በቀይ ባሕር እንቅስቃሴ ላይ ስጋት የፈጠረው እና ሚሊዮኖች የሚጠየቅበት የሶማሊያ ባሕር ላይ ውንብድና

ታትሟል
የንባብ ጊዜ: 6 ደቂቃ

በሶማሊያ የባሕር ዳርቻ ላይ እየጨመረ የመጣው ውንብድና በኢራን እና በአሜሪካ መካከል እየተካሄደ ባለው ጦርነት እንዲሁም ዕገዳ ምክንያት ጫና ውስጥ ላለው የመርከቦች እንቅስቃሴ ከባድ አደጋ ሆኗል።

ባለፈው ሳምንት በአራት ቀናት ውስጥ ሁለት የንግድ ጭነት መርከቦች በኤደን ባሕረ ሰላጤ በባሕር ላይ ዘራፊዎች ተይዘዋል። ይህም ከዓመቱ መጀመሪያ አንስቶ የተጠለፉ መርከቦች ቁጥርን ቢያንስ 13 እንዲደርስ አድርጓል። በዚህ ምክንያትም የባሕር ላይ ወንበዴዎችን ለመከላከል እስካሁን ታይቶ የማያውቅ የድሮን ጥቃት እንዲካሄድ ምክንያት ሆኗል።

ይህ ክስተት ከ10 ዓመታት በላይ በሆነ ጊዜ ውስጥ በመርከቦች ላይ የተፈጸመ ከፍተኛው ጠለፋ ነው። ለዓለም አቀፍ ንግድ እጅግ ወሳኝ የሆነው ቀጣና ምን ያህል ደኅንነቱ አደጋ ላይ ወድቋል? የሚል ስጋትን ፈጥሯል።

"የባሕር ላይ ውንብድና አጋጣሚዎችን የሚጠብቅ ወንጀል ነው" የሚለው የደኅነንት ቀውስ ጉዳዮችን የሚከታተለው ኢንተርናሽናል ክራይሲስ ግሩፕ የሶማሊያ ጉዳይ ከፍተኛ ተንታኝ ኦማር ማህሙድ "አሁን ደግሞ የባሕር ላይ ዘራፊዎቹ መልካም አጋጣሚ እንዳገኙ ያምናሉ" በማለት ያብራራል።

አጋጣሚው የተፈጠረው ደግሞ አሜሪካ እና ኢራን በፋርስ ባሕረ ሰላጤው ላይ በሚገኘው የሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ በሚያደርጉት ፍልሚያ ምክንያት ነው።

ኢራን እና አሜሪካ ወሳኙን የሆርሙዝ ወሽመጥ ለመቆጣጠር የሚያደርጉት ፍልሚያ እንደቀጠለ ነው።

የኢራን አጋር የሆኑት ሁቲዎችም የየመን አዋሳኝ በሆነው የባብ አል-መንዳብ ወሽመጥ ላይ በተመረጡ መርከቦች ላይ የሚያነጣጥር እገዳ ጥለዋል። እገዳው በዋናነት ዒላማ ያደረገው ጠላት በሚሏት የሳዑዲ አረቢያ መርከቦች ላይ ቢሆንም፣ ለዓለም አቀፍ የባሕር መጓጓዣ ደኅንነት ከፍተኛ ስጋትን ፈጥሯል።

"እንደማስበው የባሕር ላይ ዘራፊዎቹ በሆርሙዝና በባብ አል-መንደብ ያሉትን ሁለት ትልልቅ ቀውሶች በማየት፣ ዓለም አቀፍ ኃይሎች ትኩረታቸውን በእነዚህ ቀውሶች ላይ እንደሚያደርጉ እና የባሕር ላይ ውንብድናን ለመከታተል ብዙ ጊዜ እንደማያገኙ ያምናሉ" ሲሉ የሶማሊያ የባሕር ዳርቻን የሚጠብቀው የአውሮፓ ኅብረትን የባሕር ኃይል አዛዥ ምክትል አድሚራል ኢግናሲዮ ቪላኑዔቫ ሴራኖ ይናገራሉ።

በሌላ አነጋገር በሆርሙዝ እና በባብ ኤአል-መንደብ ያሉ የፀጥታ ቀውሶች የዓለም አቀፍ የባሕር ኃይሎችን ትኩረት ስለሚስቡ፣ የሶማሊያ የባሕር ላይ ዘራፊዎች ይህን ሁኔታ እንደ አመቺ አጋጣሚ ተጠቅመው ጥቃታቸውን እያሳደጉ ነው።

በቅርቡ በባሕር ላይ ወንበዴዎች ከተጠለፉት መርከቦች መካከል አንዱ የካሜሩን ሰንደቅ ዓላማን የሚያውለበልብ ነው። ይህ መርከብ በዘራፊዎች የተያዘው ነሐሴ አጋማሽ ላይ ከፊል ራስ ገዝ ከሆነችው የሶማሊያ ግዛት ፑንትላንድ የባሕር ዳርቻ አቅራቢያ ጥቃት ተፈጽሞበት ነው።

ከጥቂት ቀናት በኋላ ደግሞ፣ የኤርትራን ሰንደቅ ዓላማ የያዘ የነዳጅ ምርቶች ጫኝ መርከብ በየመን የባሕር ዳርቻ አቅራቢያ በባሕር ላይ ወንበዴዎች ቁጥጥር ስር ውሏል።

በካሜሩን ሰንደቅ ዓላማ ሲንቀሰቀስ የነበረው መርከብ ጠለፋ ግን ያልተጠበቀ ውጤት አስከትሏል።

በዚህም መርከቡን ከጠለፉት ወንበዴዎች ጋር ግንኙነት አላቸው የተባሉ እና ለጠላፊዎቹ የሚያስፈልጋቸውን ያቀርባሉ በተባሉ ጀልባዎች ላይ በተፈጸሙ ጥቃቶች 13 ሰዎች ተገድለዋል።

ነገር ግን ለድሮን ጥቃቶቹ አስካሁን ኃላፊነቱን ባይወስድም፤ የአካባቢው ባለሥልጣናት ግን የተጠለፈችው መርከብ የቱርክ ጦር መሳሪያዎችን የጫነች በመሆኗ ጥቃቱን የፈጸመችው ቱርክ ናት ይላሉ።

ቢቢሲ እንደተረዳው መርከቡ በአሁኑ ጊዜ በሚሊዮኖች ዶላር የሚቆጠር ማስለቀቂያ ገንዘብ ተጠይቆባቸው ተይዘው ከሚገኙ ስድስት መርከቦች አንዱ ነው።

ከእነዚህ ስድስት መርከቦች ውስጥ አራቱ በባሕር ላይ ዘረፋ በስፋት የምትታወቀው የሶማሊያ የዓሣ አጥማጆች ከተማ በሆነችው ባንደር ቤይላ አቅራቢያ ቆመው ይገኛሉ።

በአጭሩ፣ የሶማሊያ ባሕር ዘራፊዎች የያዟቸው መርከቦች ቁጥር እየጨመረ ሲሆን፣ ይህ ሁኔታም የድሮን ጥቃቶችን፣ ዓለም አቀፍ የደኅንነት ስጋቶችን እና ከፍተኛ የማስለቀቂያ ገንዘብ ጥያቄዎችን አስከትሏል።

አሁን በባሕር ላይ ወንበዴዎች የተያዙት መርከቦች ቁጥር ከ15 ዓመታት በፊት እንደነበረው ከፍተኛ ደረጃ ላይ ገና አልደረሰም፤ በዚያ ወቅት የባሕር ላይ ዘረፋው በዓለም ኢኮኖሚ ላይ በቢሊዮኖች ዶላር የሚቆጠር ኪሳራ አድርሶ ነበር።

በአውሮፓውያኑ 2011 የሶማሊያ የባሕር ላይ ዘራፊዎች በመርከቦች ላይ ከ200 በላይ ጥቃቶችን ፈጽመው በመቶዎች የሚቆጠሩ የመርከብ ሠራተኞችን በእገታ ይዘው ነበር።

ዓለም አቀፍ የባሕር ኃይሎች እና በንግድ መርከቦች ላይ የተቀጠሩ የግል የደኅንነት ጠባቂዎች ተቀናጅተው በወሰዱት እርምጃ ችግሩን በእጅጉ ለመቀነስ ችለው ነበር። እንዲሁም በ2023 እና 2024 የተፈጠረውን አዲስ የባሕር ላይ ዘረፋ እንቅስቃሴን በመቆጣጠር መግታት ችለዋል።

ሆኖም ባለሙያዎች እንደሚሉት የባሕር ላይ ዘራፊዎች መረቦች ተዳክመው ጥቃቱን መቆጣጠር ቢቻልም፣ ሙሉ በሙሉ አልጠፉም።

ምክንያቱም ለባሕር ላይ ውንብድናው መነሻ የሆነውን እና በሶማሊያ የሚገኘውን ድህነት፣ ሥራ አጥነት፣ የደኅንነት እጦት እና ደካማ አስተዳደርን የመሳሰሉ መሠረታዊ ችግሮች ለመፍታት ውጤታማ እርምጃ አልተወሰደም።

በአሁኑ ጊዜ የባሕር ላይ ዘረፋው እንደገና ያገረሸው በአካባቢው በተፈጠረ ቁጣ ነው። ምክንያቱም የሌሎች አገራት ዓሣ ማጥመጃ መርከቦች በሶማሊያ የባሕር ክልል ውስጥ ከልክ በላይ ዓሣ እያጠመዱ በመሆኑ በፑንትላንድ ያሉ ኑሯቸውን በዓሣ ማስገር ላይ ያደረጉ ማኅበረሰቦችን እየጎዱት ነው።

በተጨማሪም፣ አሁን ለባሕር ላይ ወንበዴዎች የሚጠለፉ መርከቦች ቁጥር ጨምሯል፤ እነዚህ መርከቦች ደግሞ ከዚህ በፊት ከነበሩት የበለጠ ትልቅ የማስለቀቂያ ገንዘብ ሊያስገኙ የሚችሉ ናቸው።

በአካበቢው ያለው የባሕር ላይ ደኅንነት ችግር አንዳንድ መርከቦች በሰሜን ከየመን በኩል ያለውን ግጭት ለመራቅ ሲሉ ወደ ደቡብ ፊታቸውን ወደ ሶማሊያ የባሕር ዳርቻ ይበልጥ አዙረዋል። የነዳጅ ዋጋ ከፍ ያለ በመሆኑም፣ የባሕር ላይ ወንበዴዎቹ ነዳጅ ጫኝ መርከብ መጥለፍ የበለጠ ትርፋማ ሆኖላቸዋል።

"ባሕር ኃይሎች የሚያደርጉት ጥበቃ ቀንሷል፤ በተመሳሳይ ጊዜ ደግሞ በመስመሩ ላይ የሚጓዙ የንግድ መርከቦች ቁጥር ጨምሯል። ይህም ለባሕር ላይ ዘራፊዎች አመቺ ሁኔታ መኖሩን ያሳያል" ይላሉ ተንታኙ ኦማር ማህሙድ።

ይህም "አንድ የተሳካ ጥቃት ከተፈጸመ በኋላ፣ ሌሎች ቡድኖችም ያንን በመኮረጅ ተመሳሳይ ጥቃቶችን እንዲፈጽሙ ያበረታታቸዋል ብዬ አስባለሁ።"

ኦማር እና ሌሎች ተመራማሪዎች የሚጠረጥሩት ሌላኛው ጉዳይ፣ በሶማሊያ የባሕር ላይ በወንበዴዎች እና በየመን ያሉ ቡድኖች መካከል ትብብር ሊኖር ይችላል የሚል ነው። ምክንያቱም በርካታ መርከቦች በየመን የባሕር ዳርቻ አካባቢ ተጠልፈዋል።

ነገር ግን ኦማር እንደሚለው፣ እነዚህ በየመን እና በሶማሊያ ቡድኖች መካከል ትብብሮች ካሉ ምናልባት ከወንጀለኛ ቡድኖች ጋር የተያያዙ ሊሆኑ እንጂ፣ የኢራን ደጋፊ ከሆኑት የሁቲ ኃይሎች ጋር በቀጥታ የተገናኙ የመሆናቸው ዕድል ያነሰ ነው።

ለዚህም አንዱ ምክንያት፣ ባለፈው ሳምንት ከተጠለፉት መርከቦች አንዱ የሆነው ነዳጅ ጫኝ መርከብ የኢራን "ስውር መርከቦች" አካል ነው ተብሎ ስለሚጠረጠር ነው።እነዚህ መርከቦች ኢራን በአሜሪካ የተጣሉባትን ማዕቀቦች ለማለፍ በምሥጢር ወይም በተለያዩ መንገዶች ነዳጅ የምታጓጉዝባቸው ናቸው።

"ይህ በቀጥታ በኢራን የሚመራ ነገር ነው ብዬ አላስብም" ይላል ኦማር።

በቅርብ ጊዜ ከተፈጠሩት የመርከቦች ጠለፋ ክስተቶች ጋር በተያያዘ የቱርክ ስምም እየተነሳ ነው።

የፑንትላንድ የደኅንነት ምንጮች እና አንድ የሶማሊያ መንግሥት ባለሥልጣን ለቢቢሲ እንደተናገሩት፣ በካሜሩን ሰንደቅ ዓላማ ሲንቀሳቀስ የተጠለፈው መርከብ በሶማሊያ ዋና ከተማ ሞቃዲሾ ውስጥ ለሚገኘው የቱርክ ወታደራዊ ማሠልጠኛ ተቋም የሚውሉ የጦር መሣሪያዎችን ጭኖ ነበር።

ቱርክ የሶማሊያን የባሕር ደኅንነት ለማጠናከር ስምምነት ያላት ሲሆን፣ ይህም በሁለቱ አገራት መካከል የተደረሰው ሰፊ የመከላከያ እና የኢኮኖሚ ትብብር አካል ነው።

የደኅንነት ምንጮቹ እንደሚሉት፣ በአሁኑ ጊዜ መርከቡ በጠላፊዎቹ ተይዞ በሚገኝበት አካባቢ አቅራቢያ ስድስት ዓለም አቀፍ የጦር መርከቦች ይገኛሉ። ከእነዚህም ሁለቱ የቱርክ፣ ቀሪዎቹ የስፔን፣ የዴንማርክ፣ የአሜሪካ እና የሕንድ ናቸው ተብሏል። ሆኖም ቢቢሲ ይህንን መረጃ ከገለልተኛ ወገን ማረጋገጥ አልቻለም።

ስማቸው እንዳይገለጽ የጠየቁ አንድ የሶማሊያ መንግሥት ባለሥልጣን በተጠለፈው መርከብ ላይ ቱርክ ከሞቃዲሾ በስተሰሜን እየገነባችው ላለው የጠፈር ጣቢያ ምርምር የሚያገለግሉ የሳተላይት መሣሪያዎችን ጨምሮ "በሶማሊያ ውስጥ ለምታከናውናቸው ተግባራት የሚውሉ ወታደራዊ መሣሪያዎች አሉ" ብለዋል።

ባለሥልጣኑ በተጨማሪ እሑድ ዕለት ዘጠኝ ታጣቂዎችን የገደለውን ሁለተኛ የድሮን ጥቃት ቱርክ ፈጽማዋለች በማለት ወንጅለዋል።

"የተገደሉት ሰዎች ወንጀለኞች ነበሩ፤ ለእነርሱ ርኅራኄ የለኝም። ግን ነገሩን ወደዚህ ደረጃ ማድረስ ሁኔታውን የበለጠ ያባብሰዋል።"

የቱርክ መከላከያ ሚኒስቴር፣ በሶማሊያ የባሕር ግዛት ውስጥ ከተጠለፈው መርከብ ጋር በተያያዘ ኃይሎቹ ለሶማሊያ ባለሥልጣናት "አስፈላጊውን ድጋፍ" እየሰጡ መሆኑን ገልጿል። ይህም በሁለቱ አገራት መካከል ባለው የደኅንነት ስምምነት ማዕቀፍ ውስጥ መሆኑን አስታውቋል። ሆኖም ቱርክ የድሮን ጥቃቶችን ፈጽማለች በሚለው ክስ ላይ በቀጥታ ምላሽ አልሰጠም።

የሶማሊያ መንግሥት ጉዳዩን በተመለከተ በይፋ በሰጠው መግለጫ በባሕር ላይ ዘራፊ ቡድኖችን ላይ የሚካሄዱትን ዘመቻዎች እንደሚያውቅ እና የባሕር ላይ ወንበዴዎችን ለመቋቋም እርምጃዎችን እንደሚወስድ ብቻ ገልጿል።

የፑንትላንድ ግዛት ባለሥልጣናት ግን ይበልጥ ግልጽ አቋም ወስደዋል።

የፑንትላንድ ምክትል የደኅንነት ሚኒስትር አብዲራህማን ዩሱፍ፣ ለቢቢሲ ሶማሊኛ አገልግሎት ሲናገሩ፣ ቱርክ ለጥቃቶቹ ተጠያቂ መሆኗን የሚያሳይ ማስረጃ እንዳላቸው ገልጸዋል።

እሳቸው ይህን የተናገሩት በተጠለፈው መርከብ አካባቢ እና በፑንትላንድ የባሕር ዳርቻ ላይ የታየውን የቱርክ እንቅስቃሴ መሠረት በማድረግ ነው።

ሆኖም ቢቢሲ እነዚህን ክሶች ከገለልተኛ ወገን ማረጋገጥ አልቻለም።

የፑንትላንድ የደኅንነት ሚኒስቴርም ባወጣው መግለጫ "በሲቪል ሰዎች ላይ ያነጣጠሩ በዓለም አቀፍ የጦር መርከቦች የተፈጸሙ የቦምብ ጥቃቶችን" እንደሚቃወም እና ጥቃቶቹ "የባሕር ላይ ዘረፋን ለመዋጋት የሚደረገውን ትብብር ያዳክማል" ሲል ገልጾ፣ ለምን እንደተፈጸሙ በአስቸኳይ ማብራሪያ እንዲሰጥ ጠይቋል።

ተንታኞች እንደሚሉት፣ ፑንትላንድ ቱርክ ከሶማሊያ ፌዴራል መንግሥት ጋር ያላትን ጥብቅ ወታደራዊ ግንኙነት በጥርጣሬ ትመለከታለች። ክስተቶቹም በከፊል ራስ ገዟ ፑንትላንድ እና በሶማሊያ መንግሥት መካከል ለረጅም ጊዜ የቆየውን የፖለቲካ ውዝግብ የበለጠ ሊያወሳስቡት ይችላሉ። ይህ ውዝግብ ደግሞ የባሕር ላይ ዘረፋን በተቀናጀ ሁኔታ ለመዋጋት ለሚደረገው ጥረት እንቅፋት እየሆነ ነው።

በአሁኑ ጊዜ ያለው የባሕር ላይ ውንብድና ገና ወደ ግዙፍ የባሕር ላይ ዘረፋ አልደረሰም፤ ነገር ግን በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ያለው ጦርነት ካልቆመ ወይም ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ የባሕር ላይ ወንበዴዎችን ለመከላከል የበለጠ እርምጃ ካልወሰደ፣ የሶማሊያ የባሕር ላይ ዘረፋ ለዓለም ንግድ ለእጅግ ወሳኝ በሆነው ይህ የባሕር መስመር ላይ የሚደቅነውን የአደጋ ደረጃ ማሳደጉን ይቀጥላል።