አሜሪካ በኩባ ባለሥልጣናት እና ኩባንያዎች ላይ አዲስ ማዕቀቦችን ጣለች

ዶናልድ ትራምፕ እና ማርኮ ሩቢዮ

የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

ታትሟል
የንባብ ጊዜ: 2 ደቂቃ

አሜሪካ በኩባ ባለሥልጣናት እና ኩባንያዎች ላይ አዲስ ዙር ማዕቀቦችን መጣሏን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ ተናገሩ።

አዲስ በተጣለው ማዕቀብ ውስጥ ባለቤትነታቸው የመንግሥት የሆኑ ዘጠኝ የማዕድን ድርጅቶች፣ የብረት እና ሕንፃ ተቋማት፣ የኮንስትራክሽን ሚኒስቴር እና ተቀማጭነታቸውን በኩባ ካደረጉ ዓለም አቀፍ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት ያላቸው ባለሥልጣናት ተካትተዋል።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ማርኮ ሩቢዮ በመግለጫቸው ላይ ከቀድሞው የኩባ መሪ ፊደል ካስትሮ 100ኛ ዓመት የልደት በዓል ጋር በተያያዘ "አዲስ ዓለም አቀፍ የደጋፊዎች ቡድንን ከአገዛዙ ባለሥልጣናት ጋር ለማገኛኘት ወደ ሃቫና አጓጉዘዋል" ያሏቸውን ባለሥልጣናት ከስሰዋል።

ሩቢዮ እንዳሉት የማዕቀቡ ዒላማ የሆኑት ባለሥልጣናት፣ "ገዥው መንግሥት የማርክሲዝም፣ የዘር ጥላቻን እና የኮሚዩኒስት አመፅን በዓለም የማስፋፋት ድርጊት አካል" ናቸው።

ሚኒስትሩ ጨምረውም " የተጣለው ማዕቀብ የትራምፕ አስተደዳር የኩባ መንግሥትን የጭቆና ድጋፍ ወይም ለአስርተ ዓመታት የቀጠለውን የፀረ - አሜሪካዊያን እንቅስቃሴ ጥረት እንደማይታገስ ያሳየ ነው" ብለዋል።

ኩባ በበኩሏ በትራምፕ አስተዳደር የተጣለባትን ሁሉንም ማዕቀቦች አውግዛለች።

አሜሪካ በጣለችው አዲስ ዙር ማዕቀብ የኩባ የሕዝብ ለሕዝብ ወዳጅነትተቋም ወይም 'ኢንስቲቲዩት ኦፍ ፍሬንድሽፕ ዊዝ ፒፕልስ' ( አይሲኤፒ) ኢላማ ሆኗል።

የአገሪቱ መንግሥት እንደ አውሮፓውያኑ በ1960 በፊደል ካስትሮ የተመሰረተውን ተቋም፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተመሳሳይ ሃሳብ ካላቸው ድርጅቶች ጋር ግንኙነት ለመፍጠር በራሳቸው አገር ሆነው የኩባን መንግሥት የሚደግፉ ጎብኝዎችን ለማስተናገድ ይገለገልበታል።

ሆኖም ሩቢዮ ቡድኑን " በሐሰት፣በስለላ እና የአሜሪካ ዜጎችን በማታለል እና በመበረዝ" ከስሰዋል።

በመሆኑም ኩባ 5 የተባለው የስለላ ቡድን አባል የሆኑት እና የቡድኑ ፕሬዚደንት ፈርናንዶ ጎንዛሌዝ ሊሎርት ማዕቀብ ከተጣለባቸው ባለሥልጣናት ዝርዝር ውስጥ እንደተካተቱ ተገልጿል።

ከእርሳቸው በተጨማሪም የሃቫና የኤነርጂ፣ የገንዘብ እና የመከላከያ መሥሪያ ቤት ከፍተኛ ባለሥልጣናት የአሜሪካ ማዕቀብ ተጥሎባቸዋል። ቀውስ ውስጥ የሚገኘው መንግሥት ከፍተኛ ገቢ የሚያገኝበት የቱሪዝም ኢንደስትሪም ወድቋል።

የኩባ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ብሩኖ ሮድሪጎዝ በኤክስ ገፃቸው ባሰፈሩት ጽሁፍ የሩቢዮን ማዕቀብ አውግዘው፣ "የኩባ ኩባንያዎችን እና ኢኮኖሚውን የበለጠ ለመጉዳት" እየሞከሩ ነው ብለዋል።

ሮድሪጎዝ ጨምረውም ማዕቀቡ ቀድሞውኑ በእገዳው ምክንያት ችግር ውስጥ ለሚገኘው ሕዝብ መንግሥት የሚያቀርበውን መሠረታዊ አገልግሎት እንዳይሰጥ እንደሚያደርግ ገልጸዋል።

አሜሪካ በአገሪቱ ላይ የተለያዩ ማዕቀቦችን የጣለች ሲሆን በዚህ ዓመት መጀመሪያ ላይ ወደ ኩባ ነዳጅ እንዳይገባ አግዳለች። በዚህም ምክንያት የኤሌክትሪክ ኃይል መቋረጥ እና የምግብ እጥረት ተፈጥሯል።

ደሴቷ የኤሌክትሪክ መሠረተ ልማቷ ከውጭ በሚገባ ነዳጅ ላይ የተመሰረተ ሲሆን ሆስፒታሎች ጀኔሬተሮች ለመጠቀም ተገደዋል።

ለረዥም ጊዜ የሚቆይ እና ተደጋጋሚ የኃይል መቋረጥ ሕዝባዊ ተቃውሞ ረዥም እስር በሚያስከትልባት ኩባ እምብዛም ያልተለመዱ ተቃውሞዎችን አስከትሏል።