ትራምፕ ለኢራን ጦርነት ዲፕሎማሲያዊ መፍትሄ እንዲፈልጉ ቱርክ ጠየቀች

የፎቶው ባለመብት, Reuters
የቱርክ ፕሬዚዳንት ረሲብ ጣይብ ኤርዶዋን ከአሜሪካው አቻቸው ዶናልድ ትራምፕ ጋር በስልክ ባደረጉት ውይይት ወቅት ለኢራን ጦርነት ዲፕሎማሲያዊ መፍትሄ እንዲፈልጉ ጠየቁ።
የሁለቱ መሪዎች የስልክ ውይይት የተካሄደው ትናንት ሰኞ ነሐሴ 11/2018 ዓ.ም. ምሽት መሆኑ ተገልጿል።
በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የተፈረመው እና ለ60 ቀናት የሚቆየው የመግባቢያ ስምምነት እያበቃ ሲሆን ስለመቀጠሉ እስካሁን ድረስ የታወቀ ነገር የለም።
የቱርክ ፕሬዝዳንት ጽህፈት ቤት ባወጣው መግለጫ “ፕሬዝዳንት ኤርዶዋን በኢራን እና በአሜሪካ መካከል ውጥረት ባለበት ወቅት ዲፕሎማሲን በተሻለ ሁኔታ መጠቀም አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል፤ ንግግሮች እንደሚቀጥሉ ያላቸውን ተስፋ በመግለጽም ቱርክ ለሰላም የሚደረጉ ጥረቶችን መደገፏን እንደምትቀጥል አስታውቀዋል” ብሏል።
ኤርዶዋን በተጨማሪም የጋዛ ስምምነት ወደ ሁለተኛው ምዕራፍ ለማሸጋገር ጥረቶች በሚደረጉበት ወቅት፣ እስራኤል በፍልስጤማውያን ላይ የምታደርገው ጥቃት ተባብሶ መቀጠሉ ስጋት እንደፈጠረባቸው ኤርዶዋን መግለጻቸውን መግለጫው አመልክቷል።
የኔቶ አባል የሆነችው እና ከኢራን ጋር ድንበር የምትጋራው ቱርክ በዚህ ወር መጀመርያ ላይ ከሳዑዲ አረቢያ እና ፓኪስታን ጋር ወታደራዊ ስምምነት ተፈራርማለች።
በስምምነቱ መሠረት በአንዱ አገር ላይ የሚፈጸም ማንኛውም ጥቃት በሌላኛው አገር ላይ እንደተፈጸመ ተደርጎ ይቆጠራል።
ፕሬዚዳንት ትራምፕ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ስምምነቱን አድንቀው “ይህ ስምምነት የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት እንዴት እየተቀራረቡ እንደሆነ፣ እንዲሁም አገራት በመጨረሻ ራሳቸውን በይበልጥ ውጤታማ በሆነ መንገድ መከላከል የሚያስችላቸውን አቅም እንዴት እንደሚያገኙ ያሳያል” ብለዋል።
በስልክ ውይይታቸው ወቅት፣ ኤርዶዋን ስምምነቱ “የቀጣናውን መረጋጋትና ደኅንነት ለማረጋገጥ ያለመ ጠንካራ አቋምን” የሚያንጸባርቅ መሆኑን ለትራምፕ ገልጸዋል።










