እስራኤል ዌስት ባንክን ለሁለት የሚከፍለውን ሰፈራ ለመገንባት ጨረታ አወጣች

ታትሟል
የንባብ ጊዜ: 2 ደቂቃ

የፍልስጤም በአገርነት የምትመሠረትበትን ማንኛውም ዕድል ለማጥፋት እየሞከረ ያለው የእስራኤል መንግሥት፤ በወረራ የተያዘው ዌስት ባንክ ስትራቴጂክ አካል በሆነ ስፍራ ላይ 1,200 ገደማ ቤቶችን ለመገንባት ጨረታ አወጣ።

በምሥራቅ እየሩሳሌም 'ኢ1' ተብሎ በሚጠራው ስፍራ ላይ ግንባታ ለማካሄድ የተያዘው ዕቅድ ለረጅም ጊዜ ዓለም አቀፍ ውግዘት ሲደርስበት ቆይቷል። በዓለም አቀፍ ሕግ መሠረት የእስራኤል ሰፈራዎች ሕገ ወጥ ናቸው።

ይህ ግንባታ ዌስት ባንክን ለሁለት የሚከፍል እና ምሥራቅ ኢየሩሳሌምን የሚነጥል ነው።

የዩናይትድ ኪንግደም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኤድ ሚሊባንድ ጨረታውን መውጣቱት "ተቀባይነት የሌለው እና አውዳሚ ድርጊት" ሲሉ ተቃውመውታል። እስራኤል "በአስአቸኳይ የኢ1 የግንባታ ዕቅዶችን ትግበራ እንድታቋርጥ እና የሰፈራ ማስፋፋትን በሙሉ እንድታቆም" ጠይቀዋል።

እስራኤል በአውሮፓውያኑ 1967 በተደረገው የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት ወቅት ዌስት ባንክ እና ምሥራቅ ኢየሩሳሌምን በወረራ ከያዘች ወዲህ 700 ሺህ አይሁዶች የሚኖሩባቸው 160 ገደማ ሰፈራዎችን ገንብታለች።

ሰፈራ የተገነባባቸው መሬቶች፣ ፍልስጤማውያን ወደፊት እንደምትመሠረት ተስፋ የሚያደርጓት አገር አካል እንዲሆኑ የሚፈልጓቸው ናቸው። ከእነዚህ ሰፈራዎች አጠገብ 3.3 ሚሊዮን ገደማ ፍልስጤማውያን ይኖራሉ።

ምንም እንኳ እጅግ ከፍተኛ ዓለም አቀፍ ተቃውሞ ቢኖርም፣ በተከታታይ የመጡ የእስራኤል መንግሥታት ሰፈራዎቹ እንዲስፋፉ ፈቅደዋል።

ሰፈራዎቹ በከፍተኛ መጠን የጨመሩት ግን ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታንያሁ በአውሮፓውያኑ 2022 ሰፈራዎቹን የሚደግፈው ቀኝ ክንፍ ጥምረት መሪ ሆነው ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ ነው። በመስከረም 2016 ዓ.ም. የገዛ ጦርነት ከተነሳ በኋላም ሰፈራዎቹ ተስፋፍተዋል።

እስራኤል በዓለም አቀፍ ጫና ምክንያት ለአስርት ዓመታት የ'ኢ1' ግንባታ ዕቅድን አዘግይታ ቆይታለች።

ይህ ዕቅድ ዌስት ባንክን በመክፈል፣ የሁለት አገርነት ተስፋን የሚያቀጭጭ እንደሆነ የእስራኤል አጋሮች እና ፍልስጤማውያን ይናገራሉ።

የአሁኑ የእስራኤል መንግሥት ግን የአገረ ፍልስጤም ሀሳብን "እንዲጠፋ" ለማድረግ ሲል ከአንድ ዓመት በፊት ግንባታው እንዲጀመር ፈቅዷል።

በአካባቢው የሚኖሩ ፍልስጤማውያን እና የእስራኤል የሰላም ቡድኖች ዕቅዱን ለማስቆም ለእስራኤል ፍርድ ቤት አቤቱታ አቅርበዋል። ይህ ቢሆንም ግን የአገሪቱ የቤት ልማት ሚኒስቴር እንዲገነቡ ከጸደቁት 3,401 ቤቶች ውስጥ የ1,234 ያህሉን ግንባታ ለማስጀመር ጨረታ አውጥቷል።

ዕቅዱ ይፋ በሆነበት ወቅት፣ አክራሪ ብሔርተኛ እና ሰፋሪ የሆኑት የፋይናንስ ሚኒስትሩ ቤዛሌል ስሞትሪች የአገረ ፍልስጤም ሀሳብ "እየጠፋ ነው" ሲሉ ተናግረዋል።

ጨረታው የሚያበቃው በጥቅምት ወር ከእስራኤል ጠቅላላ ምርጫ በጥቂት ቀናት በፊት ስለሆነ፣ ወደፊት የሚመጣ መንግሥትም ጨረታውን ለመቀልበስ አዳጋች ይሆንበታል።

የዩናይትድ ኪንግደም የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኤድ ሚሊባንድ ረቡዕ ምሽት ባወጡት መግለጫ፣ "ብሪታኒያን አታፈገፍግም፤ የሁለት አገርነት መፍትሄ መውደምንም አትቀበልም" ብለዋል።

"ዩኬ በኢ1 ዕቅድ ላይ ያላትን ተቃውሞ እና ለሁለት አገርነት መፍትሄ የምትሰጠው ድጋፍ በግል እና በይፋ ግልፅ ስታደርግ ቆይታለች" ያሉት ሚኒስትሩ፤ "ሁሉም ሰፈራዎች ያንን ተስፋ የሚጎዱ እና ግልፅ የዓለም አቀፍ ሕግ ጥሰት ናቸው" ሲሉ የአገሪቱን አቋም አሳውቀዋል።