ቀጥታ, ትራምፕ አጋራቸው የሆነችው ኦማንን ለኢራን ስምምነት “እንቅፋት ከሆነች” እንደሚደበድቡ አስጠነቀቁ

ትራምፕ የአሜሪካ አጋር የሆነችው ኦማን ከኢራን ጋር ባለው ንግግር ጣልቃ የምትገባ ከሆነ እንደሚደበድቡ መዛታቸውን ፎክስ ኒውስ ዘገበ። አሜሪካ እና ኦማን የሆርሙዝ ወሽመጥን ለማስከፈት ከቴህራን ጋር በተናጠል እየተደራደሩ ነው።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ትራምፕ ለኢራን ጦርነት ዲፕሎማሲያዊ መፍትሄ እንዲፈልጉ ቱርክ ጠየቀች

    የቱርክ ፕሬዚዳንት ረሲብ ጣይብ ኤርዶዋን

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የቱርክ ፕሬዚዳንት ረሲብ ጣይብ ኤርዶዋን ከአሜሪካው አቻቸው ዶናልድ ትራምፕ ጋር በስልክ ባደረጉት ውይይት ወቅት ለኢራን ጦርነት ዲፕሎማሲያዊ መፍትሄ እንዲፈልጉ ጠየቁ።

    የሁለቱ መሪዎች የስልክ ውይይት የተካሄደው ትናንት ሰኞ ነሐሴ 11/2018 ዓ.ም. ምሽት መሆኑ ተገልጿል።

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የተፈረመው እና ለ60 ቀናት የሚቆየው የመግባቢያ ስምምነት እያበቃ ሲሆን ስለመቀጠሉ እስካሁን ድረስ የታወቀ ነገር የለም።

    የቱርክ ፕሬዝዳንት ጽህፈት ቤት ባወጣው መግለጫ “ፕሬዝዳንት ኤርዶዋን በኢራን እና በአሜሪካ መካከል ውጥረት ባለበት ወቅት ዲፕሎማሲን በተሻለ ሁኔታ መጠቀም አስፈላጊ መሆኑን ገልጸዋል፤ ንግግሮች እንደሚቀጥሉ ያላቸውን ተስፋ በመግለጽም ቱርክ ለሰላም የሚደረጉ ጥረቶችን መደገፏን እንደምትቀጥል አስታውቀዋል” ብሏል።

    ኤርዶዋን በተጨማሪም የጋዛ ስምምነት ወደ ሁለተኛው ምዕራፍ ለማሸጋገር ጥረቶች በሚደረጉበት ወቅት፣ እስራኤል በፍልስጤማውያን ላይ የምታደርገው ጥቃት ተባብሶ መቀጠሉ ስጋት እንደፈጠረባቸው ኤርዶዋን መግለጻቸውን መግለጫው አመልክቷል።

    የኔቶ አባል የሆነችው እና ከኢራን ጋር ድንበር የምትጋራው ቱርክ በዚህ ወር መጀመርያ ላይ ከሳዑዲ አረቢያ እና ፓኪስታን ጋር ወታደራዊ ስምምነት ተፈራርማለች።

    በስምምነቱ መሠረት በአንዱ አገር ላይ የሚፈጸም ማንኛውም ጥቃት በሌላኛው አገር ላይ እንደተፈጸመ ተደርጎ ይቆጠራል።

    ፕሬዚዳንት ትራምፕ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ስምምነቱን አድንቀው “ይህ ስምምነት የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት እንዴት እየተቀራረቡ እንደሆነ፣ እንዲሁም አገራት በመጨረሻ ራሳቸውን በይበልጥ ውጤታማ በሆነ መንገድ መከላከል የሚያስችላቸውን አቅም እንዴት እንደሚያገኙ ያሳያል” ብለዋል።

    በስልክ ውይይታቸው ወቅት፣ ኤርዶዋን ስምምነቱ “የቀጣናውን መረጋጋትና ደኅንነት ለማረጋገጥ ያለመ ጠንካራ አቋምን” የሚያንጸባርቅ መሆኑን ለትራምፕ ገልጸዋል።

  2. በስሪ ላንካ ከአንድ ሰው የሽንት ፊኛ ውስጥ 3 ኪሎ ግራም የሚመዝን ጠጠር ወጣ

    ሐኪሞች ጠጠሩን ካወጡ በኋላ ቀዶ ሕክምናውን ሲያደርጉ፣ ፊት ለፊት ጠጠሩን በጨርቅ የያዘ የጤና ባለሙያ ይታያል

    የፎቶው ባለመብት, Trincomalee General Hospital

    የምስሉ መግለጫ, በስሪ ላንካ የሚገኙ የሕክምና ባለሙያዎች ከአንድ ታማሚ አዲስ የተወለደ ሕጻን የሚያክል ጠጠር ማስወገዳቸውን ተናግረዋል

    የስሪ ላንካ ዶክተሮች 3.1 ኪሎ ግራም የሚመዝን የሽንት ፊኛ ጠጠር ማወጣታቸውን ገለጹ።

    ከአንድ ሰው ይህንን ያህል ክብደት ያለው ጠጠር ሲወጣ ይህ የመጀመርያው ነው ተብሎም ይታመናል።

    ለሕመምተኛው ቀዶ ሕክምናው የተከናወነው ባለፈው ሳምንት ትሪንኮማሌ በተባለ ሆስፒታል ውስጥ ነው።

    የ55 ዓመቱ ሕመምተኛ ወደ ሆስፒታል የገባው ስትሮክ ካጋጠመው በኋላ መሆኑ ተገልጿል።

    ግለሰቡ ሕክምና እየተደረገለት እያለ ለመሽናት ሲቸገር የተመለከቱት ባለሙያዎች ተጨማሪ ምርመራ ሲያደርጉለት በሽንት ፊኛው ውስጥ ጠጠር መኖሩን መረዳታቸውን ገልጸዋል።

    ከቀዶ ሕክምናው በኋላ የወጣው ጠጠር ሲመዘን የአንድ ጨቅላ ሕጻን ኪሎን እንደሚያክል እና የሰጎን እንቁላልን የሚመስል መሆኑን ጨምረው አስታውቀዋል።

    "ባሉ መረጃዎች መሠረት፣ እስካሁን ድረስ በቀዶ ሕክምና መውጣቱ ከተመዘገበ ትልቁ የፊኛ ጠጠር መካከል ነው" ሲሉ ቀዶ ሕክምናውን የመሩት ዶክተር ፕራሃላሃን ባላሪሽናን ለቢቢሲ ሲንሃላ ተናግረዋል።

    ታካሚው "በጣም ጥሩ ጤንነት" ላይ እንደሚገኝም አክለዋል።

    የሰጎን እንቁላል የሚመስለው የፊኛ ጠጠር 17 ሴንቲ ሜትር ያህል ይረዝማል

    የፎቶው ባለመብት, Trincomalee General Hospital

    የምስሉ መግለጫ, የሰጎን እንቁላል የሚመስለው የፊኛ ጠጠር 17 ሴንቲሜትር ያህል ይረዝማል

    ግለሰቡ አሁንም በሆስፒታል ውስጥ የሚገኝ ሲሆን ለሌሎች የጤና እክሎቹ ሕክምና እየተከታተለ መሆኑን ዶክተሮች ተናግረዋል።

    ዶ/ር ባላክራሽናን አክለውም የሽንት ፊኛ ጠጠሩ፣ በታካሚው ፊኛ ውስጥ ከአምስት እስከ 10 ዓመታት ያህል የቆየ ሊሆን ይችላል ብለዋል።

    የሽንት ፊኛ ጠጠር በሽንት ውስጥ የሚገኙ ማዕድናት በፊኛ ውስጥ እርስ በእርሳቸው ሲጠባበቁ የሚፈጠር ሲሆን ሽንትን ሙሉ በሙሉ ማፍሰስ እንዳይቻል ያደርጋል።

    ትንንሽ አሸዋ መሰል ጠጠሮች በራሳቸው በሽንት ቱቦ በኩል አልፈው ይወገዳሉ።

    ከ4 ሴንቲ ሜትር በላይ ከፍ ያለ ጠጠር ግን ግዙፍ እንደሆነ ይቆጠራል።

    እአአ በ2003 በብራዚል ከአንድ ታካሚ ትልቁ የፊኛ ጠጠር መወገዱ በዓለም ድንቃ ድንቅ መዝገብ ላይ ሰፍሮ ይገኛል።

    በወቅቱ ከታካሚው የወጣው ጠጠር ክብደቱ 1.9 ኪ.ግ እንዲሁም ርዝመቱ 17.9 ሴ.ሜ መሆኑ ተመዝግቧል።

    ባለፈው ሳምንት በሲሪላንካ የተወገደው የፊኛ ጠጠርም 17 ሴ.ሜ ርዝመት አለው።

  3. በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ለማለፍ የሞከረ ነዳጅ ጫኝ መርከብ ምንነቱ ባልታወቀ ተወንጫፊ ተመታ

    ነዳጅ ጫኝ መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ማክሰኞ ማለዳ በሆርሙዝ በኩል ለማለፍ የሞከረ የነዳጅ ጫኝ መርከብ ምንነቱ ባልታወቀ ተወንጫፊ መመታቱን የዩናይትድ ኪንግደም ባሕር ትራንስፖርት አስታወቀ።

    ዩኬኤምቲኦ ባወጣው መግለጫ ”የኩባንያው የደኅንነት ባለሙያ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ለማለፍ ሲሞክር መርከቡ ባልታወቀ ተወንጫፊ መመታቱን አስታውቋል። በጥቃቱ የመርከቡ ሞተር የተመታ ሲሆን ሠራተኞችም ላይ ጉዳት ደርሷል” ብሏል።

    የመርከቧ ቀሪ ሠራተኞች በኦማን የባሕር ዳርቻ ጠባቂዎች ድጋፍ እየተደረገላቸው መሆኑን ጨምሮ አስታውቋል።

    ባለሥልጣናት ክስተቱን ለማጣራት እየሞሩ እንደሚገኙ የተገለጸ ሲሆን በጥቃቱ አካባቢ ላይ ስለደረሰ ተጨማሪ ጉዳት ምንም የተባለ ነገር የለም።

    ዩኬኤምቲኦ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚያልፉ የነዳጅ መርከቦች ጥንቃቄ እንዲያደርጉ እና አጠራጣሪ ነገር ሲመለከቱ እንዲያሳውቁ መክሯል።

    የአሜሪካ እና ኢራን ጦርነት ከተቀሰቀሰ ወዲህ የሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ያለው ውጥረት ተጠናክሯል።

    ኢራን ወሽመጡን ሙሉ በሙሉ መዝጋቷን ተከትሎ የዓለም የነዳጅ አቅርቦት ተስተጓጉሏል።

    ዋሺንግተን እና ቴህራን በሚያደርጉት ንግግር ወሽመጡን ዳግም ማስከፈት ዋነኛ አጀንዳ ነው።

  4. ትራምፕ፤ ኦማን ለኢራን ስምምነት “እንቅፋት ከሆነች” እንደሚያጠቋት አስጠነቀቁ

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ትራምፕ የአሜሪካ አጋር የሆነችው ኦማን ከኢራን ጋር ባለው ንግግር ጣልቃ የምትገባ ከሆነ ጥቃት እንደሚፈፅሙባት መዛታቸውን ፎክስ ኒውስ ዘገበ።

    አሜሪካ እና ኦማን የሆርሙዝ ወሽመጥን ለማስከፈት ከቴህራን ጋር በተናጠል እየተደራደሩ ነው።

    አሜሪካ ኢራን ላይ ጦርነት ከከፈተች ጊዜ ጀምሮ የዓለም አንድ አምስተኛ የነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ መጓጓዣ የሆነው ወሽመጥ ተዘግቷል።

    ፎክስ ኒውስ እንደዘገበው ትራምፕ ኦማንን ያስጠነቀቁት በስልክ በሰጡት ቃለ ምልልስ ወቅት ነው።

    የኢራን ባለሥልጣናት ከኦማን ጋር የሚያደርጉትን ድርድር እያጠናቀቁ እንደሆነ ተናግረው ነበር።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ በአሜሪካ እና ኢራን መካከል ለስልሳ ቀናት የተፈረመው የተኩስ አቁም መግባቢያ ሰነድ ጊዜው በመጠናቀቅ ላይ ይገኛል።

    ሰኞ እለት ትራምፕ በኦቫል ኦፊስ በሰጡት መገለጫ ቢቢሲ የመግባቢያ ሰነዱ እንዲራዘም ይፈልጉ እንደሆን ጠይቆ “አልፈልግም” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል የሚደረገው ንግግር በዋናነት የሚያተኩረው የሆርሙዝ ወሽመጥን ማስከፈት ላይ ነው።

    ኦማን በወሽመጡ ደቡባዊ ክፍል የምትዋሰን ሲሆን በግጭቱ ውስጥ ገለልተኛ ወገን መሆኗን ስትገልጽ ቆይታለች።

    ይሁን እንጂ ኢራን ተደጋጋሚ ጥቃት የፈጸመችባት ሲሆን አሁን ወሽመጡ እንዲከፈት በሚደረገው ድርድር ውስጥ ቁልፍ ሚና እየተጫወተች ትገኛለች።

    ዋሺንግተን ይህ የመርከቦች መተላለፊያ እንዲከፈት የራሷን ጥረት እያደረገች ትገኛለች።

    ፎክስ ኒውስ ትራምፕ “ኦማን ጣልቃ የምትገባ ከሆነ ከባድ ድብደባ ይደርስባታል” ማለታቸውን ዘግቧል።

    ትራምፕ ጣልቃ መግባት ሲሉ ምን ምን እንደሚያካትት ግልጽ አይደለም።

    በዚሁ ቃለ ምልልሳቸው ላይ አሜሪካ በኢራን ጦር፣ ምጣኔ ሃብት እና ፖለቲካ ውስጥ ወሳኝ ከሆነው ኃይል ከሆነው ከእስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ጋር በእጅ አዙር ግንኙነት እንዳላቸው ተናግረዋል።

    የእስላማዊ አብዮታዊ ዘቡ ቃል አቀባይ የትራምፕን ንግግር አስተባብሏል።

    ቃል አቀባዩ ለኢራን የዜና ወኪል ታስኒም ኒውስ "በአብዮታዊ ዘቡ ባለሥልጣናት እና በአሜሪካውያን መካከል ምንም ዓይነት ውይይት አልተደረገም፤ እናም ይህ የትራምፕ ውሸት በጦርነቱ ሽንፈት እና ተስፋ መቁረጥ ሰበብ የመጣ ግራ መጋባት እና ቅዠት ምክንያት የተፈጠረ ተስፋ መቁረጥ ብቻ ነው" ብለዋል።

    ትራምፕ ኦማን ላይ ዛቻውን የሰነዘሩት ኢራን ሁለቱ አገራት በወሽመጡ መርከቦች ማለፍ እንዲችሉ ስምምነት ላይ መድረሳቸውን ከተናገረች ከጥቂት ሰዓታት በኋላ ነው።

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ ለጋዜጠኞች "የመጓጓዣ መስመሩን ካርታ በተመለከተ መግባባት ላይ ተደርሷል" ብለዋል።

    ሁለቱም ወገኖች የጋራ መግለጫ ከማውጣታቸው በፊት ዝርዝር ጉዳዮችን እንደሚያጠናቅቁ ተናግረዋል። ኦማን ቀደም ሲል ውይይቱ በአዎንታዊ መልኩ እየሄደ መሆኑን ገልጻ ነበር።

    በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ፣ ወሽመጡ ዳግም ሙሉ በሙሉ እንዲከፈት አሜሪካ የመግባቢያ ሰነዱን በመጣሷ ካሳ መክፈሏ ላይ ይወሰናል ብለው ነበር።

    ሮይተርስ አንድ የኢራን ባለሥልጣንን ጠቅሶ ቴህራን በባሕረ ሰላጤው ውስጥ ከሚጓዙ የጭነት መርከቦች ከ5 በመቶ እስከ 7 በመቶ የሚደርስ ክፍያ እንደምትጠብቅ ዘግቧል።

  5. የትራምፕ ልዑክ ከሐማስ አመራሮች ጋር ከተገናኙ በኋላ ከኔታንያሁ ጋር ተወያዩ

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የመካከለኛው ምሥራቅ ልዑክ ጃሬድ ኩሽነር

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    የምስሉ መግለጫ, የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የመካከለኛው ምሥራቅ ልዑክ ጃሬድ ኩሽነር

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ የመካከለኛው ምሥራቅ ልዑክ ጃሬድ ኩሽነር ከእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሀ ጋር መገናኘታቸውን ቃል አቀባዩ ለቢቢሲ ተናገሩ።

    ኩሽነር እስራኤል የደረሱት ከሐማስ ጋር ከተነጋገሩ በኋላ ትናንት ምሽት ነው።

    የትራምፕ የሰላም ቦርድ ባለፈው ወር በጋዛ ውስጥ ሐማስን እና ሌሎች የታጠቁ ቡድኖችን "ሙሉ በሙሉ ትጥቅ ለማስፈታት" ስምምነት ላይ ከደረሰ በኋላ እስራኤል ባለ 15 ነጥቡን የሰላም ዕቅድ ውድቅ አድርጋለች።

    የሰላም ዕቅዱ የእስራኤል ወታደሮች እንዲወጡ እና ጋዛ በአዲስ የሲቪል አስተዳደር ስር ዳግም እንድትገነባ ይጠይቃል።

    ስምንት ሙስሊም አገራት ትናንት እሁድ ባወጡት መግለጫ እስራኤል ዕቅዱን ውድቅ ማድረጓን ኮንነዋል።

    ትራምፕ በጋዛ ሰላም ለማስፈን ታስቦ የተቋቋመውን የሰላም ቦርድን የሚመሩ ሲሆን፣ በኋላ ላይ በዓለም ዙሪያ የሚከሰቱ ግጭቶችን መፍታት እንደሚያካትት ተገልጿል።

    እሁድ ዕለት አንድ የፍልስጤም ባለሥልጣን ለቢቢሲ እንደተናገሩት የትራምፕ ልዑክ በግብፅ የሐማስ አዲሱ መሪ ካሊል አል-ሃይያ የሚመራውን ልዑክ አግኝተው ነበር።

    ሃማስ ባወጣው መግለጫ፣ በኋላ ላይ አስታራቂዎችን እና የሰላም ቦርዱን እስራኤል ለቀጣዮቹ እርምጃዎች የመንገድ ካርታውን እንድታፀድቅ "እንዲያስገድዱ" ጥሪ አቅርቧል።

    ሐማስ በኋላ ላይ ባወጣው መግለጫ አደራዳሪዎች እና የሰላም ቦርዱ እስራኤል ለቀጣዩ እርምጃ ፍኖተ ካርታውን እንድታጸድቅ “እንዲያስገድዱ” ጠይቋል።

    ብዙ እስራኤላውያንም ሐማስ ትጥቅ ለመፍታት ዝግጁ መሆኑ ላይ ጥርጣሬ አላቸው።

    ኩሽነር ከሃይያ ጋር ያደረጉት ስብሰባ ባለፈው ዓመት በጋዛ ሰርጥ የተኩስ አቁም እንዲኖር ከተደረገው ስምምነት ወዲህ የመጀመሪያው እንደሆነ ይታመናል።

  6. ኢራን ሁለት የፈረንሳይ ኤምባሲ ሠራተኞች ወደ አገሯ እንዳይገቡ አገደች

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ኢራን ባለፈው ወር በዲፕሎማሲ እሰጥ አገባ ውስጥ የተሳተፉ የፈረንሳይ ኤምባሲ ሁለት ሠራተኞች ወደ አገሯ እንዳይገቡ መከልከሏን አስታወቀች።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ እንደተናገሩት ሁለት የቪየና ኮንቬንሽንን የጣሱ የፈረንሳይ ኤምባሲ ሠራተኞች መታገዳቸውን አስታውቀዋል።

    ባጋይ “እነዚህ ግለሰቦች የሲቪል ማኅበረሰብን ከመደገፍ ጋር በተያያዙ ተግባራት ውስጥ ተሳትፈዋል ብሎ መናገር በራሱ የቪየና ኮንቬንሽን ተጥሷል የሚለውን አምኖ መቀበል ነው” ሲሉ በሳምንታዊ መግለጫቸው ወቅት ተናግረዋል።

    ቴህራን ለረዥም ጊዜ የምዕራቡ ዓለም በውስጥ ጉዳዬ ጣልቃ እየገባ ነው በሚል በተደጋጋሚ ስታስጠነቅቅ ተደምጣለች።

    የፈረንሳዩ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዣን ኖኤል ባሮት ባለፈው ወር ከፍራንስ ኢንተር ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ የሁለቱ የኤምባሲ ሠራተኞች ተልዕኮ “የኢራን ሲቪል ማኅበረሰብን፣ ተማሪዎችን እና አርቲስቶችን የሚደግፉ ፕሮግራሞችን ማዘጋጀት ነው… ፈረንሳይ በዓለም ላይ ለኢራን ሲቪል ማኅበረሰብ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ካበረከቱ አገሮች አንዷ ናት፣ እናም ለዚህ ዋጋ ከፍለናል” ብለዋል።

  7. በፋርስ ባሕረ ሰላጤ የተሰማሩ የአሜሪካ ወታደሮች እና የአእምሮ ጤና ጉዳይ

    ዩኤስኤስ ሊንከን አውሮፕላን ተሸካሚ መርከብ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, ዩኤስኤስ ሊንከን አውሮፕላን ተሸካሚ መርከብ

    በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኘው የአሜሪካ ሠራዊት ከፍተኛ አዛዥ የሆኑት አድሚራል ብራድ ኩፐር በባሕረ ሰላጤው በተሰማራው የአሜሪካ ግዙፍ የጦር መርከብ ላይ ለሚገኙ ወታደሮች የአእምሮ ጤና “ቀዳሚ” ትኩረት እንደሚሰጥ ተናገሩ።

    ወታደራዊ መኮንኑ ይህንን ያሉት ከኢራን ጋር በሚደረገው ጦርነት ተሳታፊ በሆነው ዩኤስኤስ ሊንከን የጦር መርከብ ላይ ያሉ የአሜሪካ ወታደሮች በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ እንደሚገኙ እንዲሁም አንዳንዶችም ራስን የማጥፋት ሙከራ ማድረጋቸው ከተዘገበ በኋላ ነው።

    አውሮፕላን ተሸካሚው መርከብ ወደ ባሕረ ሰላጤው የደረሰው ባለፈው ጥር ሲሆን ከኢራን ጋር በሚደረገው ጦርነት ተሳታፊ ነው። ከዚህም ባሻገር አሜሪካ በኢራን ወደቦች ላይ የጣለችውን እገዳ በማስፈጸም ላይ ነው።

    በመርከቡ ላይ የሚገኙ የአሜሪካ የሠራዊት አባላት ከ240 ቀናት በላይ በባሕር ላይ መቆየታቸው የተነገረ ሲሆን ይህም የተለያዩ ችግሮችን እያስከተለባቸው መሆኑ ተዘግቧል።

    በዚህም ሳቢያ በመርከቧ ላይ የሚገኙ ባሕረተኞች ቤተሰቦችም የወታደሮቹ የአእምሮ ጤና ሁኔታ እያሽቆለቆለ በመሆኑ አንዳንዶች ከመርከቧ ላይ ለመዝለል ሙከራ ማድረጋቸውን ተናግረዋል።

    ይህንን ተከትሎ በመርከቧ ላይ ጉብኝት ያደረጉት አድሚራል ኩፐር እሁድ ዕለት እንዳሉት “ለአካላዊ ጤና የምናደርገውን ዓይነት ትኩረት ለአእምሮ ጤና ማድረግ እንዳለብን አምናለሁ” ሲሉ ለሁኔታው ትኩረት እንደሚሰጡ ተናግረዋል።

    ባለፈው ሳምንት የአሜሪካ ባሕር ኃይል አምስት ሺህ ሰዎችን በያዘው መርከብ ላይ የአቅርቦት ችግር እንዳለ ቢያምንም፣ የአእምሮ ጤና ችግርን በተመለከተ ግን ማስተባበያ ሰጥቷል።

    አውሮፕላን ተሸካሚው የሊንከን መርከብ ተልዕኮ ባለፈው ግንቦት ወር እንዲያበቃ እቅድ ተይዞ የነበረ ቢሆንም በተደጋጋሚ እንዲራዘም ተደርጓል።

    ወታደሮቹ በባሕር ላይ ለረጅም ጊዜ መቆየታቸውን በተመለከተ በአሜሪካ ምክር ቤት የጦር ኃይሎች አገልግሎት ጉዳዮች ኮሚቴ አባል የሆኑ 13 ዲሞክራቶች ለመከላከያ ሚኒስትሩ ፔት ሄግሴት የወቀሳ ደብዳቤ ጽፈዋል።

    ሚኒስትሩ ፔት ሄግዜትም ሆኑ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የቀረበውን ወቀሳ አጣጥለውታል። ነገር ግን፣ ዩኤስሰስ ጆርጅ ዋሺንተግን የተባለ ሌላ መርከብ የሊንከንን ቦታ እንዲተካ ወደ መካከለኛው ምሥራቅ እንደተላከ እና በአንድ ሳምንት ውስጥ ወደ አካባቢው እንደሚደርስ ተዘግቧል።

  8. የዴሞክራቲክ ኮንጎ ኢቦላ ወረርሽኝ እስካሁን በአገሪቱ ከተከሰቱት የከፋው ሆኖ ተመዘገበ

    የሕክምና ጭንብል ያደረገ ሰው

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    በዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ የተነሳው የኢቦላ ወረርሽኝ እስካሁን በአገሪቱ ታሪክ ከተከሰቱት እጅግ የከፋው ሆኖ መመዝገቡን የማኅበረሰብ ጤና ባለሥልጣናት ተናገሩ።

    ቫይረሱ መከሰቱ ግንቦት ላይ ከታወጀ ወዲህ በአጠቃላይ 2,325 ሰዎች ሕይወታቸው አልፏል። ይህ የሞት ቁጥር አገሪቱ ከአውሮፓውያኑ 2018 እስከ 2020 ድረስ ባለው ጊዜ ውስጥ ካጋጠማት የበለጠ ነው።

    የወረርሽኙ የስርጭት መጠን በታሪክ ከታዩት ፈጣኑ እንደሆነ የተባበሩት መንግሥታት የሰብዓዊ ጉዳዮች ኃላፊ ቶም ፍሌቸር ባለፈው ሳምንት ተናግረዋል። “ወረርሽኑ በየ30 ደቂቃው ሰው እየገደለ ነው” ሲሉም አስጠንቅቀው ነበር።

    የኮንጎ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት እሁድ ዕለት ባወጣው መረጃ 4,945 ሰዎች በቫይረሱ መያዛቸው እንደተረጋገጠ አስታውቋል። ከእነዚህ ውስጥ 101 ያህሉ የተመዘገቡት በ24 ሰዓታት ውስጥ ነው።

    ቫይረሱ ከዴሞክራቲክ ኮንጎ ውጪ ያለው ስርጭት በአንጻራዊነት አነስተኛ ነው። በአጎራባቿ ዩጋንዳ 20 ሰዎች መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን ጀርመን ውስጥ ሁለት ሰዎች ሕክምና እያገኙ ነው። ፈረንሳይ በቫይረሱ የተያዘ አንድ ሰው ማግኘቷን አስታውቃለች።

    ኢቦላ ኮንጎ ውስጥ ያለው የስርጭት ፍጥነት ግን ከዚህ ተቃራኒ ነው። የዓለም ጤና ድርጅት “ልዩ” ሲል የገለጸው ይህ ወረርሽኝ፣ በኮንጎ 26 ግዛቶች ውስጥ ተሰራጭቷል።

    በዓለም አቀፍ ደረጃ በርካታ ሰዎች የሞቱበት እና ከአውሮፓውያኑ 2014 እስከ 2016 በምዕራብ አፍሪካ የተከሰተው ወረርሽኝ 1,000 ሰዎችን ለመግደል አምስት ወራት እንደፈጀበት ሮይተርስ ዘግቧል። የአሁኑ ወረርሽን ግን ከሦስት ወር ባነሰ ጊዜ ውስጥ 2,000 ሞቶች ተመዝግበውበታል።

    ከ50 ዓመት በፊት ለመጀመሪያ ጊዜ የተገኘው ኢቦላ፣ ዴሞክራቲክ ኮንጎ ውስጥ ሲከሰት ይህ ለ17ተኛ ጊዜ ነው። በአገሪቱ ለዓመታት የዘለቀ ግጭት እና ከፍተኛ የሰዎች እንቅስቃሴ መኖሩ የበሽታውን ስርጭት ለመቆጣጠር የሚደረገውን ጥረት አስቸጋሪ አድርጎታል።

    የዓለም የጤና ድርጅት የበሽታው ስርጭት በሦስት ወር ውስጥ ይቀለበሳል የሚል ተስፋ ቢኖረውም፣ ስርጭቱ በቁጥጥር ስር ይውላል ወይም ወርሽኙ ሙሉ በሙሉ ያበቃል ማለት እንዳልሆነ ገልጿል።

    ኢቦላ ብዙም ያልተለመደ ነገር ግን ገዳይ በሽታ ነው። አሁን የተከሰተው የቡንዲቡግዮ የተባለው የኢቦላ ቫይረስ ዝርያ ደግሞ ከዚህ ቀደም ከሚታወቁት ሁለት ዝርያዎች አንጻር እጅግ ያልተለመደ ነው።

    እስካሁን ድረስ ለዚህ ዝርያ የሚሆን የተረጋገጠ ክትባት የለም። የተለያዩ ተቋማት ክትባት ለመስራት ሂደት ላይ ናቸው።

  9. ጥቃቶች ከተፈጸሙ በኋላ በሆርሙዝ በኩል የሚያልፉ መርከቦች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ ቀነሰ

    ሆርሙዝ ወሽመጥ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ባለፈው ሳምንት በነዳጅ ጫኝ መርከቦች ላይ ጥቃቶች ከተፈጸሙ በኋላ፣ ቅዳሜ እና እሁድ በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ያለፉ መርከቦች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ መቀነሱን መረጃዎች አመለከቱ።

    ይህ ዜና የተሰማው በኢራን እና በአሜሪካ መካከል እየተካሄደ ያለውን ግጭት ለማስቆም የሚደረገው ድርድር ተቋርጦ ባለበት ሁኔታ ነው።

    ኢራን ወሳኙ የባሕር መተላለፊያ መስመር፣ የሆርሙዝ ወሽመጥ የሉዓላዊ ግዛቷ አካል በመሆኑ በቁጥጥሯ ስር እንደሚሆን እየገለጸች ነው። አሜሪካ ደግሞ ስፍራው ነጻ ዓለም አቀፍ የባሕር አካል እንዲሆን እየጣረች ነው።

    በዚህም ሳቢያ ኢራን ሳያሳውቁ እና ከተፈቀደው መስመር ውጪ በሆርሙዝ በኩል ለማለፍ በሚሞክሩ መርከቦች ላይ ጥቃት እየፈጸመች ሲሆን፣ አሜሪካ በበኩሏ የኢራን መርከቦች በወሽመጡ እንዳይንቀሳቀሱ ዕገዳ ጥላለች።

    ባለፈው ሳምንት በተፈጸሙ ጥቃቶች ምክንያት በአካባቢው በሚደረገው እንቅስቃሴ ላይ ስጋት ተፈጥሯል። ኬፕለር የተባለው የባሕር ጉዞ እንቅስቃሴን የሚከታተል ተቋም ያወጣው መረጃ እንደሚያሳየው፣ ቅዳሜ ዕለት አምስት የጭነት መርከቦች ሲያልፉ፣ እሁድ ዕለት ግን አንድም መርከብ በሆርሙዝ አላለፈም።

    በወዲያኛው ሳምንት ቅዳሜ እና እሁድ 31 መርከቦች በወሳኙ የባሕር መተላለፊያ ወሽመጥ በኩል ማለፋቸው ተመዝግቦ ነበር። ይህም ካለፉት ቀናት ጋር ሲነጻጸር በከፍተኛ ሁኔታ የመርከቦች እንቅስቃሴ መገታቱን ያመለክታል።

  10. የትራምፕ ልዩ መልዕክተኛ የጋዛ የሰላም ዕቅድን ለማስፈጸም ከሐማስ መሪዎች ጋር ተገናኙ

    በጋዛ ፍርስራሾች መሃል ልጆች ይዛ የምትሄድ ሴት

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የመካከለኛው ምሥራቅ መልዕክተኛ የሆኑት ጃሬድ ኩሽነር፣ ባልተለመደ ሁኔታ በአሜሪካ ስለሚደገፈው የጋዛ የሰላም ዕቅድ አተገባበር ከሐማስ መሪዎች ጋር ተወያዩ።

    የትራምፕ አማች የሆኑት ኩሽነር በአዲሱ የሐማስ መሪ ኻሊል አል ሃያ የሚመራውን ልዑክ ያገኙት ትናንት እሁድ ግብፅ ውስጥ እንደሆነ አንድ የፍልስጤም ባለሥልጣን ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    የሰላም እቅዱን ትግበራ የሚቆጣጠረው የትራምፕ የሰላም ቦርድ ሐማስ እና በጋዛ የሚገኙ ሌሎች ታጣቂ ቡድኖች “ሙሉ በሙሉ ትጥቅ እንዲፈቱ” የሚያደርግ ስምምነት ላይ መድረሱን ሐምሌ ላይ አስታውቆ ነበር።

    ባለፈው ሳምንት ግን እስራኤል ወታደሮቿን እንድታስወጣ እንዲሁም ጋዛ ውስጥ አዲስ የፍልስጤም ሲቪል አስተዳደር እንዲመሠረት የሚያደርገውን ባለ 15 ነጥብ እቅድ እንደማትቀበለው ገልጻለች።

    ስምንት ሙስሊም አገራት ትናንት እሁድ ባወጡት መግለጫ እስራኤል እቅዱን ውድቅ ማድረጓን ኮንነዋል።

    መጀመሪያ ላይ ጋዛ ውስጥ ሰላም ለማምጣት ታስቦ የተቋቋመውን እና ኋላ ላይ በዓለም ዙሪያ የሚካሄዱ ግጭቶችም እንዲያካትት የተቋቋመውን የሰላም ቦርድ የሚመሩት ፕሬዝዳተት ትራምፕ ናቸው።

    የትራምፕ መልዕክኛ ኩሽነር ከሐማሱ መሪ አል ሃያ ጋር ያደረጉት ስብሰባ፣ የጋዛ ተኩስ ማቆም ስምምነት ከተፈረመ ወዲህ የተካሄደ የመጀመሪያው ንግግር እንደሆነ ተገልጿል።

    የሰላም ቦርድ መልዕክተኞች የሆኑት ኒኮላይ ምላደኖቭ እንዲሁም የቀድሞው የዩናይትድ ኪንግደም ጠቅላይ ሚኒስትር ቶኒ ብሌር ስብሰባው ላይ መገኘታቸውን ዘገባዎች አመልክተዋል። የሰላም ጥረቱን ሲያሸማግሉ የቆዩት የግብፅ፣ ኳታር እና ቱርክ ተወካዮችም መሳተፋቸው ተሰምቷል።

    የሐማስን ትጥቅ መፍታት በተመለከተ ስለሚወሰዱ ተግባራዊ እርምጃዎች እንዲሁም የእስራኤል ወታደሮችን መውጣት እና ሰብዓዊ ጥረቶችን በተመለከተ በውይይቱ ምን እንደተባለ እስካሁን ይፋ አልሆነም።

    የትራምፕ መልዕክተኛ ኩሽነር በግብፅ ቆይታቸው፣ ከአገሪቱ ፕሬዝዳንት አብደል ፋታህ አል ሲሲ ጋርም ተገናኝተዋል። ዛሬ ሰኞ ደግሞ ኩሽነር፣ ምላደኖቭ እና ብሌር የትራምፕን እቅድ ለማስፈጸም ከእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታንያሁ ጋር ይገናኛሉ።

    የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ስምምነቱ እንዲተገበር መጀመሪያ ሐማስ ሙሉ በሙሉ ትጥቅ መፍታት እንዳለበት ገልጸዋል።

    ኔታንያሁ ባለፈው ሳምንት ባደረጉት ንግግር፣ “እስራኤል የሰላም ቦርዱን ባለ 15 ነጥብ የጋዛ ሰነድ አትቀበልም። ሐማስ የእውነት ትጥቁን እስካልፈታ የእስራኤል መከላከያ ሠራዊት በምንም አይነት አይወጣም” ሲሉ የቅርብ አጋራቸው አሜሪካን ተቃውመዋል።

    ግብፅ፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች፣ ኳታር፣ ሳውዲ አረቢያ፣ ዮርዳኖስ፣ ቱርክ፣ ፓኪስታን እና ኢንዶኔዥያ እሁድ ዕለት ባወጡት የጋራ መግለጫ፣ እስራኤል የአሜሪካን ዕቅድ ውድቅ ማድረጓ የትራምፕን የሰላም ጥረት አደጋ ላይ ይጥለዋል የሚል ስጋታቸውን አንጸባርቀዋል።

    ከጥቅምት አንስቶ ወደ ሥራ የገባው የተኩስ አቁም ስምምነት አሁንም ተግባራዊ መሆን አላቆመም።

    ነገር ግን እስራኤል ስምምነቱ ከተፈረመ ጊዜ ጀምሮ በጋዛ ውስጥ በርካታ ጥቃቶችን ፈጽማለች። ሐማስ ተኩስ አቁሙን ጥሷል በሚል የመጨረሻውን ጥቃት ያደረሰችው ኻን ዩኒስ እና ኑሴራት በተባሉት የጋዛ አካባቢዎች ነው።