ኬንያ ውስጥ ሄሊኮፕተር ተከስክሶ የኢኳዶር የስለላ ኃላፊን ጨምሮ ሰባት ሰዎች ሞቱ

ወደ አደጋ ስፍራው የሚወርድ የቀይ መስቀል ሠራተኛ

የፎቶው ባለመብት, Kenya Red Cross/Handout via Reuters

ታትሟል
የንባብ ጊዜ: 2 ደቂቃ

በኬንያ በተከሰተ የሄሊኮፕተር መከስከስ አደጋ የኢኳዶር የስለላ ኃላፊ እና ባለቤታቸውን ጨምሮ የሰባት ሰዎች ሕይወት አለፈ።

የስለላ ኃላፊው ሚኬሌ ሴንሲ ኮንቱሂ እና ባለቤታቸው ስቴፋኒ ሆሊሃን የሞቱበት አደጋ የተከሰተው ረቡዕ ዕለት ኬንያ ሳምቡሩ ግዛት ውስጥ ነው።

ሌሎቹ አምስት ሟቾች አሜሪካውያን እንደሆኑ የዋሽንግተን ውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ቃል አቀባይ ተናግረዋል።

የኬንያ ሲቪል አቪዬሽን ባለሥልጣን እንደገለጸው 'ሎይሳባ' ከተባለው የዱር እንስሳት ጥበቃ ጣቢያ የተነሳው ሄሊኮፕተር፣ በርካታ ብሔራዊ ፓርኮችን አቋርጦ ወደሚያልፈው 'ኢዋሶ ኚሮ' ወንዝ ለጉብኝት እየተጓዘ ነበር።

አደጋው የደረሰበት ሳምቡሩ ግዛት በርካታ የግል የዱር እንስሳት ጥበቃ ጣቢያዎች የሚገኙበት እና አስደናቂ መልክዓ ምድርን የያዘ ታዋቂ የቱሪስት መዳረሻ ነው።

ከአደጋ ስፍራው የወጡ ቪዲዮዎች ላይ ኦሎሎክዌ ተራራ ጫካ ውስጥ ከሚገኘው የአደጋ ስፍራ ጭስ ሲወጣ እና የኬንያ ቀይ መስቀል አባላት እየተቃጠለ ወደሚገኘው ስብርባሪ ሲጠጉ ይታያል።

የኢኳዶር መንግሥት፣ በአውሮፓውያኑ በ2024 የአገሪቱ ስትራቴጂክ ኢንተሊጀንስ ማዕከል ዋና ዳይሬክተር ሆነው ስለተሾሙት ሚኬሌ ሴንሲ ሞት እስከአሁን ዝርዝር መረጃ አልወጣም።

የአገሪቱ ፕሬዝዳንት ጽሕፈት ቤት መንግሥት በደኅነንት ኃላፊው ሞት የተሰማውን ሐዘን ገልጿል።

የቀድሞው የኢኳዶር ፕሬዝዳንት ጊለርሞ ላሶ የስለላ ኃላፊው በሄሊኮፕተር አደጋ ህይወታቸው እንዳለፈ ጠቅሰዋል።

የተከሰከሰው ሄሊኮፕተር ባለቤት የሆነው የኬንያ የአውሮፕላን ኪራይ ተቋም 'ሌዲ ሎሪ ሄሊኮፕተርስ'፣ በአደጋው የተሰማውን "ጥልቅ ሐዘን" ገልጿል።

ተቋሙ ባወጣው መግለጫ፣ "ለእንግዶቹ፣ ለበረራው አባላት፣ ለቤተሰቦቻቸው እና ለሚወዷቸው ሰዎች እንዲሁም በዚህ አሳዛኝ አደጋ ለተጎዱ ሁሉ ጥልቅ ሐዘናችንን እንገልፃለን" ብሏል።

የቢቢሲ አጋር የሆነው 'ሲቢኤስ ኒውስ' የተመለከተው የውስጥ ማስታወሻ እንደሚያሳየው በአደጋው ሕይወታቸው ካጡት አሜሪካውያን አንዱ የኤንቢሲ ዩኒቨርሳል ጋዜጠኛ ሆሴ አልቤርቶ ሱዋሬዝ ነው።

በማያሚ የሬስቶራንት ባለቤት የሆነው ሮጀር ዱዋርቴም ከሞቱት አሜሪካውያን መካከል እንደሚገኝበት የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

የቀሪዎቹ አራት አሜሪካውያን ተጎጂዎች ማንነት አልተለየም።

መጀመሪያ ላይ የወጡ ዘገባዎች በአደጋው ሕይወታቸው ያለፈው ስድስት ጎብኚዎች እና አንድ ፓይለት እንደሆኑ አመልክተው ነበር።

ኬንያ ውስጥ የሄሊኮፕተር አደጋ ያልተለመደ አይደለም።

የካቲት ላይ ናንዲ በተባለው የስምጥ ሸለቆ ስፍራ በተከሰተ የሄሊኮፕተር መከስከስ አደጋ የፓርላማ አባልን ጨምሮ ስድስት ሰዎች ሕይወታቸው አልፏል።

በአውሮፓውያኑ 2024 ደግሞ 11 ሰዎችን አሳፍሮ የነበረ የኬንያ መከላከያ ሄሊኮፕተር በአገሪቱ ምዕራባዊ ክፍል ተከስክሶ፤ የሠራዊቱ ኢታማዦር ሹም ጄኔራል ፍራንሲስ ኦሞንዲ ኦጎላን ጨምሮ ዘጠኝ ሰዎች ሞተዋል።

በሰኔ 2021 በዋና ከተማዋ ናይሮቢ አቅራቢያ ለማረፍ የሞከረ ሌላ ወታደራዊ ሄሊኮፕተር በመከስከሱ ቢያንስ 10 ወታደሮች ሕይወታቸው አልፏል።