የቼዝ 'ግራንድ ማስተር' በማጭበርበር ስሜ ጠፍቷል ሲል የ100 ሚሊዮን ዶላር ካሳ ጠየቀ

ሃንስ ኒማን በውድድር ወቅት አጭበርብሬ አላውቅም ሲል የቀረበበትን ክስ አስተባብሎ ነበር

የፎቶው ባለመብት, Getty Images

ታትሟል

አሜሪካዊው የቼዝ ጨዋታ ግራንድ ማስተር ሃንስ ኒማን ተፎካካሪውን ማግኑስ ካርልሰንን በጨዋታ ወቅት አጭበርብረሃል ሲል ስሜን አጥፍቷል በሚል የ100 ሚሊዮን ዶላር ካሳ ጠየቀ።

በመላው ዓለም መነጋገሪያ ሆኖ የቆየውን ይህንን ክስ ይፋ ያደረገውን ቼዝ ዶት ኮም የተሰኘው ዌብሳይት ላይ የአሜሪካው ግራንድ ማስተር ተመሳሳይ ክስ አቅርቦበታል።

Chess.com ድr-ገጽ ኒማን ከ 100 ግዜ በላይ በበይነ መረብ ላይ በተደረጉ ጨዋታዎች ላይ ሳያጭበረብር አይቀርም ሲል ሪፖርት አድርጎ ነበር።

ኒማን እንደሚለው ሁለቱም ተከሳሾች ተመሳጥረው ያለውን መልካም ስም እና ገቢ የሚያገኝበትን ስራውን ለማሳጣት ሰርተዋል።

የቼዝ ዶት ኮም ጠበቃዎች ኒማን ያቀረበው ክስ ምንም አይነት መሰረት የሌለው ነው ሲሉ ውድቅ አድርገውታል። አክለውም በሃቅ ለሚጫወቱ የቼዝ ተጫዋቾች ሲባል እውነቱን ይፋ ማውጣት እንደሚያስፈልግ ገልጸዋል።

በጉዳዩ ላይ አስተያየት እንዲሰጥ የተጠየቀው ካርልሰን ምላሽ ሳይሰጥ ቀርቷል።

የ 19 ዓመቱ ኒማን "ተከሳሾች በቼዝ ውድድር ህይወቱ ላይ ካደረሱበት ከባድ ጉዳት ለማገገም’’ በሚል ካሳ እንዲከፍሉት ጠይቋል። ይህም ስሙን ከማጥፋት ባሻገር ከሞያው እንዲታገድ እና በጥቁር መዝገብ ውስጥ እንዲገባ ተመሳጥረው ሰርተዋል የሚል ክስን የያዘ ነው።

ኒማን በተጨማሪም ግራንድ ማስተር ሂካሩ ናካሙራ እነዚህን ክሶች በመከተል በ ቼዝ ዶት ኮም ላይ በመቅረብ በቀጥታ ስርጭት ተመሳሳይ ጉዳት አድርሶብኛል በሚል ከሶታል። ናካሙራ በጉዳዩ ላይ አስተያየት ከመስጠት ተቆጥቧል።

በቼዝ ጨዋታ ውስጥ የሁልግዜም ምርጥ ተጫዋች ነው ተብሎ የሚታመነው ካርልሰን ባሳለፍነው መስከረም ወር ውስጥ ከኒማን ጋር በአካል ተገናኝተው ባደረጉት ጨዋታ መሸነፉ ብዙዎችን አነጋግሯል።

የ 31 ዓመቱ ካርልሰን የ 19 ዓመቱን ኒማንን በጨዋታ ወቅት አጭበርብረሃል በሚል የከሰሰው ሲሆን በቼዙ አለም ያሳየው ፈጣን እድገት ለማመን በሚያስቸግር መልኩ ፈጣን ነበር ሲል ወቅሶታል።

ኒማን በበኩሉ ካርልሰን ሽንፈቱን መቀበል ስላቃተው እና ድጋሚም ሊያሸንፈው ስለማይችል ስም ማጥፋት ላይ አተኩሯል ሲል መልሷል።

ካርልሰንም ሆነ ቼዝ ዶት ኮም በኒማን ላይ ላቀረቡት ክስ ይሄ ነው የሚባል ማስረጃ እስካሁን ድረስ አላቀረቡም።

ቼዝ ዶት ኮም በዌብሳይቱ ላይ ባወጣው የ 72 ገጽ የምርመራ ውጤት ላይ ኒማን ከ 100 በላይ በሚሆኑ በበይነ መረብ ላይ የተደረጉ የቼዝ ግጥሚያዎች ላይ አጭበርብሯል ሲል ደምድሟል።

ይህ ትንታኔ አብዛኛው የኒማን የጨዋታ ሂደቶች በኮምፒውተር ከሚመከሩ ሂደቶች ጋር ተመሳሳይ መሆናቸውን እና ይህም ከሰዎች ብቃት የተሻለ እንደሆነ ይግልጻል።

ኒማን የ 12 እና የ 16 ዓመት ታዳጊ በነበረበት ወቅት ከዚህ በፊት በነበሩ መደበኛ ባልሆኑ ጨዋታዎች ላይ ማጭበርበሩን ቢያምንም በውድድር ወቅት ግን ይህንን በፍጹም አድርጎ እንደማያውቅ ተናግሯል።

ክሱን ተከትሎም ኒማን በቼዝ ዶት ኮም ላይ በሚደረጉ የበይነ መረብ ውድድሮች ብሎም ተቋሙ ስፖንሰር በሚያደርጋቸው የፊት ለፊት ውድድሮች ላይ እንዳይሳተፍ ታግዷል።

ኒማን የቼዝ ዶት ኮም ውሳኔ በካርልሰን ጫና ውስጥ የወደቀ ነው ብሎ እንደሚያምን እና ራሱን ‘’የቼዝ ንጉስ’’ አድርጎ በማየቱ ቼዝ ጫወታ ውስጥ ምንም ነገር ማድረግ እችላለሁ ብሎ ያምናል ሲልም በክሱ ላይ ወርፎታል።