አዲስ አበባ "የኦሮሚያ ክልል መቀመጫነቷ በሕገ መንግሥት እንዲደነገግ" ምክረ ሀሳብ ቀረበ

የአገራዊ ምክክር አርማ
ታትሟል
የንባብ ጊዜ: 3 ደቂቃ

በኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ጉባኤ ሲያከራክር በቆየው የአዲስ አበባ ጉዳይ ላይ የከተማዋ "የኦሮሚያ ክልል መቀመጫነት በፌደራል ሕግ መንግሥት እንዲሰፍር" የሚጠይቅ ምክረ ሃሳብ መቅረቡን ምንጮች ለቢቢሲ ተናገሩ።

ከተማዋ "ከኦሮሚያ ክልል ጋር የሚኖራትን ግንኙነት" በተመለከተ ግን ኮሚሽኑ የመጨረሻው የሚለውን ምክረ ሀሳብ ለመንግሥት እንደሚያቀርብ ማስታወቁን አንድ ምንጭ ገልጸዋል።

በስምንት አጀንዳዎች ላይ ከአንድ ወር ለሚበልጥ ጊዜ ሲካሄድ የነበረው የአገራዊ ምከክር ጉባኤ ዛሬ ቅዳሜ ነሐሴ 16/2018 ዓ.ም. የማጠቃለያ ሥነ ስርዓቱ ተካሂዷል።

ከማጠቃለያው አስቀድሞ ትናንት አርብ ነሐሴ 15 ከአመሻሽ 11፡30 ጀምሮ የመጨረሻዎቹ ምክረ ሀሳቦች አራት ሺህ ገደማው ተሳታፊዎች ላሉት ጉባኤ መቅረቡን አንድ ምንጭ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

የመጨረሻዎቹ ምክረ ሀሳቦች እንዲገለጹ ሐሙስ ዕለትም የጉባኤው ተሳታፊዎች ተሰብስበው የነበረ ቢሆንም በአዲስ አበባ ጉዳይ ላይ በተፈጠረው አለመግባባት ምክንያት "የመፍትሔ ሃሳብ" የሚያቀርብ ኮሚቴ እንዲቋቋም መደረጉ ይታወሳል።

ይህ ኮሚቴ ከ12ቱ ርዕሳነ መስተዳድሮች፣ ከሁለቱ ከንቲባዎች፣ ከሀገር ሽማግሌዎች እና ከባለሙያዎች የተውጣጣ ነው። ይህ ኮሚቴ ከትናንት ጠዋት ሲመክር እንደነበር ለቢቢሲ የተናገሩት ምንጭ፤ ዘጠኝ ሰዓት ተቀጥሮ የነበረው ጉባኤ በተያዘለት ሰዓት እንዳልጀመረ ጠቅሰዋል።

ጉባኤው ከተጀመረ በኋላ ምክረ ሀሳቦቹ በአጠናቃሪዎች አማካኝነት መቅረብ ከመጀመሩ አስቀድሞ በአዲስ አበባ ጉዳይ ላይ ተጨማሪ ሀሳብ እንደሚኖር መገለጹን አክለዋል።

"ከአጀንዳ አንድ ጀምሮ ምክረ ሀሳቦች ተራ በተራ መቅረብ ጀመሩ። አብዛኛው ምክረ ሀሳብ ከዚህ ቀደም 500 አባላት ባሉት ቡድን ላይ የቀረቡት ናቸው። ራሱ ነው የተደገመው። አንዳንድ አጀንዳዎች ላይ ግን ምክረ ሀሳብ እንደቀረበባቸው አስተውያለሁ" ሲሉ ምንጩ ተናግረዋል።

Skip podcast promotion and continue reading
የቢቢሲ አማርኛ ዩቲዩብ ቻናል

ዜና፣ ትንታኔ እና ታሪኮችን በምሥል እና በድምጽ ለማግኘት

ይህንን በመጫን ሰብስክራይብ ያድርጉ

End of podcast promotion

"የፌደራል ከተሞች" በሚለው ሰባተኛ አጀንዳ ውስጥ ለሚገኘው የአዲስ አበባ ጉዳይ ላይም "ለተወሰኑ የቃላት ለውጦች" ውጪ ሐሙስ በቀረበው ምክረ ሀሳብ ላይ "የተቀየረ ነገር" አለመኖሩንም አንስተዋል።

በአዲስ አበባ ጉዳይ ከቀረቡ ምክረ ሀሳቦች አንዱ አዲስ አበባ "ራሷን በራሷ የምታስተዳደር" እና "ለፌደራል መንግሥት ተጠሪ የሆነች" ከተማ መሆኗ እንዲቀጥል ነው። አዲስ አበባ ከኦሮሚያ ክልል ጋር የሚኖራትን ግንኙነት በተመለከተ ደግሞ በሕገ መንግሥቱ ላይ የተደነገገው "ልዩ ጥቅም" እንዲሻር ምክረ ሀሳብ ቀርቧል።

በምትኩም ኦሮሚያ እና አዲስ አበባ "በአስተዳደራዊ ጉዳዮች ላይ የጋራ ተጠቃሚነትን እንዲኖራቸው በሚያስችሉ ጉዳዮች ላይ የሚሰሩበት ዝርዝር የሕግ ማዕቀፍ ይቀመጥ" የሚል ምክረ ሀሳብ መቀመጡን ቢቢሲ ያነጋገራቸው ምንጭ አስረድተዋል።

የአዲስ አበባ "የጸጥታ መዋቅር ራሱን የቻለ እና ተጠሪነቱ ለከተማዋ አስተዳደር እንዲሆን" የሚለውም ከምክረ ሀሳቦቹ መካከል መሆኑን ጠቅሰዋል።

ዋና የክርክር ምንጭ በሆነው እና "አዲስ አበባ የኦሮሚያ ክልል መቀመጫነት በሕገ መንግሥቱ እውቅና እንዲሰጠው" የሚጠይቀው ጉዳይ ላይ ሁለት አማራጮች ቀርበዋል። ለዚህ ጉዳይ የቀረበው የመጀመሪያው አማራጭ የከተማዋ "የኦሮሚያ ክልል መቀመጫነት በሕገ መንግሥት እንዲሰፍር" የሚጠይቅ ነው።

ሁለተኛው ደግሞ እንደ የክልሎች ዋና ከተማዎች ያሉ ጉዳዮችን የተመለከተ ድንጋጌ በሕገ መንግሥቱ እንዲካተተት ይጠይቃል።

የፌደራል ከተሞችን ጨምሮ በሁሉም አጀንዳዎች ላይ የተጠናቀሩ ምክረ ሀሳቦች ከቀረቡ በኋላ ከምክትል ኮሚሽነሮች አንዱ በሆኑት ዶ/ር ዮናስ አዳዬ አለመግባባት በተፈጠረበት የአዲስ አበባ ጉዳይ ኮሚሽኑ ስለተከተለውን አካሄድ ገለጻ መስጠታቸውን ምንጩ ተናግረዋል።

እንደ ምንጩ ገለጻ፣ ዶ/ር ዮናስ መግባባት ባልተደረሰበት የአዲስ አበባ ጉዳይ ላይ መፍትሔ እንዲሰጥ የተቋቋመው ኮሚቴ ደረሰበት ድምዳሜ ለተሳታፊዎች ይፋ አድርገዋል። "የሽምግልና ኮሚቴው 'አዲስ አበባ የኦሮሚያ ክልል መቀመጫነቷ መረጋገጡ ተገቢ ነው' የሚለው ውሳኔ ለኮሚሽኑ አቅርቧል" ማለታቸውን አስረድተዋል።

አዲስ አበባ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

ቢቢሲ አፋን ኦሮሞ ያነገጋራቸው የአገራዊ ምክክር ምንጭ "አዲስ አበባ ከተማ የኦሮሚያ ክልል ዋና ከተማ መሆኗ በፌደራል ሕገ መንግሥቱ ውስጥ እንዲደነገግ" የሚጠይቅ ምክረ ሀሳብ መቅረቡን ገልጸዋል።

የኦሮሚያ ክልል ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ አቶ ሀይሉ አዱኛ በፌስቡክ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ ከቀረቡት ምክረ ሀሳቦች አንዱ፣ አዲስ አበባ የኦሮሚያ "ዋና ከተማ በመሆን የሕገ መንግሥት እውቅና እንዲያገኝ" የሚያደርግ መሆኑን ገልጸዋል።

ቢቢሲ አማርኛ ያነገጋራቸው ምንጭ እንደሚያስረዱት፣ የአዲስ አበባ እና ኦሮሚያ ክልል ግንኙነትን በተመለከተ ግን የምክክር ኮሚሽኑ "ጉዳዩን በድጋሚ ተመልክቶ የመጨረሻ ምክር ሀሳብ እንደሚያቀርብ" ይፋ ተደርጓል።

"ኮሚሽኑ በአዋጅ በተሰጠው የመጨረሻውን ምክረ ሀሳብ የማቅረብ ሥልጣን መሠረት ይህንን ሀሳብ ወስዶ፣ ሌላ ቡድን አቋቁሞ፣ ኮሚሽኑ ጉዳዩን ተመልክቶ ምክረ ሀሳቡን ለመንግሥት እንዲያቀርብ ተወስኗል" በሚል ገለጻ መሰጠቱን ተናግረዋል።

ትናንት የተካሄደው ጉባኤም በተመሳሳይ ቅሬታዎች ተነስተውበት እንደነበር ምንጮች ለቢቢሲ ተናግረዋል። አንድ ምንጭ እንደሚገልጹት ዶ/ር ዮናስ ከኮሚቴው የተሰጠውን ምክረ ሀሳብ በሚያቀርቡበት ሰዓት አዳራሹን ጥለው የወጡ ተመካካሪዎች ነበሩ። "ጭብጨባ እና ጩኸት" ይሰማ እንደነበረም አክለዋል።

ከነሐሴ 8/2018 ዓ.ም. ጀምሮ ሲካሄድ የቆየው አገራዊ ምክክር ጉባኤ ዛሬ ቅዳሜ ነሐሴ 16 ቀን የመዝጊያ ሥነ ሥርዓት ተደርጎለታል። የኢትዮጵያ ምክክር ኮሚሽን ከአንድ ወር በላይ በወሰደው ምክክር የቀረቡ ምክረ ሀሳቦችን በቀጣይ ለመንግሥት እንደሚያቀርብ ይጠበቃል።

በመዝጊያው ስነ ስርዓት ላይ ንግግር ያደረጉት ዋና ኮሚሽነሩ ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ "ብዙ ውሳኔዎችን አሳልፋችኋል። እነዚህ ውሳኔዎቻችሁ ወደየሚላኩበት ቦታ ይላካሉ" ብለዋል።