ኢራን በኳታር የተመቱ የተዋጊ ጄት አብራሪዎቿ እንዲለቀቁ ጠየቀች

ኢራን ከአሜሪካ ጋር የሚደረገው ጦርነት በተጀመረበት ወቅት በተካሄደ ወታደራዊ ዘመቻ ወቅት ሁለት ተዋጊ ጄቶች በአየር መከላከያ ከተመቱ በኋላ በኳታር የተያዙት ሦስት ፓይለቶቿ እንዲለቀቁ ጠየቀች። ሦስቱ አብራሪዎች ላለፉት ስድስት ወራት በኳታር ተይዘው መቆየታቸውን ኢራን ለዓለም አቀፉ የቀይ መስቀል ኮሚቴ ኃላፊ በጻፈችው ደብዳቤ አስታውቃለች።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. አረብ ሊግ እስራኤል በሊባኖስ የምትፈጽመው ጥቃት ጦርነቱ እንዲስፋፋ ያደርጋል ሲል አስጠነቀቀ

    ለ11 ሰዎች ሞት ምክንያት የሆነውን የቅዳሜ ዕለት የእስራኤል ጥቃት “አደገኛ የውጥረት መባባስ” ሲል የጠራው አረብ ሊግ፣ አገሪቱ በደቡባዊ ሊባኖስ የምታደርሰው ጥቃት መቀጠሉን አወገዘ።

    የአረብ ሊግ ቃል አቀባይ ባወጡት መግለጫ፣ ከቅዳሜ ጠዋት ጀምሮ የተፈጸሙት የእስራኤል ጥቃቶች “የሊባኖስን ሉዓላዊነት በግልጽ የጣሱ” መሆናቸውን አስታውቀዋል። “እየተካሄደ ያለውን ጦርነት ለመፍታት እና ወረራውን ለመቋጨት የሚደረጉ ማናቸውም ጥረቶች ስጋት ላይ የሚጥል አደገኛ የውጥረት መባባስ ነው” ብለዋል።

    ቃል አቀባዩ በመግለጫቸው፤ የእስራኤል ፖሊሲዎች እና እርምጃዎች “ወራሪው አካል ግጭቱን ለማራዘም፣ ድርድሮችን ለማሰናከል እና መሬት ላይ አዲስ እውነታን ለመጫን ያለውን ፍላጎት በግልጽ የሚያሳዩ ናቸው” ሲሉ ወቅሰዋል።

    የእስራኤል እርምጃ “ሙሉ በሙሉ ተቀባይነት እንደሌለው እና ውድቅ” መሆኑንም ጠቅሰዋል።

    ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ፣ በተለይም አሜሪካ የእስራኤልን “የጦርነት ማሽን” እስካላስቆሙ እንዲሁም አገሪቱ ለተመድ የጸጥታው ምክር ቤት ውሳኔ እንድትገዛ ካላስገደዱ በስተቀር፣ ግጭቱ ሊስፋፋ እንደሚችል አስጠንቅቀዋል።

    በአውሮፓውያኑ 2006 የጸደቀው ይህ ውሳኔ፣ በእስራኤል እና ሄዝቦላህ መከካል ሙሉ ግጭት ማቆም እንዲደረግ የሚጠይቅ ነው።

    እስራኤል ትናንት በደቡባዊ ሊባኖስ በፈጸመችው ጥቃት ሦስት ሕፃናትን ጨምሮ 11 ሰዎች መገደላቸውን የሊባኖስ ባለሥልጣናት ተናግረዋል። ከዚህ ጥቃት በኋላ በርካታ ነዋሪዎች ከደቡባዊ ሊባኖስ መሸሽ ጀምረዋል።

  2. ሩሲያ በመላው ዩክሬን በከፈተችው አዲሱ ዙር ጥቃት አምስት ሰዎች ተገደሉ

    ዩክሬን ውስጥ በተከፈተው አዲስ ዙር የሩሲያ ጥቃት፣ ቢያንስ አምስት ሰዎች ሲገደሉ፣ ከ10 በላይ ሰዎች መቁሰላቸውን ባለሥልጣናት ተናገሩ።

    ሩሲያ የሲቪል መሠረተ ልማቶችን ዒላማ አድርጋለች በማለት የከሰሱት የዩክሬን ፕሬዝዳንት ቭሎዲሚር ዜሌንስኪ፣ በዋና ከተማዋ ኪዬቭ የተመቱ ስፍራዎች ላይ የድንገተኛ አደጋ አገልግሎት እየቀረበ መሆኑን ገልጸዋል።

    የሩሲያ መዲና ሞስኮ ከንቲባ በበኩላቸው፣ ዩክሬን ሌሊት ላይ 600 የገደማ ድሮኖችን ከተማው ላይ ማዝነቧን ገልጸዋል። ዋልድቤሪስ የተባለው የሩሲያ የኦንላይን ችርቻሮ ንግድ ኩባንያ መጋዘንም ጥቃት ደርሶበታል።

    ከቅርብ ሳምንታት ወዲህ ሩሲያ በመላው ዩክሬን የምትፈጽመውን የአየር ጥቃት አጠናክራለች። ዩክሬምን በተመሳሳይ የሩሲያን ወታደራዊ አቅርቦት ለማስተጓጎል በማለም በአገሪቱ የሎጂስቲክስ ማዕከላት ላይ የምትፈጽማቸውን ጥቃቶች ጨምራለች።

    ቅዳሜ ሌሊት ላይ በኪዬቭ ከተማ በደረሰው ጥቃት ሕፃን ልጅን ጨምሮ ቢያንስ ስድስት ሰዎች መቁሰላቸውን ከንቲባው ተናግረዋል።

    የ44 ዓመት ግለሰብ በፍርስራሽ ውስጥ ሕይወቱ አልፎ መገኘቱን፣ ሌላ ሰው መገደሉን እንዲሁም 14 የብረት ፋብሪካ ሠራተኞች መጎዳታቸውን ገልጸዋል። ዛፖሪዥያ ከተማ ውስጥ ደግሞ አንድ ቤት በመውደሙ ዕድሜያቸው በ60ዎቹ ውስጥ የሆኑ ሁለት ሰዎች ተገድለዋል።

    ፕሬዝዳንት ዜሌንስኪ፣ ክሬመንቹክ እና ክሪቪ ሪህ የተባሉት ከተሞች የተመቱት በባለስቲክ ሚሳዔል መሆኑን ተናግረዋል። “ሩሲያውያን በባለስቲክ ሚሳዔሎቻቸው መድረስ በሚችሉበት ቦታ ሁሉ የሲቪል መሰረተ ልማቶችን ይመታሉ” ሲሉም ወንጅለዋል።

    ሩሲያ በበኩሏ የቅዳሜ ምሽቱ የኪዬቭ ጥቃት ያነጣጠረው፣ የዩክሬንን ፍላሚንጎ ሚሳዔል ክፍሎችን በሚያመርተው ‘ፋየርፖይንት” የተባለ ተቋም እና የድሮን አካላትን በሚሰራ ፋብሪካ ላይ እንደሆነ አስታውቃለች።

  3. እስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ በፈጸመችው ጥቃት ሦስት ሕፃናትን ጨምሮ 11 ሰዎች ተገደሉ

    ሰኔ ላይ የተኩስ አቁም ስምምነት ከተፈረመ ወዲህ ከታዩት እጅግ አስከፊው በተባለው የእስራኤል ጥቃት፣ ደቡባዊ ሊባኖስ ውስጥ ሦስት ሕፃናትን ጨምሮ 11 ሰዎች መገደላቸውን ባለሥልጣናት ተናገሩ።

    የሊባኖስ ጠቅላይ ሚኒስትር፣ ከአገሪቱ ዋና ከተማዋ ቤይሩት 70 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ከሚገኘው አንሳር ወጣ ብሎ በተሰራ መኖሪያ ቤት ላይ በተፈጸመው ጥቃት 11 ሰዎች መገደላቸውን ገልጸዋል።

    ከተገደሉት መካከል ሦስት ሕፃናት እና ሁለት ሴቶች እንደሚገኙበት የአገሪቱ የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት በኢራን ድጋፍ የሚደረግለት የሺዓ ታጣቂ ቡድን የሆነው ሄዝቦላህ አንድ አዛዥን መገደሉን አስታውቋል።

    አዛዡ “እንደ የሰው ጋሻ የተጠቀማቸው” ቤተሰቦቹ ስፍራው ላይ እንደነበሩ እና በጥቃቱ “መጎዳታቸውን” ጦሩ ገልጿል።

    ቅዳሜ ዕለት በዴር አል-ዛህራኒ ከተማ በደረሰ ሌላ ዙር ጥቃት አራት ሰዎች ሲገደሉ አምስት ሌሎች ደግሞ መቁሰላቸውን የሊባኖስ ጤና ሚኒስቴር ገልጿል።

    የሊባኖስ ባለሥልጣናት እንደሚናገሩት፣ የአንሳር ከተማው ጥቃት የተፈጸመው የተፈናቀሉ ቤተሰቦች የሚኖሩበት ስፍራ ላይ ነው።

    ማኅበራዊ ሚዲያ በተሰራጨ አንድ ቪዲዮ ላይ የሳይረን ድምጽ ከሚሰማበት የአንድ መንደር ጎዳናዎች ከፍተኛ ጭስ ወደላይ ሲወጣ አሳይቷል።

    የሊባኖስ ጠቅላይ ሚኒስትር ናዋፍ ሳላም የተገደሉት ሰባት ሲቪሊያን “የወታደራዊ መሰረተ ልማት” አካል እንዳልነበሩ በመግለጽ ጥቃቱን አውግዘዋል።

    “እስራኤል ይህንን ግጭት የማባባስ እርምጃ ማቆም አለባት” ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ “የሕዝባችን ደኅንነት እና መሬታቸው ላይ በሕይወት የመኖር መብታቸው ለድርድር አይቀርብም” ሲሉ ተናግረዋል።

    የእስራኤል ጦር ኋላ ላይ ባወጣው መግለጫ፣ አንሳር ውስጥ ጥቃት እንዲፈጸም ምክንያት የሆነው ክስተት የተፈጠረው አሊ አል ጣሂር ሪጅ በተባለው ስፍራ እንደሆነ ጠቅሷል። ደቡብ ምሥራቃዊ ሊባኖስን ወደታች መመልከት የሚያስችለው ይህ ስትራቴጂካዊ ስፍራ፣ በጦርነቱ ከፍተኛ ግጭት የተካሄደበት ቦታ ነው።

    የእስራኤል ጦር የራድዋን ኃይል የተባለው የሄዝቦላህ ወታደራዊ ክፍል አዛዥ እንደሆነ የገለጸው አሊ ሳሚር አል ሃጅ ሀሰን በዚህ ጥቃት መገደሉን አስታውቋል።

    “በእስራኤል ወታደሮች ላይ የሽብር ጥቃቶችን የማስፋፋት ተግባር ላይ ተሳታፊ የነበሩ ሌሎች ተጨማሪ አሸባሪዎች ከእርሱ ጋር ተወግደዋል” ብሏል።

    “ጥቃቱ ያተኮረው በዓለም አቀፍ ሕግ መሠረት ሕጋዊ ዒላማ በነበረው ሀሰን ላይ እንጂ እንደ የሰው ጋሻ በተጠቀማቸው ቤተሰቦቹ ላይ ያነጣጠረ እንዳልነበረ” የእስራኤል ጦር ገልጿል።

    ሄዝቦላህ በበከሉ ሊባኖሳዊያን ንጹኃን ሰዎች “ሆነ ተብሎ ቤታቸው ውስጥ ዒላማ ተደርገዋል” ሲል የእስራኤልን ማብራሪያ ውድቅ አድርጓል።

  4. ኢራን በኳታር የተመቱ የተዋጊ ጄት አብራሪዎቿ እንዲለቀቁ ጠየቀች

    ኢራን ከአሜሪካ ጋር የሚደረገው ጦርነት በተጀመረበት ወቅት በተካሄደ ወታደራዊ ዘመቻ ወቅት ሁለት ተዋጊ ጄቶች በአየር መከላከያ ከተመቱ በኋላ በኳታር የተያዙት ሦስት ፓይለቶቿ እንዲለቀቁ ጠየቀች።

    አብራሪዎቹ ጃቫድ ሳሌሂ፣ አብዱል ማጂድ ዳሽቲያን እና ኢምራን ቤህሮሺያን ላለፉት ስድስት ወራት ተይዘው መቆየታቸውን ኢራን ለዓለም አቀፉ የቀይ መስቀል ኮሚቴ ኃላፊ በጻፈችው ደብዳቤ አስታውቃለች።

    ደብዳቤውን የላኩት የኢራኑ ብርጋዴር ጄነራል መሐመድ ባገርዛዴህ እንደገለጹት፣ በየካቲት መጨረሻ ጦርነቱ በተጀመረ በሦስተኛው ቀን በተደረገው ዘመቻ የተገደለው የአራተኛው ፓይለት ማጂድ ካዜሚ አስከሬን ወደ አገሩ ተመልሷል።

    ጥያቄው የቀረበላት ኳታር የኢራንን ገለጻ “ሙሉ በሙሉ ውድቅ” አድርጋዋለች። “በእነዚህ አሳሳች መግለጫዎች እንደተገረመችም” ተናግራለች።

    የኢራኑ ጄነራል መሐመድ ባገርዛዴህ እንደሚናገሩት፣ ሦስቱ አብራሪዎች በኳታር የተያዙት በአገሪቱ የሚገኝ ጦር ሠፈርን ዒላማ ባደረገ የውጊያ ተልዕኮ ወቅት፣ ከተመቱት ጄቶች ተመንጥቀው ከወጡ በኋላ ነው።

    ለዓለም አቀፉ የቀይ መስቀል ኮሚቴ ኃላፊ ሚርያና ስፖልያሪች የተጻፈው እና በኢራን መገናኛ ብዙኃን የወጣው ደብዳቤ፣ ኳታር “ከሁሉም ዓለም አቀፍ ሕጎች እና ደንቦች በተቃረነ ሁኔታ የእነዚህ እስረኞች የማይገፈፉ” መብቶች እንደጣሰች በማንሳት ይከስሳል።

    ሦስቱ አብራሪዎች ቤተሰቦቻቸውን እንዲያገኙ ወይም እንዲያነጋግሩ እንዳልተፈቀደላቸውም ደብዳቤው ጠቅሷል።

    የኳታር የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ማጄድ መሐመድ አል አንሳሪ ግን፣ በወቅቱ “የኳታርን የአየር ክልል ጥሰው ከገቡ” በኋላ ከአብራሪዎቹ ጋር ግንኙነት ለመፍጠር ቢሞከርም ምላሽ አለመገኘቱን ገልጸዋል።

    ቃል አቀባዩ በኤክስ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፣ “ዓለም አቀፍ ሕግ መሠረት ግዛታችንን ለመከላከል አስፈላጊው እርምጃ ተወስዷል” ብለዋል።

    በወቅቱ “የፓይለቶቹን አስከሬን ለመፈለግ” የተሰማሩት የኳታር የፍለጋ እና ነፍስ አድን ቡድኖች፣ “ኃላፊነታቸውን እስከ ጥግ ማከናወናቸውን” አክለዋል።

    ኳታር “የተገኘውን የአንዱን አብራሪ አስከሬን [ለኢራን] የሚተላለፍበትን መንገድ ለማቀናጀት” ከቴህራን ጋር ግንኙነት ማድረጓን ቃል አቀባዩ አስታውሰዋል። ኢራን የፍለጋ እና ነፍስ አድን ዘመቻውን ዝርዝር እንድትመረምር ለቀረበላት ጥሪ እስካሁን ምላሽ እንዳልሰጠችም ተናግረዋል።

  5. ኢራን ከአሜሪካ ጋር ውይይት ለመቀጠል “ከውሳኔ ላይ አልተደረሰም” አለች

    ኢራን ከአሜሪካ ጋር ቀጥተኛ ያልሆነ ድርድር ለመጀመር እስካሁን አልወሰነችም ሲሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሯ ተናገሩ። በአደራዳሪዎች አማካኝነት የሚደረጉ የመልዕክት ልውውጦች ወደ ድርድር እንደተመለሰች ተደርጎ ሊተረጎም እንደማይገባም አፅንዖት ሰጥተዋል።

    አባስ አራግቺ በፓኪስታን አደራዳሪነት በሰኔ ወር በሁለቱ አገራት መካከል የተፈረመውን የ60 ቀናት የተኩስ አቁም ስምምነት ማራዘም እንደሚያስፈልግ የሚገልጹ ሪፖርቶችን ውድቅ አድርገዋል።

    “በኢስላማባድ የመግባቢያ ሰነድ ውስጥ የተካተቱት የጦርነቱ ማብቃት እንጂ የተኩስ አቁም ስምምነት አልነበረም።” ሲሉ ለኢራን ኢስና የዜና ወኪል ተናግረዋል።

    “ዩናይትድ ስቴትስ ስምምነቱን ጥሳለች፤ እናም ጦርነቱ ዳግም ቀጥሏል። ስለዚህ የ60 ቀናት የተኩስ አቁም ስምምነት ማራዘም አስፈላጊ አይደለም።” ብለዋል።

    በመግባቢያ ሰነዱ ውስጥ የተጠቀሰው የ60 ቀናት የተኩስ አቁም የመጨረሻ ስምምነት ላይ ለመድረስ የሚደረጉ ድርድሮች ላይ ለማተኮር እንደሆነ ተናግረዋል።

    “ኳታርም ሆነ ፓኪስታን መልዕክት መለዋወጣቸውን እና ከእኛ ጋር ግንኙነታቸውን ቀጥለዋል፣ ይህ ማለት ግን ድርድር ማለት አይደለም።” ሲሉም አስረድተዋል።

    “ከዩናይትድ ስቴትስ ጋር ንግግር ለመቀጠል እስካሁን ምንም ዓይነት ውሳኔ አልተወሰነም።”

    አራግቺ ኢራን ከኦማን ጋር የምታደርገው ድርድር መቀጠሉን ተናግረው፤ ከዋሽንግተን ጋር ከሚደረጉ ማናቸውም ውይይቶች ፈጽሞ የተለየ ነው ብለዋል።

    ውይይቱን ቀደም ሲል የነበሩት የመርከቦች መተላለፊያ መንገዶች ተስማሚ ስላልነበሩ በሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ በኩል አዳዲስ የመርከብ መስመሮችን ማቋቋም ላይ ያተኮረ የቴክኒክ ባለሙያዎች ድርድር እንደሆነ ገልጸዋል።

    “በአሁኑ ጊዜ ወደፊት ወደ ዘላቂ መተላለፊያነት የሚቀየር ጊዜያዊ መንገድ እየነደፍን ነው” በማለት ድርድሩ ያለበትን ሁኔታ አስረድተዋል።

    ከሁለቱም አገሮች የተውጣጡ ባለሙያዎች እንዲሁም የኢራን የጦር ኃይሎች በድርድሩ ላይ እንደሚሳተፉ እና ውይይቱ በቅርቡ እንደሚጠናቀቅ አክለዋል።

    አራግቺ በመርከብ መስመሮች ላይ የሚደረጉ የቴክኒክ ድርድሮች ከባሕር ወሽመጥ እንደገና መከፈት ጋር መምታታት እንደሌለባቸው አፅንዖት ሰጥተዋል።

    “መንገዱ አንዴ ከተወሰነ በኋላ የሆርሙዝ ወሽመጥ ዳግም መከፈት ዩናይትድ ስቴትስ ማክበር ካለባት ሌሎች ቅድመ ሁኔታዎች ጋር የሚያያዝ ነው” ብለዋል።

  6. የሁቲ ታጣቂዎች የቀይ ባሕር ወደብ ላይ ጥቃት መፈጸማቸው ተነገረ

    ቅዳሜ ዕለት በኢራን የሚደገፉት ሁቲዎች በዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ እውቅና ያለው መንግሥት የሚቆጣጠረውን የቀይ ባሕር ወደብ ማጥቃታቸውን እና አንድ የደኅንነት አባል መግደላቸውን የየመን ጦር ገለጸ።

    የጦሩ ቃል አቀባይ ኮሎኔል ማጂድ አል ናዚሊ በሰጡት መግለጫ አርብ ምሽት ሁቲዎች ወደ ሞቻ ወደብ ስድስት ባሊስቲክ ሚሳዔሎች መተኮሳቸውን ተናግረዋል።

    ቃል አቀባዩ “ለሰላማዊ ሰዎች ወሳኝ የሆነ ተቋም ላይ ያነጣጠረ አዲስ የአሸባሪዎች ጥቃት” ሲሉ በገለጹት በዚህ ጥቃት ስምንት ሰዎች መጎዳታቸውን እና ሁለት ሰዎች የደረሱበት አለመታወቁን ጨምረው አስታውቀዋል።

    አርብ እለት እንዲሁ ሁቲዎች ወደ ወደቡ ስድስት ባሊስቲክ ሚሳዔሎችን አስወንጭፈው አራት ሰላማዊ ሰዎችን መግደላቸውን የየመን መንግሥት ገልጿል።

    የየመን ጦር የሁቲዎች ጥቃት የሰላማዊ ሰዎችን እንዲሁም በወደቡ የሚገኙ የሕዝብ ሃብቶችን ዒላማ ማድረጉን ይናገራል።

    ሁቲዎች በሞቻ ወደብ የሚገኝ የጦር ሠራዊትን፣ መሣሪያን እና የጦር መርከብን ማጥቃታቸውን ተናግረዋል።

    የየመን ወታደራዊ ምንጭም ሁቲዎች ወደ ሞቻ ወደብ እና በምዕራባዊው የባሕር ዳርቻ በሚገኙ የሲቪል ተቋማት ላይ 44 ድሮኖች መተኮሳቸውን፤ የአገሪቱ መከላከያም ከእነዚህ ውስጥ 15ቱን መትቶ መጣሉን ለመገናኛ ብዙኃን ተናግረዋል።

    በሁቲ አማጺያን እና በየመን መንግሥት መካከል ያለው ውጥረት እየተባባሰ የመጣው፣ አሜሪካ ከኢራን ጋር በምታካሄደው ጦርነት የተነሳ ቀጣናዊ ውጥረቶች እየከረሩ በመጡበት ወቅት ነው።

    በኢራን የሚደገፉት የሁቲ ታጣቂዎች የዩናይትድ ስቴትስና የእስራኤል ተቃዋሚዎች ናቸው።

    ሁቲዎች አሜሪካ በኢራን ላይ ለምትፈጽመው ጥቃት አጸፋ ለመስጠት የሳዑዲ አረቢያ መርከቦች በቀይ ባሕር ላይ እንዳያልፉ እግድ ጥለዋል።

    በኢራን የሚደገፈው ታጣቂ ቡድን እገዳውን የጣለው ሳዑዲ ሁቲ የሚቆጣጠራቸውን የሰሜን ምዕራብ የመን ወደቦችን እና አየር ማረፊያዎችን በመዝጋቷ የተወሰደ የበቀል እርምጃ እንደሆነ ገልጿል።

    የየመንን ዋና ከተማ ሰነዓን ጨምሮ ሰሜናዊውን እና ሌሎችንም የአገሪቱን ግዛቶች የሚቆጣጠሩት ሁቲዎች የተጠናከረ ወታደራዊ ኃይል እና የጦር መሳሪያ እንዳላቸው ከዚህ ቀደም በእስራኤል እና በሳዑዲ ላይ በፈጸሟቸው ጥቃቶች አሳይተዋል።

  7. በኢንዶኔዢያ በተከሰተ ርዕደ መሬት ቢያንስ 38 ሰዎች ሞቱ

    በኢንዶኔዢያ በተከሰተ ከባድ ርዕደ መሬት ቢያንስ 38 ሰዎች መሞታቸውን የአገሪቷ የአደጋ መከላከያ ድርጅት ገለጸ።

    ቅዳሜ ዕለት ጠዋት በፍሎርስ ግዛት የተከሰተው ርዕደ መሬቱ በሬክተር ስኬል 7.7 ማግኒቲዩድ የተለካ ነው።

    በፍርስራሽ ውስጥ የተቀበሩ ሰዎችን ለማውጣት የሚደረገው ፍለጋ እና የነፍስ አድን ሥራ የቀጠለ ሲሆን የሟቾች ቁጥርም እየጨመረ ነው።

    በተፈጥሯዊ አደጋው ከሞቱት በተጨማሪም በርካታ ሰዎች የተለያየ መጠን ጉዳት ደርሶባቸዋል።

    በርዕደ መሬቱ እና ቀጥለው ባጋጠሙት በርካታ ንዝረቶች በክልሉ ያሉ ሕንፃዎችም ፈራርሰዋል።

    የአገሪቷ ሚቲዮሮሎጂ እና ጂኦፊዚክስ ኤጀንሲ እንደገለፀው ርዕደ መሬቱ ፍሎርስ ደሴትን የመታው ቅዳሜ ጠዋት 1፡00 ሰዓት ላይ ሲሆን 15 ኪሎ ሜትር ጥልቀት አለው።

    የመሬት መንቀጥቀጥ ጥልቅ ባልሆነ ሥፍራ ሲያጋጥም ብዙ ጉዳትን ያስከትላል።

    ከርዕደ መሬቱ በኋላ በአካባቢው በ6.1 ማግኒቲዩድ የተለኩ ጠንካራ ንዝረቶችም ተሰምተዋል።

    የርዕደ መሬቱ ማዕከል በሆነችው ግዛት በምዕራብ አቅጣጫ የምትገኘው ሩተንግ ከተማ ነዋሪ የሆኑት የዩኒቨርሲቲ አስተማሪ ዩሊያን ጁተታ ኢካሊያ “ እንደዚህ ዓይነት ከባድ የመሬት መንቀጥቀጥ ተሰምቶኝ አያውቅም” ሲሉ ለኤኤፍፒ የዜና ወኪል ተናግረዋል።

    “ልጆች እየዘለሉ የሚጫወቱበት ማስፈንጠሪያ (ስፕሪንግ) ላይ እንደሆንን ነበር የተሰማኝ ። በጣም አስፈሪ ነበር።” ብለዋል።

    ወጣ ብሎ በሚገኘው ተራራማ ሥፍራ በደረሰው አደጋው ያጋጠመውን አጠቃላይ ውድመት ለመገምገምም ጊዜ ይወስዳል ተብሏል።

    ሆኖም የመጀመሪያ ደረጃ ሪፖርቶች 54 ቤቶች፣ አምስት የጤና መሠረተ ልማቶች፣ ሦስት የእምነት ተቋማት፣ ስድስት የመንግሥት ሕንፃዎች፣ የትምህርት ተቋም እና መጋዘን በከፍተኛ መጠን መውደማቸውን አመልክተዋል።

  8. እስራኤል በደቡባዊ ሊባኖስ በፈጸመችው አዲስ ጥቃት ሰባት ሰዎች ሲገደሉ፣ ሦስት ቆሰሉ

    የእስራኤል ጦር ቅዳሜ ማለዳ በደቡባዊ ሊባኖስ በሚገኝ አንድ ቤት ላይ በፈጸመው የአየር ድብደባ ቢያንስ ሰባት ሰዎች መገደላቸውንና ሌሎች ሦስት ሰዎች ደግሞ መቁሰላቸውን የሊባኖስ ብሔራዊ የዜና ወኪል ዘገበ።

    የእስራኤል የጦር አውሮፕላኖች በናባቲዬህ ውስጥ፣ ከአንሳር ከተማ ዳርቻ እና ወደ ዛራሪዬህ ከተማ በሚወስደው አቅጣጫ ላይ የሚገኝ ቤት መትተው እንዳወደሙ ኤጀንሲው ጠቅሷል።

    የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች ከፍርስራሹ ውስጥ የሞቱ እና የተጎዱ ሰዎችን በማውጣት ወደ ናባቲዬህ ሆስፒታል ወስደዋቸዋል።

    ጥቃቱ በእስራኤል እና በሊባኖስ መካከል የተኩስ ማቆም ስምምነት ከተደረሰ ወዲህ የተፈጸመ የመጀመርያው ጥቃት ነው ተብሏል።

    በተጨማሪም፣ የእስራኤል የጦር አውሮፕላኖች ናባቲዬህ አል-ፋውቃ ዳርቻ ላይ በሚገኘው የአሊ አል-ታሄር ኮረብታ ላይ ያነጣጠሩ ተከታታይ የአየር ጥቃቶችን ማድረሳቸውን ኤጀንሲው ዘግቧል።

    በአሜሪካ ድጋፍ ሰኔ 26 በቤይሩት እና በቴል አቪቭ መካከል ስምምነት ቢፈረምም፣ እስራኤል በሊባኖስ ላይ ጥቃት መፈጸሟን ቀጥላለች።

    እስራኤል ሊባኖስ ላይ ጥቃት መሰንዘር የጀመረችው ሄዝቦላህ በኢራን ላይ የተከፈተውን ጦርነት በመቃወም ሮኬቶችን ማስወንጨፍ በመጀመሩ ነው።

    በእስራኤል ጥቃት 4 ሺህ 335 ሊባኖሳውያን ሲገደሉ 12 ሺህ 277 ደግሞ መቁሰላቸውን የአገሪቱ ጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።

    በእስራኤል እና በሊባኖስ መካከል የተፈረመው ስምምነት ሄዝቦላህን ጨምሮ ሌሎች የታጠቁ ቡድኖች ትጥቅ እንዲፈቱ ይጠይቃል።

    በሂደትም እስራኤል ከያዘቻቸው የሊባኖስ ግዛቶች ቀስ በቀስ ስትወጣ ቦታዎቹን የአገሪቱ ጦር እንደሚረከብ በስምምነቱ ሰነድ ላይ ሰፍሯል።

    እስራኤል እአአ በ2023 እና 2024 መካከል በተደረገው ጦርነት እንዲሁም ከዚያ በፊት በነበሩ ግጭቶች ወቅት በደቡባዊ ሊባኖስ ውስጥ አንዳንድ አካባቢዎችን ተቆጣጥራ ትገኛለች። በአሁኑ ጥቃት ወቅትም ከ10 ኪሎ ሜትር በላይ ወደ ሊባኖስ ግዛት ዘልቃ ገብታለች።

  9. ዶናልድ ትራምፕ “በቅርቡ” ሆርሙዝ የአሜሪካ ግዛት አካል እንደሚሆን ተናገሩ

    ከኢራን ጋር ያለው ግጭት እየተባባሰ ባለበት በአሁኑ ሰዓት የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ኢራን ከተሸነፈች በኋላ ሆርሙዝ የአሜሪካ ግዛት አካል እንደሚሆን ተናገሩ።

    አርብ ዕለት በኒውዮርክ ለደጋፊዎቻቸው ንግግር ያደረጉት ትራምፕ፣ አሜሪካ በቅርቡ ለዓለም የነዳጅ፣ የተፈጥሮ ጋዝ እና የማዳበሪያ አቅርቦት ወሳኝ የሆነውን የሆርሙዝ የባሕር መስመር የግዛቷ አካል እንደምታደርግ ገልጸዋል።

    "አሁን ላይ ከፍተኛ ሽንፈት እየገጠማት ያለችውን ኢራንን ድል አድርገን ከጨረስን በኋላ፣ በቅርቡ የሆርሙዝ ወሽመጥን የአሜሪካ ግዛት አድርጌ አውጃለሁ" ሲሉ ትራምፕ በኒው ዮርክ ግዛት፣ ጋርደን ሲቲ በሚገኝ የፖሊስ አካዳሚ በተደረገ ስብሰባ ላይ ተናግረዋል። "ይህ እውነት ነው" ሲሉም አክለዋል።

    ትራምፕ አርብ ዕለት ንግግር ባደረጉበት ወቅት የሆርሙዝ ወሽመጥ በመዘጋቱ ምክንያት ስለጨመረው የነዳጅ ዋጋ አስተያየታቸውን የሰጡ ሲሆን አሜሪካውያን ተጨማሪ ክፍያ መክፈላቸውን መቀበል አለባቸው ብለዋል።

    የፕሬዚዳንቱ ንግግር ከአምስት ወር በላይ በቆየው የኢራን ጦርነት ላይ ዋሺንግተን የፖሊሲ ለውጥ ስለማካሄዷ ወይም ታስቦበት የተሰነዘረ አስተያየት ስለመሆኑ ምንም የታወቀ ነገር የለም።

    የኢራን ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ካዜም ጋሪባባዲ የትራምፕን አስተያየት ከሰሙ በኋላ ወሽመጡ በኢራን ቁጥጥር እና ሥልጣን ሥር ይቆያል “ምንም አንረበሽም” በማለት ተናግረዋል።

    አሜሪካ እና እስራኤል የካቲት 21፣ 2018 ዓ.ም. በጋራ በመሆን ኢራን ላይ ጦርነት ካወጁ ወዲህ የሆርሙዝ ወሽመጥ በቋሚነት ተዘግቷል።

    አሜሪካ እና ሌሎች የአገሪቱ ከፍተኛ ባለሥልጣናት የኢራን ጦር በጀመረበት ወቅት የአገሪቱን የኒውክሌር ፕሮግራም ማስቆም ዋነኛ ዓላማቸው መሆኑን ሲናገሩ ነበር።

    ኢራን በበኩሏ ለሚፈጸምባት ድብደባ በባሕረ ሰላጤው አገራት የሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሠፈሮችን እንዲሁም በወሽመጡ በኩል የሚያልፉ ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን በማጥቃት ምላሽ ሰጥታለች።

    አሜሪካ ወደ ኢራን ወደቦች የሚገቡ እና የሚወጡ መርከቦችን እንቅስቃሴ የገደበች ሲሆን የሁለቱ አገራት መካረር የዓለም ነዳጅ ዋጋ ቅናሽ እንዳያሳይ አድርጎታል።

    በሰኔ ወር አሜሪካ እና ኢራን ወታደራዊ እርምጃዎችን የሚያስቆም የመግባቢያ ሰነድ ቢፈራረሙም ከጥቂት ሳምንት በኋላ ፈርሶ ጦርነቱ ዳግም አገርሽቷል።

    ትራምፕ አርብ ዕለት የአገሪቱ ሕግ አውጪዎች በተሰበሰቡበት ባደረጉት ንግግር፣ ኢራን ወደቦች ላይ የጣሉት እግድ ማንም ሊጥሰው የማይችል መሆኑን በመግለጽ አወድሰውታል።

    እንዲሁም እርምጃውን በሆርሙዝ በኩል በሚደረግ የመርከቦች እንቅስቃሴ ላይ ለሚደገፉ አገራት የሚሰጥ የሕዝብ አገልግሎት አድርገው አቅርበውታል።

    “እያደረግን ያለነው ነገር ለዓለም የሚሰጥ ታላቅ አገልግሎት መሆኑን ማስታወስ ብቻ ነው ፤ ለእኛ ብቻ ሳይሆን ለዓለም ጭምር።” ሲሉ የተናገሩት ትራምፕ፣ “እግዱን ማስቆም እንደማይቻል" እና "የብረት ግንብ" ማለት እንደሆነ አስረድተዋል።

    ትራምፕ በኒውዮርክ ተገኝተው ንግግር ያደረጉት በቅርቡ ለሚደረገው ምርጫ ለሪፐብሊካን ተመራጮች ድጋፍ ለማሰባሰብ ነው።

  10. በጃፓን በተከሰተ ከዚህ ቀደም “ታይቶ የማይታወቅ” ከባድ ዝናብ ምክንያት ስምንት ሰዎች ሞቱ

    በምሥራቃዊ ጃፓን ያጋጠመ ከባድ ዝናብ ቢያንስ የስምንት ሰዎች ሕይወት እንዲያልፍ እና በሺህዎች የሚቆጠሩ ተጓዦች በረራ እንዲስተጓጎል አደረገ።

    ባለሥልጣናት ከዚህ በፊት "ታይቶ የማይታወቅ" ሲሉ የገለጹት ይህ ከባድ ዝናብ፣ ቺባ ግዛት ውስጥ በሚገኙ ከ20,000 በላይ መኖሪያ ቤቶች የኤሌክትሪል ኃይል እንዲቋረጥ ምክንያት ሆኗል።

    የቺባ ግዛት አስተዳዳሪ ቶሺሂቶ ኩማጋይ "ይህ ሁኔታ በጃፓን ታሪካዊ የአየር ሁኔታ እንኳ ሲታይ እጅግ ያልተለመደ ነው" ሲሉ ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

    “ከዚህ ቀደም ለበርካታ የተፈጥሮ አደጋዎች ምላሽ ሰጥቻለሁ፤ እንደዚህ አይነት ሁኔታ ግን አጋጥሞኝ አያውቅም" ሲሉም አክለዋል።

    የጃፓን ሚቲዮሮሎጂ ኤጀንሲም “ከዚህ ቀደም ታይቶ የማይታወቅ ከባድ ዝናብ” እንደሚሆን አስቀድሞ ተንብዮ ነበር።

    በዚህ ከፍተኛ ዝናብ ምክንያት ቢያንስ ስምንት ሰዎች መሞታቸውን የጃፓን መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    ከሞቱት መካከል አንዷ በጎርፍ በተሸፈነ መንገድ ላይ ሳለች መኪናዋ ውስጥ ውሃ ገብቶ ሕይወቷ ማለፉን ባለሥልጣናት ተናግረዋል። ሁለት ሰዎች ደግሞ መንገድ ላይ ወድቀው ሕይወታቸው እንዳለፈ ተገልጿል።

    የአካባቢው ባለሥልጣናት ሐሙስ ዕለት በአገሪቱ ከፍተኛ የሆነውን ‘ደረጃ አምስት’ የአደጋ ማስጠንቀቂያ ሰጥተው ነበር። ዛሬ አርብ ይህ ማስጠንቀቂያ ወደ ደረጃ አራት ዝቅ ቢደረግም፣ መሬት መንሸራተት እና ጎርፍ ሊፈጠር ይችላል የሚለው ስጋት አሁንም ቀጥሏል።

    ይህ ከፍተኛ ዝናብ የተከሰተው በዚህ ሳምንት ጃፓን እና ጎረቤት አገራት ውስጥ ተከታታይ አውሎ ነፋሶች ከታዩ በኋላ ነው። የሚቲዮሮሎጂ ባለሙያዎች በዚህ ወቅት ባልተመደ መጠን የሚንቀሳቀስ አውሎንፋስ (ታይፉን) እንደሚከሰት ተንብየው ነበር።

    አሁኑ ከፍተኛ ዝናብ፣ ወደ አገሪቱ ምሥራቃዊ ክፍል የነፈሰው ሞቃት እና እርጥበታማ አየር ከላይ ካለው ቀዝቃዛ አየር ጋር መቀላቀሉ በፈጠረው ከፍተኛ የሆነው የአየር ሁኔታ መዛባት የተከሰተ መሆኑን የጃፓን ሚቲዮሮሎጂ ኤጀንሲ አስታውቋል።

  11. አሜሪካ ከ40 በላይ አገራት ቻይና የተጣለባትን ታሪፍ እንድታመልጥ እያገዙ ነው ስትል ከሰሰች

    ቻይና ወደ አሜሪካ የምትልካቸው ምርቶች ላይ የተጣለውን ታሪፍ ለማለፍ ስትል፣ ምርቶቿን አሜሪካ ዝቅተኛ ቀረጥ በጣለችባቸው አገራት በኩል አድርጋ እያስገባች መሆኑን ዋይት ሀውስ ገለጸ።

    ከ40 በላይ በላይ አገራትም ቻይና አሜሪካን ታሪፍ እንዳታመልጥ እገዛ እያደረጉ ነው ሲል ከስሷል።

    ዋይት ሀውስ ባወጣው ሪፖርት ከዘረዘራቸው አገራት መካከል ካናዳ፣ ህንድ፣ ሜክሲኮ፣ ጃፓን እና ደቡብ ኮሪያ ይገኙበታል። ጎረቤት አገር ኬንያ እና ሞሮኮም ዝርዝሩ ውስጥ ተካትተዋል።

    የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር እንደሚከስሰው ከሆነ፣ እነዚህ አገራት ቻይና ለአሜሪካ መክፈል የነበረባትን በቢሊዮን ዶላሮች የሚቆጠር የታሪፍ ክፍያ እንድታመልጥ አግዘዋል።

    ቻይና ምርቶቿን ወደ ሦስተኛ አገራት ከላከች በኋላ፣ የተመረቱበት ትክክለኛ ስፍራ ተሸፍኖ በድጋሚ እንዲታሸጉ አድርጋለች ሲል ዋይት ሀውስ ከስሷል።

    የዋይት ሀውስ የንግድ አማካሪ ፒተር ናቫሮ፣ ይህ አካሄድ “የአሜሪካውያንን የሥራ ዕድል እና በቢሊዮን [ዶላር] የሚቆጠር ገቢ” እንዳሳጣ ገልጸዋል።

    በዋሽንግተን የሚገኘው የቻይና ኤምባሲ ቃል አቀባይ ግን “በንግድ ጦርነት ውስጥ አሸናፊ የለም” ሲሉ ክሱን አጣጥለዋል። አሜሪካ የወሰደችውን የታሪፍ እርምጃ እንዲሁም የመንግሥት ኃይልን በመጠቀም የቻይና ኩባንያዎች ዒላማ መደረጋቸውን ተቃውመዋል።

    “ድንበር ተሻጋሪ ምርቶችን በተመለከተ የሚወሰዱ የተናጠል እርምጃዎች ወይም ስምምነቶች የሦስተኛ አካላትን ጥቅሞች ዒላማ ማድረግ ወይም መጎዳት የለባቸውም” ብለዋል።

    ቢቢሲ በዚህ ተግባር ለተከሰሱት የካናዳ፣ ህንድ፣ ሜክሲኮ፣ ጃፓን፣ ደቡብ ኮሪያ እና የሌሎች የንግድ አጋሮችን የአሜሪካ ኤምባሲዎች ጥያቄ አቅርቧል።

    ይህ ሪፖርት ይፋ የሆነው አሜሪካ እና ቻይና ተከታታይ የማዕቀብ እርምጃዎችን አንዳቸው በሌላኛቸው ላይ በጣሉበት ወቅት ነው። ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና የቻይናው መሪ ዢ ጂንፒንግም በዋሽንግተን ሊገናኙ ሳምንታት ቀርተውታል።

    የዋይት ሀውስ ሪፖርት እንደሚያሳየው 30 ቢሊዮን ዶላር እስከ 300 ቢሊዮን ዶላር እንደሚያወጡ የሚገመቱ ምርቶች ከፍተኛ ታሪፍ ከተጣለባቸው አገራት ተነስተው ዝቅተኛ የአሜሪካ ቀረጥ ባለባቸው አገራት በኩል አልፈው አሜሪካ ገብተዋል።

    “ትራንስሺፕመንት” በመባል የሚታወቀው ይህ አካሄድ፣ ከአንድ አገር የተነሱ ምርቶች በሌላ አገር በኩል ወደ መጨረሻ መዳረሻቸው የሚገቡበት ነው።

  12. የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ ብሪታኒያን ‘እስላማዊ ሪፐብሊክ’ ማለታቸው አነጋጋሪ ሆነ

    የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታኒያሁ ብሪታኒያን ‘እስላማዊ ሪፐብሊክ’ ብለው መጥራታቸው አነጋጋሪ ሆኗል።

    ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከአገራቸው ጦር ሠራዊት ፖድካስት ጋር በነበራቸው ቃለ ምልልስ፣ ቀደምት የብሪታኒያ መሪዎች የእስራኤል አጋር እንደነበሩ እና ይህ ሁኔታ አሁን መቀየሩን ባነሱበት ጊዜ ነው አነጋጋሪውን አስተያየት የሰነዘሩት።

    እስራኤል በጋዛ፣ በሊባኖስ እና በኢራን ጦርነት ወቅት ባካሄደቻቸው ዘመቻዎች የተነሳ ብሪታኒያን ጨምሮ በአውሮፓ አገራት ተቃውሞ ሲሰነዘርባት ቆይቷል።

    ጠቅላይ ሚኒስትር ኔታኒያሁ በስድስቱ ቀን ጦርነት ወቅት የቀድሞው የብሪታኒያ ጠቅላይ ሚኒስትር ዊኒስተን ቸርችል ልጆች ወደ እስራኤል ሄደው ጦርነቱን እስራኤልን በሚደግፍ ሁኔታ መዘገባቸውን አንስተዋል።

    “ያንን [ድጋፍ] አሁን ለመግኘት ሞክር፣ ልታገኝ የምትችለው የብሪታኒያ እስላማዊ ሪፐብሊክን ነው” በማለት እየሳቁ ሲናገሩ ተደምጠዋል።

    ይህ የኔታኒያሁ ንግግር መነጋገሪያ መሆኑን ተከትሎ ቃል አቀባያቸው አገላለጹን ተከላክለው ምላሽ ሰጥተዋል።

    የጠቅላይ ሚኒስትሩን አስተያየት ተከትሎ የፖድካስቱ አስተናጋጅ ከብሪታኒያ በተጨማሪ አጠቃላዩ አውሮፓ በእስራኤል ላይ ተመሳሳይ አቋም እያራመደ መሆኑን ጠቅሶ ላቀረበላቸው ጥያቄ ተጨማሪ ሃሳብ ሰንዝረዋል።

    ኔታኒያሁ ሃሳባቸውን የበለጠ በማጠናከር “አዎ፤ ነገር ግን አንድ ሰው እንዳለው ኒውክሌር ጦር መሳሪያ የታጠቀች የመጀመሪያዋ እስላማዊ ሪፐብሊክ የምትሆነው ብሪታኒያ እስላማዊ ሪፐብሊክ ናት” በማለት መልሰዋል።

    በብሪታኒያ እና በእስራኤል መካከል ያለው ግንኙነት እየሻከረ ሲሆን አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር አንዲ በርንሃም ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ የበለጠ ሊበላሽ እንደሚችል ሲነገር ቆይቷል።

    በርንሃም ብሪታኒያ መካከለኛው ምሥራቅን በተመለከተ አዲስ አካሄድን እንደምትከተል ተናግረዋል። በእስራኤላዊ ግለሰቦች እና ተቋማት እንዲሁም ህገወጥ ሰፋሪዎች ላይ ማዕቀብ እንደሚጥሉ “በእስራኤል መንግሥት ላይ ጫና እንደሚያሳድሩ” ገልጸዋል።

  13. አሜሪካ ተተኪ አውሮፕላን ጫኝ ግዙፍ መርከብ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ አሰማራች

    በአውሮፕላን ተሸካሚ መርከቦች ላይ ከ250 ቀናት በላይ የቆዩ የአሜሪካ ጦር አባላት የአአምሮ ጤና ሁኔታ ስጋት ከፈጠረ ወዲህ በፓሲፊክ ውቅያኖስ ላይ የሚገኝ አውሮፕላን ተሸካሚ መርከብ፣ ዩኤስኤስ ጆርጅ ዋሺንግተን ወደ መካከለኛው ምሥራቅ መጓዝ ጀመረ።

    በመካከለኛው ምሥራቅ ለረዥም ጊዜ የቆየው ዩኤስኤስ አብራሃም ሊንከን አውሮፕላን ጫኝ መርከብ የአቅርቦት እጥረት እንደገጠመው ተዘግቧል።

    አዲስ የተሰማራው መርከብ ለወራት የቆየውን ሊንከን የተሰኘውን መርከብ ተክቶ አሜሪካ በኢራን ላይ የምታካሄደውን የአየር ድብደባ ያግዛል።

    በመርከቡ ላይ የሚገኙ ባሕረተኞች ከ260 ቀናት በላይ መቆየታቸውን በመጥቀስ የሕግ አውጪዎች ስጋታቸውን እየገለጹ ነው።

    በርካታ ዲሞክራት የሕግ አውጪዎች ፔንታገን ተጠያቂ እንዲሆን እና ትራምፕ ጦርነቱን እንዲቋጩ ግፊት እያደረጉ ነው።

    የመከላከያ ሚኒስትሩ ፒት ሄግሴት ዘገባው ያለውን እውነታ “ሙሉ በሙሉ አይወክልም” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።

    ሄግሴት አክለውም የአሜሪካ ባሕር ኃይል በኢራን ወደቦች ላይ የጣለውን እገዳ “ላልተወሰነ ጊዜ” እንደሚቀጥል ተናግረዋል።

    ዩኤስኤስ ጆርጅ ዋሺንግተን በቬትናም ከሚገኘው ዳ ናንግ ወደብ ባለፈው ሳምንት መንቀሳቀሷን ባሕር ኃይሉ አስታውቋል።

    መርከቧ በሲንጋፖር በኩል ስታልፍ የታየች ሲሆን ማላካ ወሽመጥ መድረሷም ተዘግቧል።

  14. ዓለም አቀፍ የባህር ላይ መከላከያ ጥምረት ለመመስረት አስራ አምስት አገሮች ስምምነት መፈረማቸው ተገለፀ

    አስራ አምስት አገሮች ዓለም አቀፍ የባህር መከላከያ ጥምረት ለመመስረት የተዘጋጀውን ሰነድ መፈረማቸውን የሳዑዲ አረቢያ መከላከያ ሚኒስቴር አስታወቀ።

    "የጋራ መግለጫውን የፈረሙ አገሮች ቁጥር 15 ደርሷል፤ 13 አገሮች ደግሞ ብሔራዊ ሂደቶችን አጠናቅቀው እና የጥምረቱን ቻርተር ፈርመው በይፋ መቀላቀላቸውን አስታውቀዋል" ሲል ሚኒስቴሩ ሐሙስ ዕለት በኤክስ ላይ ባወጣው መግለጫ ይፋ አድርጓል።

    ይህ መግለጫ የወጣው ሐሙስ ዕለት በጂዳ ከተካሄደው የጥምረቱ ዕቅድ አውጪዎች ሦስተኛ ስብሰባ በኋላ ነው።

    "ይህ ጥምረት ወደ ተቋማዊ እና የስራ እንቅስቃሴ ደረጃ መሸጋገሩን የሚያመለክት ሲሆን የተቀሩት አገሮች ደግሞ ጥምረቱን ለመቀላቀል የሚያስፈልጉትን ብሔራዊ ሂደቶች እያጠናቀቁ ነው” ሲል የሳዑዲ መግለጫ አክሏል።

    ጥምረቱ በሳዑዲ የሚመራ ሲሆን፣ ፓኪስታን የምክትልነቱን ቦታ እንደምትይዝ ተገልጿል።

    ሳዑዲ አረቢያ እና ሌሎች 13 አገሮች በባብ አል-ማንዳብ ወሽመጥ፣ በቀይ ባህር እና በኤደን ባሕረ ሰላጤ ውስጥ ያለውን የመርከቦች እንቅስቃሴ ነፃነት፣ ዓለም አቀፍ ንግድ እና የኃይል አቅርቦት መስመሮችን ለመጠበቅ ያለመ ባለብዙ አገር የባህር መከላከያ ጥምረት መቋቋሙን በዚህ ዓመት ሐምሌ 30 ነበር ያስታወቁት።

  15. የኢራን ጦርነት ቻይና የምትሸጣቸውን በኤሌትሪክ የሚሠሩ የከባድ መኪናዎች ቁጥር ጨምሯል ተባለ

    የኢራን ጦርነት ከተቀሰቀሰ እና የነዳጅ ዋጋ ንረት ከተከሰተ ወዲህ ቻይና ወደ ሌሎች የእስያ አገራት የምትልካቸው የኤሌትሪክ ከባድ መኪናዎች ቁጥር እንዲሁም የአገር ውስጥ ሽያጭ በከፍተኛ ደረጃ ማደጉ ተገለጸ።

    ቻይና በኤሌትሪክ የሚሠሩ ቀላል እና ከባድ የጭነት መኪናዎች በፍጥነት እያመረተች ለገበያ የምታቀርብ ሲሆን ሌሎች የእርሷን ፈለግ ለመከተል እየሞከሩ ነው።

    የካቲት 21/2018 ዓ.ም. እስራኤል እና አሜሪካ በጥምረት ኢራን ላይ ጦርነት ካወጁ ወዲህ ቻይና ወደ ውጭ የምትልከው በኤሌትሪክ የሚሠሩ የጭነት መኪናዎች ቁጥር በእጥፍ አድጓል።

    ደቡብ እና ደቡብ ምሥራቅ እስያ አገራት ከመካከለኛው ምሥራቅ በሚመጣ ነዳጅ ላይ ጥገኛ ናቸው።

    ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን መዝጋቷን ተከትሎ በናፍያ ዋጋ ላይ ከፍተኛ ጭማሪ ታይቷል።

    ይህም ለቻይና የኤሌትሪክ መኪናዎች ትልቅ ገበያ መፍጠሩን 'ግሎባል ፔትሮል ፕራይስስ ዶት ኮም' ዘግቧል።

    የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት ከተጀመረ ወዲህ በሲሪላንካ የናፍጣ ዋጋ በ48 በመቶ ሲጨምር በፊሊፒንስ ደግሞ 57 በመቶ ከፍ ብሏል።

    የቻይና መንግሥት ይፋ ባደረገው መረጃ ከኢራን ጦርነት ወዲህ በአገሪቱ የነዳጅ ዋጋ ላይ የ15 በመቶ ጭማሪ ታይቷል።

    የዓለማችን ግንባር ቀደም በኤሌትሪክ የሚሰሩ የጭነት መኪናዎች አምራች በሆነው ሳኒ ውስጥ ዓለም አቀፍ የገባያ ጥናት ባለሙያ የሆኑት ዣኦቲንግ ዩኡ “ጦርነቱ አዳዲስ ገበያዎችን ከፍቷል” ሲሉ ተናግረዋል።

  16. በማሊ መፈንቅለ መንግሥት ለማካሄድ አሲሯል በሚል 20 ዓመት የተፈረደበት ፈረንሳዊ ምህረት ተደረገለት

    በምዕራብ አፍሪካዊቷ አገር ማሊ መፈንቅለ መንግሥት ለማካሄድ አሲሯል ተብሎ የ20 ዓመት አስር ተፈርዶበት የነበረው ፈረንሳዊ ሐሙስ ዕለት ፕሬዚዳንታዊ ምህረት እንደተደረገለት ተገለጸ።

    ያን ቬዚሊየር የተባለው ፈረንሳዊ ባለፈው ዓመት “ከፈረንሳይ የደህንነት መስሪያ ቤት ተልዕኮ በመቀበል” የማሊን መንግሥት ለመጣል ከበርካታ ጦር ጄነራሎች እና ወታደሮች ጋር አሲሯል ተብሎ ተከስሶ ነበር።

    ማሊ የፍርድ ውሳኔውን እንድትቀለብስ ያደረጋት ምን እንደሆነ አልታወቀም።

    የፈረንሳይ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ከዚህ ቀደም ቬዚሊየር የአገሪቱ ሰላይ ነው መባሉ “መሠረተ ቢስ” ብሎ ከማሊ መንግሥት ጋር እየተነጋገረ መሆኑን ገልጾ ነበር።

    የማሊ መንግሥት በፌስ ቡክ ላይ ባሰፈረው መልዕክት “ይህ ምህረት የመከላከያ መብቶች ሁሉ በተከበሩበት የፍርድ ሂደት ውስጥ በተሰጠ ውሳኔ የተረጋገጡትን እውነታዎች የማይንድ ወይም በጥያቄ ውስጥ የማያስገባ፣ ግለሰቡ ከማሊ በአስቸኳይ እንዲወጣ ከማድረግ ጋር አብሮ የሚከናወን ነው” ብሏል።

    ማሊ የፈረንሳይ ቅኝ ግዛት የነበረች ሲሆን እአአ ከ2012 ጀምሮ በእስላማዊ ታጣቂዎች የተነሳ የደህንነት ቀውስ ውስጥ ገብታለች።

    ፕሬዚዳንት አሲም ጎይታ እአአ በ2021 መፈንቅለ መንግሥት አካሂደው ሥልጣን የተቆጣጠሩ ሲሆን እርሳቸው ፕሬዚዳንት ከሆኑ በኋላም የጂሃዲስቶች ጥቃት ጨምሯል።

    ባለፈው ዓመት ፈረንሳዊው በቁጥጥር ሥር በዋለበት ወቅት የማሊ የደህንነት ሚኒስትር ጄኔራል ዳውድ አሊ መሐመዳይን “የማሊ የጸጥታ ኃይሎች አካል” የሆኑ ግለሰቦች “የሪፐብሊኩን ተቋማት ለማወክ በመፈለጋቸው” በቁጥጥር ሥር ውለዋል ብለው ነበር።

    ሚኒስትሩ አክለውም "እነዚህ ወታደሮችና ሲቪሎች" "የውጭ አገራትን እርዳታ" እንዳገኙ ገልጸዋል።

    ቬዚሊየር በማሊ የፖለቲካ መሪዎችን፣ የሲቪል ማኅበረሰብን እና የጦር አባላትን በማሰባሰብ "የፈረንሳይ የስለላ አገልግሎትን ወክሎ" እርምጃ መውሰዱን ሚኒስትሩ ተናግረዋል።

    በማሊ ያለው የፖለቲካ ውጥረትና የጸጥታ ቀውስ ተባብሷል።

  17. አሜሪካ በኢራን ወደቦች ላይ የጣለችውን እገዳ ላልተወሰነ ጊዜ ልታራዝም እንደምትችል አስታወቀች

    አሜሪካ ሐሙስ ዕለት በኢራን ወደቦች ላይ የጣለችውን እገዳ ላልተወሰነ ጊዜ በማራዘም የምጣኔ ሃብት ጫናውን ልታጠናክር አንደምትችል ተናገረች።

    አሜሪካ ይህንን ያለችው በሁለቱ አገራት መካከል ይደረጋል ተብሎ የሚጠበቀው ድርድር ባለመሳካቱ ውጥረት ባየለበት እና የዓለም የነዳጅ ዘይት አቅርቦት እየቀነሰ በመጣበት ወቅት ነው።

    የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር የሆኑት ፒት ሄግሴት ለጋዜጠኞች፣ ጦሩ በኢራን ላይ የተጣለውን እገዳ ለማስቀጠል በቀጣናው መቆየት የሚያስችል አቅም አለው ብለዋል።

    በኢራን ወደቦች ላይ የተጣለው እገዳ አገሪቱ ላይ የምጣኔ ሃብት ጫና እየፈጠረ ነው።

    "የአሜሪካ የባህር ኃይል እንደዚህ ዓይነት የእግድ እርምጃን ላልተወሰነ ጊዜ ማስቀጠል ይችላል፤ ምክንያቱም ቀደም ሲል እንዳደረግነው ሁሉ መርከቦችን እየቀያየርን ማስገባትና ማስወጣታችንን እንቀጥላለን" ሲሉ ሄግሴት ወደ ፓናማ ባደረጉት ጉዞ ወቅት ለጋዜጠኞች ተናግረዋል።

    የገንዘብ ሚኒስትሩ ስኮት ቤሴንት ደግሞ አገራቸው በኢራን ኢኮኖሚ ላይ ተጨማሪ ጉዳት ለማድረስ ማቀዷን ይፋ አድርገዋል።

    “በሚቀጥለው ሳምንት ለሚሰጡ ተጨማሪ መግለጫዎች ተዘጋጁ። ምክንያቱም በአንድ አገር ላይ በሚደረግ የኢኮኖሚ ማግለል ታሪክ ውስጥ ታይቶ የማይታወቅ ዓይነት እርምጃዎችን ልንወስድ ነው” ሲሉ ከኒውስማክስ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ወቅት ተናግረዋል።

    በሰኔ ወር በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የተፈረመው የመግባቢያ ሰነድ ከፈረሰ ወዲህ ኢራን የሆርሙዝ ወሽመጥን ዳግም በመዝጋት አሜሪካ ላይ ጫና ለመፍጠር እየሞከረች ነው።

    ጦርነቱ ከጀመረበት የካቲት ወር አንስቶ ወሽመጡን ለማቋረጥ የሚሞክሩ መርከቦች ላይ ጥቃት የምትፈጽመው ቴህራን የዓለም የነዳጅ ዋጋ ከፍ እንዲል አስተዋጽኦ አድርጋለች።

    ሐሙስ ዕለት ምሽት የአቡዳቢ ብሔራዊ የነዳጅ ኩባንያ ንብረት የሆኑ ሁለት ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ጥቃት እንደደረሰባቸው የዩኤኢ ብሔራዊ ዜና ኤጀንሲ ዋም ዘግቧል።

    የዩናይትድ አረብ ኤሜሬትስ መንግሥት የኢራንን ጥቃት አውግዟል።

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ጦርነቱን በፍጥነት እንዲቋጩ ከአገር ውስጥ ከፍተኛ ግፊት እየደረሰባቸው ነው።

    ትራምፕ፣ አሜሪካ በባህር ወሽመጡ ላይ "ሙሉ ቁጥጥር" እንዳላት በተደጋጋሚ የገለጹ ሲሆን፣ ኢራን ይህንን አስተባብላለች።

    ቴሀራን ያስቀመጠቻቸው ቅድመ ሁኔታዎች እስኪሟሉ ድረስ ወሽመጡ ዳግም እንዲከፈት እንደማትፈቅድ አስታውቃለች።

    ከቅድመ ሁኔታዎቹ መካከል የኢኮኖሚ ማዕቀቦችን ማንሳት እና የታገዱ የኢራን ሃብቶችን መልቀቅ ይገኙበታል።

    ማክሰኞ ዕለት በወሽመጡ በኩል ያለፉ መርከቦች ስምንት ብቻ ናቸው። ከጦርነቱ በፊት ግን በሆርሙዝ በኩል በቀን ከ130 እስከ 140 መርከቦች ያልፉ ነበር።

    አሜሪካ በሰኔ ወር አጋማሽ ላይ በኢራን ወደቦች ላይ ጥላ የነበረውን እገዳ አንስታ የነበረ ቢሆንም ጦርነቱ ዳግም ማገርሸቱን ተከትሎ በአገሪቱ ላይ የምጣኔ ሃብት ጫና ለማሳደር በሚል ዳግም ወደ ወደቡ የሚደረግ እንቅስቃሴን አግዳለች።

    ዋሺንግተን ቀድመ ሲል ኢራን እና ኦማን በወሽመጡ አስተዳደር ላይ የሚስማሙ ከሆነ እገዳውን አነሳለሁ ብላ ነበር።

  18. አዲስ ጦርነት ከተቀሰቀሰ ኢራን የበለጠ ምላሽ በመስጠት የተራዘመ ጦርነት እንደምታካሂድ አስታወቀች

    ከፍተኛ የኢራን ወታደራዊ ባለሥልጣናት አሜሪካ ሌላ ዙር ጥቃት በአገራቸው ላይ የምትከፍት ከሆነ ከባድ ጥቃት በመሰንዘር ለተራዘመ ጦርነት እየተዘጋጁ መሆናቸውን ተናገሩ።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ከፍተኛ ባለሥልጣን ራሱል ሳናኢ-ራድ ከአሜሪካ ጋር አዲስ ጦርነት የሚቀሰቀስ ከሆነ ቴህራን “ከዚህ በፊት ከነበረው በጠነከረ ሁኔታ” ምላሽ እንደምትሰጥ አስታውቀዋል።

    ፋርስ የተባለው የኢራን ዜና ወኪል እንደዘገበው የአብዮታዊ ዘቡ ጠቅላይ አዛዥ ፖለቲካዊ ርዕዮተ ዓለም ጉዳዮች መኮንን የሆኑት ባለሥልጣን "ጠላት በአገር ውስጥ ክፍፍልን በመፍጠር እና የኢኮኖሚ ጫና በማሳደር ተቃውሞዎችን መፍጠር እንደሚችል በማሰብ ጥረት እያደረገ ነው” ብለዋል።

    በተጨማሪም የኢራን ሠራዊት ምክትል ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም አሊሬዛ ሼክ በበኩላቸው የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ “ለተራዘመ ጦርነት” እና ቀጣይነት ላለው ዘመቻ ዝግጁ መሆኗን ተናግረዋል።

    እንዲሁም የኢራን የጦርነት መርኅ ግልጽ ከሆነው የመከላከል አቋም ወደ “ጥቃትን ቀድሞ ማስቀረት እና ማጥቃት” መሸጋገሩን እንዲሁም የበለጠ ሚሳዔል እና ድሮን የማምረት አቅምን ቀጣይነት ላለው ዘመቻ ወሳኝ መሆኑን አመልክተዋል።

    በሳምንታት ውስጥ ይጠናቀቃል የተባለው አሜሪካ በኢራን ላይ የከፈተችው ጦርነት ሞቅ ቀዝቀዝ እያለ ወራትን ያስቆጠረ ሲሆን፣ በድርድር እንዲያበቃ ለማድረግ ጥረት እየተደረገ ነው።

  19. ኢራን አሜሪካ በሆርሙዝ ላይ ሙሉ ቁጥጥር አለኝ ማለቷን “መሠረተ ቢስ” ስትል አጣጣለች

    ኢራን ሐሙስ ዕለት አሜሪካን የሆርሙዝ ወሽመጥን ሙሉ በሙሉ ተቆጣጥሬያለሁ ማለቷን “መሠረተ ቢስ ውሸት” ስትል ውድቅ አደረገች።

    የዓለም አንድ አምስተኛ ነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ የሚተላለፍበት ይህ ቁልፍ የውሃ መስመር በቴህራን ቁጥጥር ስር እንደሆነም ጨምራ አስታውቃለች።

    የኢራን ጦር አዛዥ በአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ኢሪብ ላይ በተላለፈ መግለጫቸው “አሜሪካ በሆርሙዝ ወሽመጥ መርከቦች ማለፋቸውን በሚመለከት የምትናገረው ውሸት የአገሪቱ ጦር አቅም ማጣቱን እና ግራ መጋባቱን የሚያንጸባርቅ፣ ሐሰት እና መሠረተ ቢስ ነው” ብለዋል።

    “የሆርሙዝ ወሽመጥ እንደበፊቱ ሁሉ በኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ሙሉ አስተዳደርና ቁጥጥር ስር ሆኖ ይቀጥላል” ሲሉ የጦሩ ቃል አቀባይ ተናግረዋል።

    ቃል አቀባዩ አክለውም “ማንኛውም የንግድ መርከብ ወይም የነዳጅ ማመላለሻ መርከብ የኢራን ጠንካራ የጦር ኃይል ፈቃድ እና ቁጥጥር ሳይኖር የባህር ወሽመጥን በሰላም አያልፍም ወይም አይችልም” ብለዋል።

  20. ሴቶችን ወደ መኖሪያ ቤታቸው በማምጣት የተከሰሱት የፈረንሳይ አምባሳደር የሥነ ምግባር እርምጃ ሊወሰድባቸው ነው

    ፈረንሳይ የሥነ-ምግባር ጉድለት ፈጽመዋል የሚል ክስ በቀረበባቸው የማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ከፍተኛ ዲፕሎማቷ ላይ የማጣራት እርምጃ ጀምራለች።

    በአምባሳደሩ ላይ የቀረበው ክስ በርካታ ሴቶችን ወደ መኖሪያ ቤታቸው በማምጣት ከተወሰኑት ጋር ወሲብ ፈጽመዋል የሚል ነው።

    አምባሳደር ብሩኖ ፉሼ እአአ ከጥር 2024 እስከዚህ ዓመት መጋቢት ወር ድረስ ባለው ጊዜ ውስጥ ፈጽመዋል ተብለው የቀረቡባቸው ክሶች ከደኅንነት ጉዳዮች ጥሰት ጋር ሊያያዙ ይችላሉ በሚል ነው የፈረንሳይ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ምርመራ የጀመረው።

    አንድ የፈረንሳይ ዲፕሎማት ለቢቢሲ እንደገለፁት፥ ክሱን ተከትሎ ሚኒስቴሩ በአምባሳደሩ ላይ አስተዳደራዊ እርምጃ ለመውሰድም በሂደት ላይ ነው።

    ቢቢሲ በባንጉ የሚገኘውን የፈረንሳይ ኤምባሲ አስተያየት ጠይቋል። በፉሼ ላይ የተጀመረው የዲሲፕሊን ሂደት ምንን እንደሚያካትት እና እስከምን ድረስ እንደሚቀጥል እስካሁን የታወቀ ነገር የለም።

    ከፈረንሳይ መገናኛ ብዙኃን በተገኙ ዘገባዎች ከሆነ፣ ፉሼ በዋና ከተማዋ ባንጉ በሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው ውስጥ 30 የሚጠጉ ሴቶችን ጋብዘዋል ተብሏል።

    አንዳንዶቹ ሴቶች ሌሊቱን ሙሉ በዚያው አድረዋል መባሉ የደህንነት ስጋቶችን አስነስቷል።

    ዕድሜያቸው 65 ዓመት የሆኑት ፉሼ፣ ከ2023 ወዲህ በባንጉ የአገራቸው ዋና ዲፕሎማት በመሆን እያገለገሉ ይገኛሉ።

    እርሳቸው ፈፀሙ የተባለው የሥነ-ምግባር ጉድለት ይፋ የሆነው፣ ፈረንሳይ እና ማዕከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ ተበላሽቶ የነበረውን ግንኙነታቸውን ለማሻሻል እየሰሩ ባሉበት ወቅት ነው።