በድሬዳዋ ከተማ ጉዳይ ላይ በሀገራዊ ምክክሩ ከምን ስምምነት ላይ ተደረሰ?

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
በሀገራዊው ምክክር ላይ የድሬዳዋ ከተማ በፌዴራል ከተሞች ጉዳይ ስር ምክክር ከተደረገባቸው ሁለት ከተሞች አንዱ ነው። ከኦሮሚያ እና ከሶማሌ ክልሎች በተወከሉ የምክክሩ አባላት መካከል ከፍተኛ የይገባኛል ክርክር እንደተደረገባት በምክክሩ ላይ የተሳተፉ ታማኝ ምንጭ ለቢቢሲ ተናግረዋል።
ይሁን እንጂ የአዲስ አበባ ከተማ ጉዳይ ሰፊ መነጋገሪያ መሆኑ፣ የድሬዳዋ ጉዳይ ብዙም ትኩረት እንዳያገኝ አድርጎታል።
እስካሁን ያለው የከተማዋ አስተዳደር ምን ይመስላል?
የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር በሥራ ላይ ባለው የኢትዮጵያ ሕገ-መንግሥት አይታወቅም።
ከተማዋ የሶማሌ እና የኦሮሚያ ክልሎች የይገባኛል ጥያቄ የሚያነሱባት በመሆኑ፣ በሕግ መሠረት የመጨረሻ ውሳኔ እስኪያገኝ በሚል ከ1985 ዓ.ም. ጀምሮ ለፌደራል መንግሥት ተጠሪ ሆና ስትተዳደር ቆይታለች።
የከተማዋን አስተዳደር እና ለፌዴራል መንግሥት ተጠሪ ሆና መዋቀሯን የሚደነግገው ሕጋዊ ሰነድ፣ ማለትም "የድሬዳዋ አስተዳደር ቻርተር አዋጅ" አዋጅ ቁጥር 416/1996 የተዘጋጀው ደግሞ በ1996 ዓ.ም. ነው።
ቻርተሩ የተዘጋጀው ዘላቂ የሆነ ሕጋዊ መፍትሔ እስኪገኝ ድረስ የድሬዳዋ ከተማ ለጊዜው እራሱን በራሱ የሚያስተዳድርበት ሕጋዊ መሠረት እንዲኖረው ለማስቻል ስለመሆኑ በአዋጁ መግቢያ ላይ ተጠቅሷል።
ይህ ቻርተር በተዘጋጀ ማግስት በቀጣዩ ዓመት ከተካሔደው የ1997 ዓ.ም. ምርጫ በኋላ የከተማዋ አስተዳደር የተለየ ቅርጽ ይዞ ቀጥሏል።
ይኸውም 40-40-20 የሥልጣን ክፍፍል ያካተተ ሲሆን እስከ አሁንም ድረስ በሥራ ላይ ያለ ነው።
በቻርተሩ ውስጥ በግልፅ ባልተጠቀሰው በዚህ የሥልጣን ክፍፍል መሠረት፣ የኦሮሞ እና የሶማሌ ተወላጆች 40፣ 40 በመቶውን የከተማ አስተዳደር ምክር ቤት እና የካቢኔ ቦታ ሲከፋፈሉ፣ የተቀረው 20 በመቶ በከተማዋ ለሚኖሩ ሌሎች ብሔረሰቦች እንዲሆን ተደርጓል።
የከንቲባነቱን ቦታ ደግሞ የሁለቱ ብሔሮች ተወላጆች ተራ በተራ እየተፈራረቁ ይይዛሉ። ይህ "በፖለቲካዊ ውሳኔ" የተተገበረው እና ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ የዘለቀው የሥልጣን ክፍፍል በብዙዎች ዘንድ ትችት ሲሰነዘርበት ቆይቷል።
በአስተዳደሩ ላይ የሚነሱ ቅሬታዎች
ይህን አካሔድ የሚተቹ የድሬዳዋ ከተማ ነዋሪዎችም ቁጥር ጥቂት የሚባል አይደለም። ከምሁራን በተጨማሪ አስተያየታቸውን የሰጡን ሦስት የከተማዋ ነዋሪዎችም የነበረውን የከተማዋ አስተዳደር አወቃቀርን የሚተቹ ናቸው።
በሥልጣን ክፍፍሉ ደስተኛ አለመሆናቸውን ማንነታቸው እንዲታወቅ ያልፈለጉት አስተያየት ሰጪዎቹ ለቢቢሲ ተናግረዋል። ይህ አካሔድ "የከተማዋ እድገት ወደ ኋላ እንዲቀር እና የመልካም አስተዳደር ችግር እንዲኖር ከፍተኛ ሚና አለው" ይላሉ አንዱ ምክንያታቸውን ሲያስረዱ።
የሥልጣን ክፍፍሉ "የከተማዋን ነዋሪዎች እና ተወላጆች ያገለለ ነው" ሲሉም ይተቻሉ። ነገር ግን "ዋናው የምንፈልገው ሰላማችንን ነው" በማለት ይህ ሁኔታ ብዙም እንደማያሳስባቸው አንስተዋል።
ካነጋገርናቸው ውስጥ ነዋሪዎች መካከል ሌላኛው ግለሰብ ለ40 ዓመታት ያህል በድሬዳዋ የኖሩ ናቸው። ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በከተማዋ እየተስተዋለ ላለው አለመረጋጋት ያለውን የአስተዳደሩን አወቃቀር ተጠያቂ ያደርጋሉ።
የሰላም እና የፍቅር ተምሳሌት ተደርጋ የምትወሰደው "የበረሃዋ ገነት" ድሬዳዋ፣ ከ2008 ዓ.ም. ወዲህ "አዲስ ሆናብኛለች" ይላሉ። በ2008 ዓ.ም ተከስቶ የነበረው እና ለተወሰነ ጊዜ አልፎ አልፎ የተስተዋለው "የብሔር እና የሃይማኖት ይዘት" እንዳለው የገለፁት ግጭት በ40 ዓመታት የከተማዋ ቆይታቸው የማያውቁት መሆኑን ተናግረዋል።
በአሁኑ ወቅት ድሬዳዋ የተረጋጋች እና ሰላማዊ ከተማ እንደሆነች የሚገልፁት ግለሰቡ "እሱ ሳይናጋ እንዲቀጥል ነው ፍላጎቴ" ብለዋል። ነገር ግን "በማንኛውም ጊዜ ግጭት ሊፈጠር ይችላል" የሚል ስጋት እንዳላቸውም አልሸሸጉም።

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
በድሬዳዋ ጉዳይ ላይ ምን ስምምነት ተደረሰ?
በሀገራዊ ምክክሩ ላይ "የፌዴራል ከተሞች" በሚል የቀረበው አጀንዳ ትኩረት የሚያደርገው በአዲስ አበባ እና በድሬዳዋ ከተሞች ላይ ነው።
ድሬዳዋ በአጀንዳነት የተካተተችበት ምክንያት፣ የተለያዩ ብሔሮችና ብሔረሰቦች የሚኖሩባት እና ብዙ ጥያቄዎች የሚነሱባት በመሆኑ እንደሆነ የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ገልጿል።
የከተማዋ ጉዳይ በአጀንዳነት እንዲያዝ ከነዋሪዎቿ በተጨማሪ በሌሎችም አካባቢዎች ነዋሪዎች በስፋት መጠየቁን ለቢቢሲ ተናገሩት የኮሚሽኑ ዋና ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ፣ በመሆኑም "ዘላቂ የውሳኔ ምክረሃሳብ ለተግባሪ አካላት ቢቀርብ በሚል" ከአዲስ አበባ ጋር በአጀንዳነት እንድትቀርብ መወሰኑን አስታውሰዋል።
የድሬዳዋ ጉዳይ የአዲስ አበባን ያህል ባይሆንም "ከፍተኛ ጭቅጭቅ እና ክርክር" የተደረገበት ስለመሆኑ፣ በፌዴራል ከተሞች አጀንዳ ላይ በንቃት የተሳተፉ ማንነታቸው እንዲታወቅ ያልፈለጉ ግለሰብ ለቢቢሲ አስረድተዋል።
"በድሬዳዋ ላይ ብዙም ልዩነት የለም ከሞላ ጎደል በስምምነት አልቋል" ያሉት ምንጫችን፣ ነገር ግን የኦሮሚያ ክልል እና የሶማሌ ክልል ተወካዮች "የእኛ ነች" የሚል የጎላ ሙግት አቅርበው እንደነበር አብራርተዋል።
"የኦሮሚያ ተወካዮች 'አፍረንቃሎ' የሚባል የኦሮሞ ብሔር ጎሳ መኖሪያ አካባቢ ስለነበረ ለእኛ ይገባል የሚል መከራከሪያ አቅርበው ነበር። ሶማሌዎቹ ደግሞ ኢሳ እና ጉርጉራ የሚባል የእኛ ብሔረሰብ ጎሳ አባላት የሚኖሩበት ነበረ ብለው ተከራክረዋል" ብለዋል እኚሁ የቢቢሲ ምንጭ።
የነበረውን ሁኔታ ሲገልፁም "በጣም የተካረረ ነበረ" በማለት ነው። ይህ "ተካርሮ" የነበረው የሁለቱ ክልሎች ተወካዮች ክርክር እልባት ያገኘው፣ የብልጽግና ፓርቲ ባሳየው አቋም መሆኑን ጠቅሰዋል።
ገዢው ፓርቲ አባላቱን በየጊዜው እያገኘ በማወያየት መመሪያ ሲሰጥ እንደነበረ "መረጃ አለኝ" ያሉት የምክክሩ ተሳታፊ፣ በዚህም "አዲስ ስምምነት ላይ ደረሱ" ብለዋል። ይህን ተከትሎ "ብዙ ክርክር ሲደረግበት ነበር" ያሉት የከተማዋ ጉዳይ በስተመጨረሻ በ250ው ቡድን ላይ ወደ ስምምነት መምጣቱን ተናግረዋል።
በዚህም መሠረት "ድሬዳዋ ከተማ ተጠሪነቷ ለፌዴራሉ የሆነ፣ በነዋሪዎቿ የምትተዳደር፣ የራሷ ፍርድ ቤት እና ፖሊስ ያላት፣ በልማድ ይሠራበት የነበረው 40 በመቶ ከኦሮሞ፣ 40 በመቶ ከሶማሌ እና 20 በመቶ ከነዋሪዎች የተወከሉ እንዲያስተዳድሯት የሚለው ቀርቶ፣ በነዋሪዎች የተመረጠ አስተዳደር ይምራት የሚል መግባባት ላይ ተደርሷል" ብለዋል። በድሬዳዋ ላይ የተደረሰው ይህ ስምምነት ወደ 500ው ቡድን "ያለልዩነት በስምምነት ያለፈ አጀንዳ ነው" ሲሉም አክለዋል።
ስለዚህ ስምምነት ያነሳንላቸው ለ40 ዓመታት ያህል በድሬዳዋ የኖሩት አስተያየት ሰጪ፣ ስምምነቱ በምክክር ጉባዔው ፀድቆ ቢተገበር ምኞታቸው ነው። ነገር ግን ቢፀድቅ እንኳን ይተገበራል የሚል እምነት የላቸውም።
"በምን ዕድላችን!" የሚሉት ግለሰቡ፣ ነባሩ አካሔድ "በፍፁም ይቀራል ብዬ አላስብም" ሲሉ ስጋታቸውን ገልፀዋል። ለዚህም ምክንያታቸውን ሲጠቅሱ "እነርሱ የሥልጣን ሽሚያ ላይ ነው ትኩረት የሚያደርጉት" ብለዋል።
"በሥራው የምንመርጠው መሪ ማግኘት ብንችል ቢያንስ ለውጥ ሊያመጣ ይችላል ብዬ አስባለሁ፤ ዋናው የምንፈልገው ሰላም እና የኑሮ ውድነትን ማቅለል ላይ የሚሠራ ነው" ሲሉ አስተያየታቸው አሳርገዋል።
በአሁኑ ወቅት ምክክሩ ወደ መጠናቀቂያው መቅረቡን ኮሚሽኑ ገልጿል። ከስምንቱ የሥራ ቡድኖች የተውጣጡ 15 የአጀንዳ ምክረ-ሃሳብ አጠናቃሪዎች ያጠናቀሩትን የአጀንዳ ሃሳብ ለየሥራ ቡድናቸው አቅርበዋል።
500 አባላት ካሏቸው ስምንት የሥራ ቡድኖች ከእያንዳንዳቸው የተውታጡ 15፣ በድምሩ 120 አባላት ያሉት ቡድን ካለፈው ሐሙስ ጀምሮ በሁሉም የሥራ ቡድኖች የተነሱ የአጀንዳ ምክረ-ሃሳቦችን በማዳመጥ ወጥ የሆነ የምክረ-ሃሳብ ሰነድ ማቅረባቸውንም ሰኞ ነሐሴ 11/2018 ዓ.ም. ገልጿል።
የተደራጁ አጀንዳዎች የቀረቡላቸው ስምንቱ የሥራ ቡድኖች ሃሳብ እና አስተያየት አክለው የመጨረሻው ሰነድ እንዲዘጋጅ ለአደራጅ ቡድኖቹ መመለሳቸውንም አስታውቋል።















