ደቡብ ኮሪያ ከአሜሪካ ጋር ያላትን ወታደራዊ ልምምድ በዋሺንግተን ጥያቄ መሠረት አሳጠረች

ታትሟል
የንባብ ጊዜ: 2 ደቂቃ

ደቡብ ኮሪያ ከአሜሪካ ጋር የምታደርገውን ዓመታዊ የጋራ ወታደራዊ ልምምድ በዋሽንግተን ጥያቄ መሠረት በስድስት ቀናት እንደምታሳጥር የመከላከያ ሚኒስቴሯ አስታወቁ።

ሴኡል የ2026ቱ ወታደራዊ ልምምድ "ጊዜ እና ስፋት" የተስተካከለው "ከአሜሪካ ወገን በቀረበ ሀሳብ" ምክንያት ነው ብላለች።

ልምምዱ እንደታቀደው እአአ ነሐሴ 27 ሳይሆን ነሐሴ 21 ላይ ይጠናቀቃል። ይህ የሆነው ዶናልድ ትራምፕ ከሰሜን ኮሪያው መሪ ኪም ጆንግ ኡን ጋር ያላቸውን "በጣም ጥሩ" ግንኙነት በመጥቀስ ከደቡብ ኮሪያ ጋር የሚያደርጉትን ልምምዶች ለመቀነስ ዕቅድ እንዳላቸው ካሳወቁ በኋላ ነው።

የደቡብ ኮሪያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቾ ህዩን በፓርላማ ላይ እንደተናገሩት የደቡብ ኮሪያም ሆነ የአሜሪካ ባለሥልጣናት የትራምፕን ዕቅድ አስቀድመው አያውቁም ነበር።

ወታደራዊ ልምምዶቹ "በከፊል በመጠን ይቀንሳሉ" ስትል ሴኡል አስታውቃለች።

በልምምዱ ላይ ስለተደረጉ ቅነሳዎች "ዝርዝር ጉዳዮች" አሁንም ውይይት እየተደረገባቸው መሆኑም ተጠቅሷል።

የሁለቱ አገራት ወታደራዊ ልምምድ ማጠሩ የተሰማው የአሜሪካ ባለሥልጣናት ለዎል ስትሪት ጆርናል ትራምፕ ረዳቶቻቸውን ከኪም ጆንግ ኡን ጋር እንዲገናኙ ግፊት እያደረጉ ነው ሲሉ ከተናገሩ በኋላ ነው።

ምንጮች ለጋዜጣው እንደገለጹት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት በሚቀጥለው የእስያ ጉብኝታቸው ወቅት ከኪም ጋር በአካል ተገናኝተው ለመወያየት እንደሚፈልጉ ተናግረዋል።

ፕሬዚዳንቱ በኅዳር ወር በቻይና በሚካሄደው የእስያ-ፓሲፊክ የኢኮኖሚ ትብብር ስብሰባ ወቅት ከሰሜን ኮሪያው መሪ ጋር ሊገናኙ ይችላሉ ሲሉ ግምታቸውን አስቀምጠዋል።

ቅዳሜና እሁድ ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ "እነዚህ ልምምዶች ውድ ከመሆናቸውም በላይ አብዛኛዎቹ ወጪዎች የሚሸፍኑት በዩናይትድ ስቴትስ (እንደተለመደው!) ነው፤ ነገር ግን ሙሉ በሙሉ ተገቢ ያልሆነ እና ጠብ አጫሪነት የሚንጸባረቅበት ነው" ብለዋል።

አክለውም "ምንም እንኳን በተወሰነ መልኩ ባይገናኝም፣ በቅርቡ የደቡብ ኮሪያን ፕሬዝዳንት የኢራንን እስላማዊ ሪፐብሊክ ከኒውክሌር ነፃ ለማውጣት ከእኛ ጋር ለመቀላቀል ይፈልጉ እንደሆነ ጠይቄያቸው ነበር፣ እርሳቸውም 'አይ አመሰግናለሁ!' አሉኝ" ብለዋል።

ፕሬዝዳንቱ ሰኞ ዕለት በኦቫል ኦፊስ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፥ ውሳኔያቸውን ደቡብ ኮሪያ በኢራን ጉዳይ "ትንሽም ድጋፍ ለማድረግ" ፈቃደኛ ካለመሆኗ ጋር በግልጽ አያይዘውታል።

"ከጎረቤትህ ኪም ጆንግ ኡን የሚጠብቁህ 39,000 ወታደሮች አሉን፤ በኢራን ውስጥ በጣም ቀላል በሆነ ወታደራዊ ዘመቻ ላይ ልትረዳን አትችልም" ካሉ በኋላ "ይህ እንግዳ ነገር ነው" ሲሉ ተናግረዋል።

ባለፈው ሳምንት የአሜሪካ እና ደቡብ ኮሪያ ወታደራዊ መሪዎች ለ11 ቀናት የሚቆይ ወታደራዊ ልምምድ እንደሚደረግ አስታውቀዋል።

'ዩልቺ ፍሪደም ሺልድ' የተባለው ልምምድ አምና ከነበረው ጋር ተመሳሳይ እንደሚሆን እና ወደ 18,000 የደቡብ ኮሪያ ወታደሮች እንደሚሳተፉበት ተገልጿል።

ሰሜን ኮሪያ ለሩሲያ ጦር ወታደሮች መስጠቷን የአሜሪካ እና ደቡብ ኮሪያ ወታደራዊ መሪዎች ተናግረዋል።

የአሜሪካ ጦር ቃል አቀባይ ራየን ዶናልድ "ሥልጠና የምናደርገው ይሄ ስጋት ስላለ ነው" ብለዋል።

ወደ 28,500 የሚጠጉ የአሜሪካ ወታደሮች በደቡብ ኮሪያ ተሰማርተዋል።

ከዚህ ጋዜጣዊ መግለጫ በኋላ የሰሜን ኮሪያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የጋራ ወታደራዊ ልምምዱን "ለከባድ ጦርነት የሚደረግ ልምምድ" ሲሉ አውግዘዋል።