የፊፋን ፕሬዚዳንት ዕቅድ የተቹት ግለሰብ ኃላፊነታቸውን እንዲለቅቁ ተደረገ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የፊፋ ዋና ኦፕሬሽን ኃላፊ ኬቨን ላሙር ፕሬዚዳንት ጂያኒ ኢንፋንቲኖ የግል ባለሃብቶችን ለማሳተፍ ያቀረቡትን ሃሳብ አጥብቀው ከተቹ ከሦስት ሳምንት በኋላ ከሥልጣናቸው መባረራቸው ተሰማ።
የፊፋ ቃል አባይ በጽሑፍ ለቢቢሲ ስፖርት በሰጠው ምላሽ "በፊፋ እና በኬቨን ላሞር መካከል ያለው የሥራ ግንኙነት ከነሐሴ 11፣ 2018 ዓ.ም. ጀምሮ ተቋርጧል" ብሏል።
አክለውም "ፊፋ ኬቨን በሁለት ዓመት ውስጥ ለሰጡት አገልግሎት እያመሰገነ ወደ ፊት መልካሙ ሁሉ እንዲገጥማቸው ይመኛል" ብለዋል።
የፊፋ ባልደረቦች ሰኞ ምሽት የኦፕሬሽን ኃላፊው መባረርን በዋና ጸሃፊው ማቲያስ ግራፍስቶም በተጻፈ ኢሜል እንዲያውቁት ተደርጓል።
በኢሜሉ ላይ ላሞር እና ፊፋ "ለመለያየት ተስማምተዋል" ሲሉ ጠቅሰዋል።
ባለፈው ወር ላሞር፣ ፊፋ የዓለም ዋንጫን ጨምሮ በተለያዩ ውድድሮች ላይ ድርሻዎችን ለግል ባለሀብቶች ለመሸጥ ኢንፋንቲኖ ያቀረቡትን ሀሳብ በግልጽ ከተቃወሙ ከፍተኛ የፊፋ ባለሥልጣናት መካከል አንዱ ነበሩ።
በወቅቱ ዕቅዱን "የአንድ ሰው ፕሮጀክት" ሲሉ የተቹት ላሞር "የእግር ኳስ ፖለቲካ መሪዎች ትክክለኛዎቹን ጥያቄዎች ለራሳቸው የሚያቀርቡበትና ትክክለኛ ውሳኔዎችን የሚያሳልፉበት ጊዜ አሁን ደርሷል" ብለው ነበር።
አክለውም የፊፋ አስተዳደር ፕሮጀክቱ "ተጭበርብሯል" ሲሉ የመረረ ትችት ሰንዝረው ነበር።
"ተልዕኳችን፤ በመቶዎች የሚቆጠሩ ታታሪ፣ ቁርጠኛ እና አርአያ የሆኑ የፊፋ ሠራተኞች ተልዕኮ፣ እግር ኳስን ማገልገል ነው" ብለዋል።
"አንድ ፕሬዝዳንት ሰዎችን አንድ ላይ ማምጣት፣ አንድ ማድረግ እና ማነሳሳት አለበት። ዛሬ ግን በተቃራኒው እየተመለከትን ነው።"
ላሞር ለቀጣሪያቸው ታማኝ የመሆን ግዴታ እንዳለባቸው ገልጸው፤ ነገር ግን ለ"ተወሰኑ እሴቶች" እና ለባልደረቦቼ ድጋፍ የማድረግ ግዴታም አለብኝ ብለው እንደሚያምኑ ገልጸዋል።
"ይህ ማለት ሥራዬን ማጣት ከሆነም፣ ይሁን" ሲሉም አክለዋል። "ውሳኔውን እረዳለሁ፤ እንዲሁም አከብራለሁ። ቢያንስ ዛሬ ማታ በሰላም እተኛለሁ" ብለዋል።
ላሞር ፊፋን የተቀላቀሉት በኅዳር ወር 2024 ሲሆን ቀደም ሲል በአውሮፓ እግር ኳስ ማኅበር ውስጥ ምክትል ዋና ጸሐፊ ሆነው አገልግለዋል። በፊፋ ውስጥ ከኢንፋንቲኖ ሥር በመሆን ሲሰሩ ቆይተዋል።
በዚህ ወር መጀመሪያ ላይ ኢንፋንቲኖ በሞሮኮ በተካሄደ ስብሰባ ላይ የከፍተኛ ሥራ ኃላፊዎችን ድጋፍ ያገኙ ሲሆን ቢቢሲ ስፖርት ላሞር እንዳልተጋበዙ መረዳት ችሏል።
ላሞር በጉዳዮ ላይ አስተያየት እንዲሰጡ ጥያቄ ቢቀርብላቸውም ከመመለስ ተቆጥበዋል።
የፊፋ ዋና ጸሐፊ ግራፍስትሮም ለፊፋ ምክር ቤት አባላት በላኩት እና በቢቢሲ ስፖርት ባየው ደብዳቤ ላይ "በፊፋ አስተዳደር ውስጥ ስላለው ለውጥ አስፈላጊ መረጃ ልሰጣችሁ እፈልጋለሁ" ሲሉ ጽፈዋል።
"በቅርብ ጊዜ ከተደረጉ ውይይቶች በኋላ፣ ፊፋ እና ዋና የኦፕሬቲንግ ኦፊሰራችን ኬቨን ላሞር ለመለያየት ተስማምተዋል። እዚህ ውሳኔ ላይ የተደረሰው በጥንቃቄ ከታሰበበት እና ለኬቨን ሆነ ለሙያቸው አክብሮት ከተሰጠ በኋላ ነው… ይህንን መረጃ ራሴ ባካፍላችሁ መልካም እንደሆነ ተሰምቶኛል። እናም ኬቨን ላበረከቷቸው አስተዋፅዖዎች እና በየቀኑ በፊፋ ስም ላከናወኗቸው ሥራዎች እና ለነበራቸው ቁርጠኝነት ምስጋናዬን መግለጽ እፈልጋለሁ። ኬቨን ለወደፊቱ መልካሙን ሁሉ እመኝልዎታለሁ" ይላል።















