፕ ስምምነቱ “እንዳበቃ” የተናገሩ ሲሆን የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርም ስምምነቱ “መታገዱን” ገልጿል።

    አሜሪካ፣ በስምምነቱ መሠረት ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን አልከፈትም በማለት ትከስሳለች። ቴህራን በበኩሏ፣ ዋሽንግተን የኢራን ወደቦች ላይ የተጣለው የጉዞ እገዳን ማንሳት እና የታገዱ ሀብቶችን እንደማስለቀቅ ያሉ እርምጃዎችን አለመውሰዷን ትናገራለች።

    የዜና ወኪሉ ሮይተርስ ያነጋገራቸው ኢራን ምንጭ፣ “በአሸማጋዮዎች ውይይት እየተደረገበት ያለው አንዱ ጉዳይ የአሜሪካ ወደ ጊዜያዊ ስምምነቱ መመለስ እና የገባቻቸውን ቃሎች የምስፈጽምበት የጊዜ ሰሌዳን ማስቀመጥ” እንደሆነ ገልጸዋል።

    ነገር ግን “በዚህ ጉዳይ ላይ ምንም አይነት መሻሻል የለም” ሲሉ ለዜና ምንጩ ተናግረዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕ ረቡዕ ዕለት በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፣ አሜሪካ በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ “ሙሉ ቁጥጥር” ተናግረዋል።

    ወደ ኢራን ወደቦች የሚደረግ ጉዞ ላይ የተጣለው እግድም እንዳለ በመጥቀስ “ኢራን ልታደርግ የምትችለው ምንም ነገር የለም” ብለዋል።

    ኢራን ሆርሙዝ ወሽመጥን ለማስተዳደር ያቋቋመችው የፋርስ ባሕረ ሰላጤ ወሽመጥ ባለሥልጣን ግን የትራምፕን አስተያየት አጣጥሏል። “ሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ እገዳ የለም የሚለው የአሜሪካ ባለሥልጣናት ገለጻ እና ተደጋጋሚ ልጥፍ እውነታውን አይቀይረውም” ብሏል።

    “ሆርሙዝ ወሽመጥ እንደተዘጋ ይቆያል፣ የኢራን ቅድመ ሁኔታዎች ተቀባይነት እስካላገኙ ድረስ አይከፈትም” ሲልም አስታውቋል።

  15. የተኩስ አቁም ለማራዘም ከአሜሪካ ጋር ድርድር እየተካሄደ እንዳልሆነ የኢራን ባለሥልጣን ተናገሩ

    በቴህራን እና ዋሽንግተን መካከል የተኩስ አቁም ለማራዘም ድርድር እየተካሄደ እንዳልሆነ የኢራን ከፍተኛ ባለሥልጣን መናገራቸውን ሮይተርስ ዘገበ።

    ስማቸው ያልተጠቀሰው ከፍተኛ ባለሥልጣን “የተኩስ አቁም ለማራዘም ንግግር እየተደረገ አይደለም። ምክንያቱም አሁንም የተጀመረ ነገር ስለሌለ የሚራዘምም ነገር የለም” ብለዋል።

    ከዚህ ቀደም የተደረሰውን ስምምነት አሜሪካ “በ48 ሰዓታት ውስጥ እንዳፈረሰች” እና ከቀናት በኋላ ደግሞ “ከስምምነቱ እንደወጣች” መግለጻቸውን ሮይተርስ የዜና ወኪል ዘግቧል።

    የፓኪስታን የአገር ውስጥ ሚኒስትር ሞሼን ናቅቪ ወደ ቴህራን ተጉዘው ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጋር ተገናኝተዋል።

    ጉብኝቱን ያካሄዱት ጦርነቱን ለመግታት እና የሆርሙዝ ወሽመጥን ለማስከፈት በሚደረግ የድርድር ማዕቀፍ አማካኝነት እንደሆነ ተገልጿል።

    ሰኔ ላይ አሜሪካ እና ኢራን 14 ነጥብ ያለው የመግባቢያ ስምምነት ቢፈራረሙም የተኩስ አቁሙ ተጥሷል። ስምምነቱን በመጣስም አንዳቸው ሌላቸውን ይከስሳሉ።

  16. “ኢራን የኒውክሌር ቦምብ ለመሥራት ረዥም ጊዜ ያስፈልጋታል” የሞሳድ የቀድሞ አዛዥ

    የእስራኤል የስለላ ድርጅት ሞሳድ የቀድሞው አዛዥ ዮሲ ኮኽን ኢራን በተፈጸመባት ተከታታይ ጥቃት ምክንያት የኒውክሌር ቦምብ የመሥራቅ አቅሟ መዳከሙን ተናገሩ።

    ባለሥልጣኑ የእስራኤል የስለላ ድርጅት ፎርዶ የተባለው የኢራን ከመሬት በታች የሚገኝ የኒውክሌር ተቋም ላይ በቅርበት ባደረገው ክትትል ከፍተኛ ጉዳት ስለደረሰበት መልሶ ለመገንባት ረዥም ጊዜ ያስፈልጋታል ብለዋል።

    አሜሪካ በተቋሙ ላይ ያደረሰችውን ጉዳት ሲያልሙት የነበረው “ሕልም ስኬት ነው” ሲሉ የገለጹት ቢሆንም፤ ይህንን ሲሉ ምን ማለታቸው እንደሆነ ግን ማብራሪያ አልሰጡም።

    የቀድሞው የሞሳድ አዛዥ ተቋማቸው ኢራን ለዓመታት ከመሬት በታች ስትገነባው የቆየውን ፎርዶ የኒውክሌር ተቋምን በቅርበት እና በዝርዝር ሲከታተለው እንደቆየ ማክሰኞ ዕለት በተደረገ ስብሰባ ላይ ተናግረዋል።

    ጨምረውም ኢራን 60 በመቶ የዳበረ ዩራኒየም አዘጋጅታለች በማለት ምንም እንኳን ንጥረ ነገሩ በከፍተኛ ደረጃ የዳበረ ቢሆንም የኒውክሌር ጦር መሳሪያ እንዲኖራት ያስችላል ማለት አይደለም ብለዋል።

    “60 በመቶ ዩራኒየም ማዳበር ማለት ቦምቡን ለማሥራት ገና ብዙ ርቀት መጓዝ የሚሰስፈልገው ነው” ብለዋል።

    አሜሪካ ፎርዶ የተባለውን ከተራሮች በታች የሚገኝ የኒውክሌር ተቋምን በልዩ እና ከባድ ቦምብ የደበደበችው ባለፈው ዓመት ሰኔ ወር ላይ በፈጸመችው ጥቃት ነበር።

  17. አሜሪካ በ2025 በየመን ባካሄደችው ወታደራዊ ዘመቻ 153 ሰላማዊ ሰዎች መገደላቸውን ባለሥልጣናት ገለጹ

    አሜሪካ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በ2025 ባካሄደችው ወታደራዊ ዘመቻ 153 ሰላማዊ ሰዎች መገደላቸውን እና 243 ሰዎች ደግሞ ጉዳት እንደደረሰባቸው የአገሪቱ ባለሥልጣናት ተናገሩ።

    ማክሰኞ ዕለት የፔንታጎንን የዳሰሳ ሪፖርት የተመለከቱ ባለሥልጣናት በሰላማዊ ሰዎች ላይ የደረሰው ጉዳት እአአ በ2024 ከቀረበው ቁጥር በእጅጉ የላቀ መሆኑን ገልጸዋል።

    እአአ በ2024 በአሜሪካ ዘመቻ የተገደሉ ሰላማዊ ሰዎች ቁጥር ሁለት ሲሆን ጉዳት የደረሰባቸውም ሁለት ነበሩ።

    ለኮንግረስ የተላከውና በአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ይፋ የተደረገው ይህ የፔንታጎን ሪፖርት፣ እአአ በ2025 የተመዘገቡት ሁሉም የሰላማዊ ሰዎች ሞትና ጉዳቶች በየመን ውስጥ በተፈጸሙ ሦስት የአሜሪካ ጥቃቶች ምክንያት የደረሱ መሆናቸውን ይፋ አድርጓል።

    የፔንታጎን ሪፖርት እንደሚያሳየው የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ በሚያዝያ 2025 በየመን የተፈጸሙ ሦስት የአሜሪካ ጥቃቶች በሲቪሎች ላይ ጉዳት አድርሰው ሊሆን እንደሚችል ያምናል።

    ሪፖርቱ በተጨማሪም፣ እስከ የካቲት 2026 ድረስ በየመን ውስጥ ሌሎች 15 ክስተቶች እንደነበሩና የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ መንግሥታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች በኩል በተቀበላቸው መረጃዎች ላይ በመመስረት እነዚህን ክስተቶች በአሁኑ ወቅት እየገመገመ መሆኑን ገልጿል።

    የአሜሪካ መከላከያ የጥቃቱ ዓላማ በኢራን የሚደገፉትን የሁቲ ታጣቂዎች አቅም ማዳከም ነው ብሏል።

    የፔንታጎን ሪፖርት በካሪቢያን እና ምሥራቃዊ ፓሲፊክ የፈጸማቸው ጥቃቶች ያደረሱት ጉዳት ምን ያህል እንደሆነ አልጠቀሰም።

    አሜሪካ ሚያዝያ 20/2017 ዓ.ም. በፈጸመችው እና ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ በርካታ ስደተኞች በተገደሉበት የየመን የስደተኞች ማቆያ 68 ሰዎች መገደላቸውን እና 47 መቁሰላቸውን በሁቲ የሚተዳደረው የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር ገልጾ ነበር።

  18. የሁቲ ታጣቂዎች የኢራን ጦርነት ከተጀመረ ወዲህ በፈጸሙት ከባድ የተባለ ጥቃት ስድስት ሰዎች ተገደሉ

    በዓለም አቀፍ ደረጃ ዕውቅና ያገኘው የየመን መንግሥት በኢራን የሚደግፉት ሁቲዎች በቀይ ባህር ውስጥ በሚገኝ የጭነት መርከብ ላይ ባደረሱት ጥቃት ስድስት ሰዎች መሞታቸውን እና 10 ሰዎች መቁሰላቸውን አስታወቀ።

    የትራንስፖርት ሚኒስትሩ እንዳሉት መርከቧ ከሞቻ ወደብ በስተደቡብ በሦስት የባለስቲክ ሚሳዔሎች ከተመታች በኋላ እሳት ተነስቶ አራት መርከበኞች ሞተዋል ብለዋል።

    ከሟቾቹ መካከል ሦስቱ ፓኪስታናውያን ሲሆኑ አንዱ ኢንዶኔዥያዊ ባህረተኛ ነው ተብሏል።

    የየመን የባህር ዳርቻ ጠባቂዎች በኋላ ላይ እንደገለጹት ሁለተኛው የሚሳዔል ጥቃት የሕይወት አድን ሠራተኞችን ዒላማ አድርጓል ብለዋል።

    ሁቲዎች የሳዑዲ አረቢያ ወታደራዊ መሣሪያዎችን የጫነች መርከብ እንደመቱ ተናግረዋል። እስራኤል እና አሜሪካ የካቲት 21/2018 ዓ.ም. በኢራን ላይ ጦርነት ከከፈቱ ወዲህ ሁቲዎች በመርከብ ላይ የፈጸሙት የመጀመርያው ከባድ ጥቃት መሆኑ ተገልጿል።

    የሁቲታ ጣቂዎች ባለፈው ወር የሳዑዲ መርከቦች በቀይ ባሕር ላይ እንዳይተላለፉ እገዳ ከጣሉ በኋላ በመርከብ ላይ ጥቃት መሰንዘር ጀምረዋል።

    በመካከለኛው ምሥራቅ ያለው ጦርነት ከአምስት ወራት በላይ እንደቀጠለ ነው።

    በቀጣናው የተፈጠረው አለመረጋጋት እየተባባሰ በመጣበት በዚህ ወቅት ሁቲዎች በቀይ ባሕር በኩል የሚያልፉ የሳዑዲ መርከቦችን እና የነዳጅ ማከማቻዎችን ማጥቃት ጀምረዋል።

    ቢቢሲ የተመለከተው እና ትክክለኛነቱን ያጣራው ምስል፣ በየመን ዳርቻ ወደ ቀይ ባሕር መግቢያ ላይ በባብ ኤል መንደብ ወሽመጥ ጉዳት የደረሰበትን መርከብ ያሳያል።

  19. የሊባኖስ ፓርላማ በአገሪቱ የሞት ቅጣት እንዲቀር ወሰነ

    ሊባኖስ የሞት ቅጣትን በማቆም በመካከለኛው ምሥራቅ የመጀመሪያዋ አገር እንድትሆን የሚያስችላትን ውሳኔ የአገሪቱ ፓርላማ በአብላጫ ድምፅ አሳለፈ።

    128 መቀመጫዎች ባሉት ፓርላማ፣ አብዛኛዎቹ አባላት የሞት ቅጣት እንዲቀር የቀረበውን የውሳኔ ሃሳብ በመደገፍ ማክሰኞ ዕለት ድምፍ ሰጥተዋል። የሄዝቦላህ የፓርላማ ተወካዮች ግን ውሳኔውን ተቃውመዋል።

    ሕጉ ተግባራዊ ለመሆን ለፕሬዚዳንት ጆሴፍ አውን ከመተላለፉ በፊት ወደ ካቢኔው ይላካል። መንግሥት ለሕጉ ያለውን ይሁንታ አስቀድሞ ገልጿል።

    ምንም እንኳን በሊባኖስ ፍርድ ቤቶች የሞት ፍርድ መስጠታቸውን ቢቀጥሉም እአአ ከጥር 2004 ጀምሮ የሞት ፍርድ ተፈጻሚ እነዲሆን አላደረገችም። የመብት ተሟጋቾች ከ78 በላይ ሰዎች አሁንም የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸው እነደሚገኙ ይናገራሉ።

    በአዲሱ ሕግ መሠረት የሞት ቅጣት በእድሜ ልክ እስራት እና በከባድ የጉልበት ሥራ ይተካል። ሆኖም ግን ሕጉ አዲሱ ቅጣት እንዴት ተግባራዊ እንደሚሆን በዝርዝር አላስቀመጠም።

    ከባድ የጉልበት ሥራ በሊባኖስ ሕግ ውስጥ ያለ ቢሆንም በቅርብ ዓመታት ውስጥ እምብዛም ተግባራዊ አልተደረገም። የአገሪቱ የፋይናንስ ቀውስ እና የተጨናነቁ እስር ቤቶች የአገሪቱን ሀብትና አቅም ገድበዋል።

    ፓርላማው ድምጽ የሰጠው የሲቪል ማኅበረሰብ ቡድኖች እና ጠበቆች የሞት ቅጣትን ከሊባኖስ ሕግ ለማስወገድ ለዓመታት ዘመቻ ካደረጉ በኋላ ነው።

    "ወንጀልን በወንጀል መፍታት ወይም ዓመፅን በዓመፅ ማስቆም አንችልም" ስትል ከሊባኖስ የሲቪል ማኅበረሰብ ቡድኖች መስራቾች አንዷ የሆነችው ኦራጊት ዩናን ለቢቢሲ ተናግራለች።

  20. ክርስቲያኖ ሮናልዶ ከረዥም ጊዜ ፍቅረኛው ጆርጂና ሮድሪጌዝ ጋር ጋብቻውን ፈጸመ

    የእግር ኳስ ኮከብ የሆነው ክርስቲያኖ ሮናልዶ ከረጅም ጊዜ ፍቅረኛው ሞዴል እና ተፅዕኖ ፈጣሪዋ ጆርጂና ሮድሪጌዝ ጋር በፖርቹጋል ጋብቻቸውን መፈጸመቸው ተገለጸ።

    ፖርቹጋላዊው አጥቂ በኢንስታግራም ገፁ ላይ የጋብቻ ቀለበት ያደረጉ ሁለት እጆችን የሚያሳይ ምስል አጋርቷል።

    የፖርቹጋል ሚዲያዎች የዓመቱ ሠርግ ሲሉ የዘገቡት ይህ የጋብቻ ሥነ ስርዓት የተከናወነው ነሐሴ 5 2018 ዓ.ም. በሊዝበን አቅራቢያ በምትገኘው ካስኬይስ የባህር ዳርቻ ከተማ ነው።

    በሠርጉ ላይ አምስት ልጆቻቸውም መገኘታቸው ተዘግቧል።

    ሮናልዶ ይህንን ዜና በኢንስታግራም ገፁ ባጋራ በ30 ደቂቃ ውስጥ ከ3 ሚሊዮን በላይ ሰዎች አስተያየታቸውን በተለያየ መንገድ ሰጥተዋል።

    ጥንዶቹ ሮድሪጌዝ በምትሠራበት ማድሪድ ውስጥ በሚገኝ የጉቺ ሱቅ ውስጥ ከተገናኙ በኋላ ለ10 ዓመታት በፍቅር ቆይተዋል። ሮናልዶ በወቅቱ በስፔኑ ክለብ ሪያል ማድሪድ እየተጫወተ ነበር።

    ሮድሪጌዝ እና ሮናልዶ ባለፈው ዓመት ነሐሴ 11 ላይ መተጫጨታቸውን ይፋ አድርገው ነበር።

    በወቅቱ ሮድሪጌዝ በማኅበራዊ ድረ ገጿ ላይ "እሺ፣ በዚህ እና በሕይወቴ በሙሉ" የሚል ጽሑፍ ትልቅ ቀለበት ከሚያሳይ ምስል ጋር አጋርታ ነበር።

    ሮናልዶ በሊዝበን ለሚገኘው ስፖርቲንግ፣ ማንቸስተር ዩናይትድ፣ ሪያል ማድሪድ፣ ጁቬንቱስ፣ በሳዑዲ አረቢያ ለአል ናስር በተጫወተበት ዓመታት ወደ 1,000 የሚጠጉ ጎሎችን አስቆጥሯል።

    በቅርቡ በስድስተኛው የዓለም ዋንጫ ላይ የተጫወተው ሮናልዶ ይህም በወንዶች የፍጻሜ ውድድር ላይ በመሳተፍ ክብረ ወሰን ሆኖ ከአርጀንቲናው ሊዮኔል ሜሲ ጋር ስሙ ሰፍሯል።