እንደ እጽ አሳሳቢ በሆነው የስልክ ሱስ የምንጠመደው እንዴት ነው? መላቀቅስ ይቻላል?

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ማሪዮስ በቀን ለ14 ሰዓታት ያህል ስልኩን ይጠቀማል። በዚህ ሱስ ሲሰቃይ ነው የቆየው። ስልኩ ከእጁ ላይ እንዲርቅ አይፈልግም።
የስልክ ሱስን ከአደገኛ እፅ ሱስ ነጥሎ አያየውም።
እንደ ማሪዮ ገለፃ የአደገኛ እፅ ሱስ ሳይሻል አይቀርም። አደገኛ እፅን ለማግኘት ብዙ ሕጎችን መጣስ የሚጠይቅ ሲሆን የሕግ ተጠያቂነትንም ያስከትላል።
ስልክ ግን "የራሴን እፅ ተሸክሞ እንደመዞር ነው" ይላል።
"እፁ ሁልጊዜ በኪሴ ውስጥ ነው። በማብራት፣ በመጮህ እንድወስደው ያስታውሰኛል" ይላል የተዘፈቀበትን አደገኛ የሱስ ወጥመድ ሲገልጽ።
በሰሜን ለንደን ነዋሪ የሆነው እና የግል የስፖርት አሠልጣኝ የሆነው ማሪዮስ፣ በቀን ስልኩ ላይ ከሚያሳልፋቸው 14 ሰዓታት ውስጥ አብዛኞቹን የሚያጠፋው ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ነው።
አሁን ብቸኝነት እያስከተለበት ያለውን ይህን ሱሱን ለማስወገድ 12 ክፍሎች ያሉት የግል ሕክምና (ቴራፒ) ለመውሰድ እየሞከረ ነው።
ማሪዮስ እንደሚለው በስልኩ ስክሪን ላይ የሚያሳልፈውን ጊዜ የሚያመለክተው መረጃ በአንድ ቀን ብቻ 116 ጊዜ ስልኩን እንደነካካ ያሳያል።
ከዚህም በተጨማሪ ለሦስት ሰዓታት ያህል ስልኩ ላይ ያለማቋረጥ ተተክሎ እንደቆየ ያመለክታል።
"ማሪዮስ ሱሰኛ ሆኗል? ሱሰኛ ነኝ ማለት ነው?" ሲልም ራሱን መጠየቁን ይናገራል።
ይህንን ለማወቅ ግን አስቸጋሪ ሆኖበታል። ምክንያቱም የስልክ ሱስ የጤና ችግር መሆኑ በይፋ አልተገለፀም።
ሆኖም በቅርቡ ዴሎይት በተባለ ድርጅት በተሠራ የዳሰሳ ጥናት ከ1000 አዋቂዎች መካከል 70 በመቶ የሚሆኑት መላሾች ስልካቸው ላይ ብዙ ጊዜ እንደሚያጠፉ ተናግረዋል።
ዘመናዊ ስልኮች የአእምሮን ይዘት እየቀየሩት እንደሆነ የሚገልጹ በርካታ ጥናቶችም እየወጡ ነው።
በሱስ ላይ የሚሠሩ ባለሙያዎችም በስልክ ሱስ እየማቀቁ ያሉ በርካታ ደንበኞችን እየተከታተሉ እንደሆነ ገልጸዋል።
ባለፈው ዓመት የዩናይትድ ኪንግደም የሱስ ሕክምና ማዕከል ከሦስት ደንበኞቹ አንዳቸው የአደገኛ እፅ ሱስ ሕክምና እንደተደረገላቸው አስታውቋል።
በዓመት 3500 ሰዎችን የሚደግፈው ማዕከሉ እንዳለው እነዚህ ሰዎች ካለባቸው ሌላ ሱስ በተጨማሪ የስልካቸው ጥገኛ ነበሩ።
የሱሰኞች ቁጥርም በአውሮፓውያኑ 2019 ከነበረው ከፍ ያለ ነው። በ2019 የሱስ ሕክምና ለማግኘት ወደ ማዕከሉ የሚሄደው ከ10 ሰዎች አንዱ ነበር።
የሕክምና ማዕከሉ እንዳለው አንዳንድ ታካሚዎች ስልካቸውን እና ሌሎች መሣሪያዎቻቸውን ለማስረከብ ፈቃደኛ ባለመሆናቸው የሄዱበትን ዋነኛ ሱስ ሕክምና አቋርጠዋል።

የፎቶው ባለመብት, BBC/Emma Lynch
በሴንት ሄለንስ፣ ሜርሲሳይድ የሚገኘው 'ስቴፕስ ቱጌዘር' የማገገሚያ ማዕከል አደንዛዥ ዕፅ፣ አልኮል እና ቁማርን ጨምሮ ከሌሎች ሱሶች ጋር የሚታገሉ ሰዎችን ያስተናግዳል።
ሆኖም የሕክምና ባለሙያዎቹ (ቴራፒስቶቹ) ስልካቸውን ጨምሮ ከሌሎች የኤሌክትሮኒክስ ቁሳቁሳቸው መለየት የማይችሉ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን እያስተዋሉ ነው።
በማዕከሉ ቴራፒስት የሆኑት ኬሊ ዋትሰን "ይህ ሱስ ከየትኛውም ሁኔታ የመጣን ማንኛውንም ሰው ሊጎዳ ይችላል" ይላሉ።
"ሁላችንም ስልኮች አሉን፣ ሁላችንም ተመሳሳይ የአንጎል ስሪት ነው ያለን። እናም ብዙዎቻችን በዚህ ሱስ ልንያዝ እንችላለን" ሲሉም አስረድተዋል።
የአንጎላችን ክፍልም የሚሠራው በሽልማት ሥርዓት እንደሆነም ዋትሰን ያስረዳሉ።
"በስልካችን መልዕክት እናገኛለን። በማኅበራዊ ሚዲያዎች ውዴታ (ላይክ) እናገኛለን፤ ከድረ ገጾች አዳዲስ መረጃዎችን እናገኛለን፤ ከዚያም በአንጎላችን ውስጥ ደስታን እና መነሳሳትን የሚቆጣጠረው ዶፓሚን የተባለው መልዕክት አስተላላፊ ሆርሞን ይለቀቃል" ይላሉ።
በአንዳንዶቻችን ላይ የዚህ ሆርሞን ፍላጎት ከፍተኛ ሊሆን ይችላል። ይህም በሕይወታች ያሉን ሰዓታት፣ ቀናት በኦንላይን ዓለም እንዲጠፋ ሊያደርግ እንደሚችልም አብራርተዋል።
ይህንን ስሜት ሌስተር በሚገኘው 'የስቴፕ ቱጌዘር' ቅርንጫፍ ማዕከል ሕክምና የተከታተለው ጀምስ በደንብ ያውቀዋል።
የ48 ዓመቱ ጎልማሳ መጀመሪያ ላይ ወደ ማዕከሉ ያቀናው ከአልኮል መጠጥ ሱሰኝነቱ ለመላቀቅ ነበር። በኋላ ላይ ግን የዲጂታል ጥገኝነቱ ከቁጥጥር ውጪ መሆኑ ግልጽ ሆነ።
ጀምስ በተለይ ሥራውን ካጣ በኋላ ቀኑን የሚያሳልፈው የሶሻል ሚዲያ ገፆችን በማገላበጥ እና የዜና ድረ ገጾችን በማሰስ ነበር።
ይህ ልማዱም በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ምን እየተፈጠረ እንደሆነ የማወቅ ፍላጎቱ ከፍተኛ እንዲሆን አድርጎታል።
በማኅበራዊ ሚዲያ የሆነ ነገር ካጋራም ምን ያህል እንደተወደደ ( ላይክ እንዳገኘ) እና አስተያየት እንደተሰጠበት ለማየት በዕኩለ ሌሊት ከእንቅልፉ ሊነሳ ይችላል።
"የዲጂታል ዓለም ታጋች እንደሆንኩ ይሰማኝ ነበር" ብሏል የስሜቱን ጥልቀት ሲገልጽ።
አሁን ላይ ግን ስልኩን በመጠቀም የሚያገኘው ደስታ አክትሟል። "በጣም ያስጨንቀኝ ነበር" የሚለው ጀምስ፣ ነፍሱ ከእርሱ የተላቀቀች ያህል እንደተሰማው እና ማቆም እንዳዳገተው ያስታውሳል።

የፎቶው ባለመብት, @personaltrainermarios
ቴራፒስቷ ዋትሰን እንደሚሉት ታካሚዎች መጀመሪያ ወደ ማዕከሉ አዳራሽ ሲመጡ ይጨነቃሉ፤ ግራ ይጋባሉ፤ ስልካቸውንም ማስቀመጥ አይፈልጉም።
"ለሥራ እፈልገዋለሁ፤ ከቤተሰብ ጋር ለመገናኘት እጠቀምበታለሁ" የሚል ምክንያት እንደሚሰጡም ይጠቅሳሉ።
"ፍራቻቸውን ከድምጻቸው መረዳት እችላለሁ፤ ስልካቸው እነርሱ ሰላም የሚያገኙበት ቦታ ነው።"
አብዛኞቹ በማዕከሉ መኖሪያ ሥፍራ ቢያንስ ለ28 ቀናት የሚያሳልፉ ሲሆን፣ አንድ ለአንድ እና በቡድን ሱስ ውስጥ ባስገቧቸው ምክንያቶች ላይ ሕክምና ይሰጣቸዋል።
ሕክምናው ቀስ በቀስ ከስልካቸው ጋር ያላቸውን ጥገኝነት ለመቀነስ ረድቷቸዋል።
ዋትሰን ታካሚዎቹ ቀስ በቀስ በስልካቸው ላይ የሚያሳልፉትን ጊዜ እንዲቀንሱ አብራቸው የሠራች ሲሆን እና ከስልካቸው ወይም ከሌላ መሰል መገልገያ ቁሳቁሳቸው ሲለያዩ የሚፈጠርባቸውን ሃሳብ እና ስሜት ማወቅ ችላለች።
"ብዙ ጊዜ ምክንያቶቹ ከሕይወት ጋር የተገናኙ ናቸው። ስልካቸው ላይ በሚያሳልፉበት ጊዜ ከእውነታው ዓለም መነጠል ይችላሉ" ብለዋል።
ከዩኬው ቅንጡ የማገገሚያ ማዕከል - ሬንፎርድ ሆል - ባሻገር በዓለም ዙሪያ ያሉ ሰዎች ከዲጂታል ሱስ ለመላቀቅ እርስ በእርስ እየተደጋገፉ ነው።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
በአውሮፓውያኑ 2017 በቴክኖሎጂ እና ኢንተርኔት አጠቃቀማቸው ስጋት የገባቸው በርካታ ሰዎች 'ኢንተርኔት ኤንድ ቴክኖሎጂ አዲክትስ አኖኒመስ' (አይቲኤኤ) የተባለ ዓለም አቀፍ ኅብረት ፈጥረዋል።
ኅብረቱ የተመሠረተው 'አልኮሆሊክስ አኖኒመስ' በተባለ እና አልኮልን በማቆም ከሱስ ለመላቀቅ በሚሠራው ማኅበር አነሳሽነት ነው።
ጄኒ ከኅብረቱ አባላት መካከል አንዷ ናት። ጄኒ የስልክ ሱሷ ከፍተኛ ከመሆኑ የተነሳ ለቀናት ላትተኛ ትችላለች። ምግብ እና መጠጥም የምትወስደው በግድ ነበር። ከስልኳ መላቀቅ አትችልም ነበር።
ትክክለኛ ስሟን መግለፅ ያልፈለገችው የ30 ዓመቷ ወጣት "የሕይወቴን የተወሰነውን ክፍል አጥቻለሁ" ትላለች።
በስልኳ ላይ የሆነ ነገር እስካየች ድረስ ፊልም፣ አጫጭር ቪዲዮም ይሁን ሌላ ስለምታየው ነገር ግድ አይሰጣትም ነበር።
ጄኒ ከዚህ ልማድ እስከምትወጣ ድረስ ሱስኛ እንደነበረች አልተረዳችም ነበር።
"ጓደኞቼን እና ቤተሰቦቼን ስልኬን ጨምሮ የምገለገልባቸውን መሣሪያዎች እንዲቆልፉባቸው ለመጠየቅ ተገድጄ ነበር" ስትል ታስታውሳለች።
"በጣም መጥፎ ነው። የሆነ ነገር ካላየሁ የምሞት ነበር የሚመስለኝ" ትላለች።
ስልኳን እንኳን ማግኘት ካልቻለች ያለፈቃድ ጭምር ከቤተሰቦቿ ዘመናዊ ስልክ ወይም ላፕቶፕ ልትወስድ ትችላለች።
ድርጊቷ ያሳፍራትም፤ ጥፋተኝነት እንዲሰማት ያደርጋትም ነበር።
ይህን ስሜት ለመርሳት ስትል ደግሞ ብዙ ይዘቶችን ትመለከታለች።
ለዓመታት እርዳታ ስትፈገግ ከቆየች በኋላም ነው ኅብረቱን ያገኘችውና ከሱስ ለመውጣት የሚረዱ 12ቱን ደረጃዎች መከተል የጀመረችው።
አሁን ላይ እያገገመች ነው። ለአምስት ዓመታት ያህል ምንም ዓይነት ነገር አላስተላለፈችም፤ አላየችም።
ጄኒ መሠረታዊ አገልግሎት የሚሰጥ ስልክ መያዟ እና ለሥራ ጉዳይ ብቻ ኢንተርኔት መጠቀሟ ምቾት ሰጥቷታል። "አሁን በቁጥጥር ሥር ነኝ" ብላለች።
ሌላ የኅብረቱ አባል ቶም በበኩሉ ሱሱ ወደ ጨለማ ቦታ እንደመራው ይናገራል። በስልኩ እና በሌሎች ስክሪኖች ላይ ሙሉ ወራትን ሊያጠፋ ይችላል።
"በተከታታይ ለ10 ሰዓታት ልጠቀም እችላለሁ። በእነዚህ ሰዓታት ሙዚቃ ልሰማ፣ በዩቲዩብ የሆነ ነገር ልመለከት፣ ማኅበራዊ ሚዲያ ላስስ ወይም ቪዲዮ ጌም ልጫዎት እችላለሁ።"
ከዚያ ግን ለሁለት ሰዓታት የእግር ሽርሽር አደርጋለሁ፤ ስመለስ ግን ወደዚያው ነው የምመለሰው። ይህም ለወራት ሊቀጥል ይችላል" ብሏል።
ቶም ሱሱ ከፍተኛ ደረጃ ደርሶ ሥራውን እንዲያጣ እና የሕይወት ትርጉም እንዲጠፋው አድርጎታል።
"ራሴን የማጥፋትም ፍላጎት ነበረኝ" ብሏል።
"አሁን ግን በድጋሚ በሕይወት ትክክለኛ ደስታ ማግኘት ጀምሬያለሁ። ቴኒስ እጫዎታሉ፤ ወደ ውጭ እወጣለሁ፤ ወደ ጂምናዚየምም እሄዳለሁ።"

የፎቶው ባለመብት, BBC/Emma Lynch
የብሪታኒያ የምክር እና የሥነ ልቦና ሕክምና ማኅበር ፈቃድ ያላት የሥነ ልቦና ሐኪም ሂልዳ በርክ በቅርቡ 'ፎን አዲክሽን ዎርክቡክ' የሚል መጽሐፍ ለንባብ አብቅታለች።
በርክ መጽሐፉን የፃፈችው እርዳታ ሽተው ወደ እርሷ የሚመጡ ዲጂታል ላይ ጥገኛ የሆኑ ሰዎች መበራከታቸውን ካየች በኋላ ነው።
ባለሙያዋ ስክሪን ላይ ብዙ ጊዜ እያጠፋን እንደሆነ ካስጨነቀን ባሕርያችንን በመገምገም ወደዚያ የገፋን ምክንያት ምን እንደሆነ መመርመር እንዳለብን ትመክራለች።
"'በዚያ ዕለት ምን ነበር የሆነው? የሆነ ሰው የጽሑፍ ምላሽ እየጠበቅን ነበር?'" የሚሉ ጥያቄዎችን ራሳችሁን ጠይቁ" ትላለች።
ብዙ ጊዜ ለላክነው መልዕክት ምላሽ መጠበቅ ምቾት ይነሳል የሚሉት በርክ፣ ከዚህ ሃሳብ ለመውጣት ስንል ስልካችንን እንድንጠቀም እንደሚያደርገን ያስረዳሉ።
ሆኖም ወደ ኢንተርኔት ከመግባት ይልቅ ሌላ ነገር ማድረግን ባለሙያዋ ይመክራሉ። ይህም ለጓደኛችን መደወል፣ ዱብዱብ ማለት፣ ወይም መጽሐፍ ማንበብ ሊሆን ይችላል።
"ምላሽ ላላገኘው መልዕክታችሁም እፍረት ወይም ጥፋተኝነት እንዳይሰማችሁ ሞክሩ። በምትኩ ሌላ ጊዜ እንዲህ ዓይነት ነገሮች ሲያጋጥሟችሁ ምን ማድረግ እንዳለባችሁ አስቡ" ይላሉ።
ስልክ አምራቾችም ሰዎች ስልካቸው ላይ የሚያጠፉትን ጊዜ ለመቆጣጠር የሚያስችላቸውን ዘዴ የፈጠሩ ሲሆን፣ በርካቶቻችንን ሱስ ሊያስይዙ የሚችሉ መተግበሪያዎችን የምንጠቀምበትን ጊዜ ገድበዋል።
የሰሜን ለንደን ነዋሪው ማሪዮስ እየተከተታለ ያለው ሕክምና ከስልክ ጥገኝነቱ እያላቀቀው እንደሆነ ገልጿል።
"ስልክ መጠቀም ሙሉ በሙሉ መጥፎ አይደለም" የሚለው ማሪዮስ፣ ስልኩን በመጠቀም የስፓኒሽ ቋንቋ ጥሩ ተናጋሪ ለመሆኑ መቃረቡን ተናግሯል።
"በየቀኑ ስልክ ላይ ላለማሳለፍ ለራሴ ግብ አስቀምጫለሁ። ይህም ለውጥ እያመጣ ነው። ቀስ በቀስም በሌሎች ነገሮች እንደገና እየተደሰትኩ ነው። ማድረግ ይቻላል። እርግጠኛ ነኝ" ብሏል ማሪዮስ።















