የቀድሞ የኢኳዶር ፕሬዝዳንት በሙስና ወንጀል እስር ተፈረደባቸው

ታትሟል
የንባብ ጊዜ: 2 ደቂቃ

ጉቦ በመቀበለ ወንጀል ጥፋተኛ ሆነው የተገኙት የቀድሞው የኢኳዶር ፕሬዝዳንት ሌኒን ሞሬኖ የአምስት ዓመት እስራት ተፈረደባቸው።

የቀድሞው ፕሬዝዳንት፣ በላቲን አሜሪካዊቷ አገር ውስጥ የሃይድሮ ኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ለመገንባት ኮንትራት ካገኘው የቻይና ኩባንያ ገንዘብ አልተቀበልኩም በማለት ተከራክረዋል።

የ73 ዓመቱ ሞሬኖ ዕድሜያቸው በመግፋቱ እና የአካል ጉዳት ስላለባቸው፣ ቅጣቱን የሚፈጽሙት ቤታቸው ውስጥ በቁም እስር እንደሆነ ተገልጿል።

የቀድሞውን ፕሬዝዳንት እና ሌሎች 19 ሰዎችን በሙስና ወንጀል ጥፋተኛ ያለውን በዋና ከተማዋ ኪቶ የሚገኝ ፍርድ ቤት ውሳኔ ላይ ይግባኝ ለማለት ማቀዳቸውን ተናግረዋል።

ከአውሮፓውያኑ 2017 እስከ 2021 ኢኳዶርን በፕሬዝዳንትነት የመሩት ሞሬኖ፣ በሙስና ወንጀል የተፈረደባቸው ሦስተኛው የቀድሞ የአገሪቱ መሪ ናቸው።

ክሱ የተመሠረተው፣ ንብረትነቱ የቻይና መንግሥት የሆነው 'ሲኖሃይድሮ' የተባለ ኩባንያ 'ኮካ ኮዶ ሲንክሌር' የተባለው የሃይድሮ ኤሌክትሪክ ግድብ ግንባታን ውልን ካገኘበት መንገድ ጋር በተያያዘ ነው።

ዐቃብያነ ሕግ፣ ኩባንያው ኮንትራቱን ለማግኘት መዝገብ ላይ ብቻ በሚገኙ ኩባንያዎች በኩል ውሉ ውስጥ ለተሳተፉ ሰዎች በድምሩ 76.1 ሚሊዮን ዶላር ጉቦ ከፍሏል የሚል ክስ አቅርበዋል።

ከቀድሞው ፕሬዝዳንት በተጨማሪ የፍርድ ውሳኔ ከተላለፈባቸው ተከሳሾች መካከል የሞሬኖ ባለቤት፣ ሴት ልጅ እና ወንድማቸው ይገኙበታል። የቀድሞ የኃይል ማመንጫው ሥራ አስኪያጆች፣ የሲኖሃይድሮ ተወካዮች እና በኢኳዶር የቻይና አምባሳደርም ይገኙባቸዋል።

ሞሬኖ በዚህ የሙስና ወንጀል የተቀበሉት ገንዘብ እጅግ ትንሽ ቢሆንም፣ የቤተሰባቸው አባላት ግን በአስር ሺዎች የሚቆጠር ዶላር እንዳገኙ ዐቃብያነ ሕግ ገልጸዋል።

በዚህ ወንጀል ጥፋተኛ የተባሉት ተከሳሾች ከተቀበሉት ጉቦ ሦስት እጥፍ የሚበልጥ ገንዘብ እንዲከፍሉ ተወስኖባቸዋል። ሞሬኖ ደግሞ በመንግሥት የሥራ ኃላፊነት እንዳይሰሩ ሙሉ በሙሉ ታግደዋል።

የቀድሞው ፕሬዝዳንት በዚህ ወንጀል ውስጥ እጃቸው እንደሌለበት በመግለጽ በተደጋጋሚ አስተባብለዋል። በምትኩም ምክትል ፕሬዝዳንት በነበሩበት ወቅት የአገሪቱ መሪ የነበሩትን እና 2020 ላይ በሌላ የሙስና ክስ የስምንት ዓመት እስራት የተፈረደባቸውን የቀድሞ ፕሬዝዳንት ራፋኤል ኮሪያን ተጠያቂ አድርገዋል።

ሞሬኖ እንደሚናገሩት፣ 'ኮካ ኮዶ ሲንክሌር ፕሮጀክት'ን በተመለከተ ፈቃድ የሰጡት የቀድሞው ፕሬዝዳንት ኮሪያ ናቸው። እርሳቸው ኮሪያን ተክተው ፕሬዝዳንት ከሆኑ በኋላ በግንባታው ላይ በታዩት ችግሮች ዙሪያ ምርመራ አስጀምረው እንደነበር ገልጸዋል።

የኢኳዶር መንግሥት ግድቡ ላይ ስንጥቆች መታየታቸውን እና ሌሎች ቴክኒካዊ ጉድለቶች መከሰታቸውን ተከትሎ፣ በ2021 ሲኖሃይድሮ ላይ ክስ ከፍቶ ነበር። በዚህ ዓመት መጀመሪም ክሱን ለመፍታት ከኩባንያው ባለቤት ጋር የ400 ሚሊዮን ዶላር ስምምነት ተደርሷል።

ቢቢሲ ስለ ውንጀላዎቹ አስተያየት ለማግኘት ለሲኖሃይድሮን እና በኢኳዶር ለሚገኘው የቻይና ኤምባሲ ጥያቄ አቅርቧል።