ቱፓክን ማን ገደለው? ከ30 ዓመታት በኋላ ውሳኔ ያገኘ የወንጀል ድርጊት

ታትሟል
የንባብ ጊዜ: 3 ደቂቃ

የቀድሞው የወሮበላዎች ቡድን አለቃ ዱዌን "ኪፊ ዲ" ዴቪስ፣ የቱፓክ ሻኩርን ግድያ በማቀነባበር ጥፋተኛ ሆኖ ተገኘ።

ይህም ለ30 ዓመታት ያህል የሂፕ-ሆፕ አድናቂዎች ትኩረት የሆነው እና ዕልባት ሳያገኝ የቆየው ጉዳይ የመጀመሪያ የጥፋተኝነት ውሳኔ ነው።

ዳኞች ዴቪስን እአአ መስከረም 7/1996 በላስ ቬጋስ እየተንቀሳቀሰ ካለ መኪና በተፈፀመ ተኩስ የራፕ ኮከቡን በመግደል ወንጀል ጥፋተኛ ሆኖ አግኝተውታል።

ጥቁር ልብስ ለብሶ ችሎቱን የታደመው የ63 ዓመቱ ዴቪስ፣ በላስ ቬጋስ ፍርድ ቤት ፍርዱ ከተነበበ በኋላ ይግባኝ እንደሚል ተናግሯል። የቱፓክ ሻኩር ዘመዶች እጅ ለእጅ ተያይዘው፣ አንዳንዶቹም ተቃቅፈው ሲያለቅሱ ታይተዋል።

ከፍተኛ ተጽዕኖ ፈጣሪ ከሆኑ የራፕ ድምጻውያን አንዱ የነበረው ቱፓክ በሙያው ከፍተኛ ደረጃ ላይ ደርሶ በነበረበት በ25 ዓመቱ ነበር ተገደለው። አርቲስቱ በዓለም አቀፍ ደረጃ ከ75 ሚሊዮን በላይ ቅጂዎችን ሸጧል።

የ 'ሳውዝ ሳይድ ኮምፕተን ክሪፕስ' የጎዳና ላይ ወሮበላ ቡድን መሪ የነበረው ዴቪስ፣ ሻኩርን የገደለውን ጥይት በቀጥታ ባይተኩስም፣ የወንድሙ ልጅ ኦርላንዶ አንደርሰን እንዲተኩስ ማዘዙን እና ሽጉጡን ማቅረቡን በማንሳት ዐቃቤ ሕጎች በችሎቱ ላይ ተከራክረዋል።

ከግድያው ከጥቂት ሰዓታት በፊት በላስ ቬጋስ ከሻኩር እና ከራፐሩ የቡድን አባላት ጋር የተፈጠረውን ፀብ ተከትሎ ዴቪስ ግድያውን ለመፈፀም ማቀዱን ለፍርድ ቤቱ ተናግረዋል።

ጉዳዩ ላለፉት 30 ዓመታት በአሜሪካ በጣም ከሚታወቁ ያልተፈቱ ጉዳዮች አንዱ ሆኖ የቆየ ሲሆን ስፍር ቁጥር የሌላቸውን ሴራዎችም አስነስቷል።

የሻኩር ግድያ የተፈፀመው በኢስት ኮስት እና በዌስት ኮስት የራፕ ትዕይንቶች መካከል ከፍተኛ ፉክክር በነበረበት እንዲሁም በሂፕ-ሆፕ ውስጥ ሥር በሰደዱት በብሌድስ እና ክሪፕስ የወሮበላ ቡድኖች መካከል ግጭት በነበረበት ወቅት ነው።

ቤተሰቦቹ በፍርድ ቤት ስሜታዊ ሆነው ታይተዋል፤ እህቱ ፍርዱ ከተነበበ በኋላ ዐቃቤ ሕግን አቅፋ ስታለቅስ ሌሎቹ ደግሞ ቁጭ እንዳሉ እያለቀሱ ታይተዋል።

ከውጭ የነበሩ የሻኩር ደጋፊዎችም በእልቅሻ፣ በጩኸት እና በተለያየ መልኩ ስሜታቸውን ሲገልፁ ነበር።

ለፍርዱ ጉዳይ ቁልፍ ማስረጃ የነበረው፣ ቱፓክ የተገደለበት ጥይቶች የተተኮሱበት ነጭ ካዲላክ መኪና ውስጥ መሆኑን በተደጋጋሚ የተናገረበት የራሱ የዴቪስ ቃላት ሲሆኑ ይህንንም በይፋ አምኗል።

እአአ በ2008፣ በመድረክ ስሙ ኖቶሪየስ ቢ.አይ.ጂ. በመባል የሚታወቀውን ራፐር ክሪስቶፈር ዋላስ ሞትን በተመለከተ ፖሊስ ባደረገለት ምስጢራዊ ቃለ ምልልስ ወቅትም በሻኩር ሞት ላይ ስለነበረው ሚና ተናግሮ ነበር።

ዴቪስ በ2019 ባሳተመው 'ኮምፕተን ስትሪት ሌጀንድ' የተባለ መጽሐፉ ላይ ባሰፈረው ማስታወሻም እንዲሁ ስለተጫወተው ሚና የበለጠ ማብራሪያ ሰጥቷል። ይህም በስምምነታቸው መሠረት በምስጢር ተይዞ ነበር የቆየው።

ነገር ግን በመጽሐፉ ይፋ ያደረገው እውነታ እና የሚዲያ ቃለ ምልልሶቹ፣ ምንም አይነት የወንጀል ክስ እንዳይቀርብበት ያደረገውን እና ከባለሥልጣናት ጋር የፈፀመውን ስምምነት ውድቅ አድርገውታል። ለተፈፀመበት የግድያ ክስ ችሎት ላይ ከፖሊስ ጋር ያደረገው ቃለ ምልልስ ጥቅም ላይ መዋል እንደሚችል ፍርድ ቤቱ ወስኗል።

ዐቃቤ ሕግ ቢኑ ፓላል በመዝጊያ ክርክራቸው፣ ዳኞች ዴቪስ ራሱ የሰጠውን ቃል መሠረት በማድረግ በጥፋተኝነት እንዲፈርዱበት ጠይቀዋል።

"ለቱፓክ ሻኩር ግድያ ተጠያቂው እርሱ ስለመሆኑ" ዴቪስ ለዓመታት በዘጋቢ ፊልሞች፣ በማስታወሻው፣ በፖድካስቶች እና በፖሊስ ቃለ መጠይቅ ሲናገር መቆየቱን ዐቃቤ ሕጉ ተናግረዋል።

"የተኩሱን ትዕዛዝ የሰጠው እርሱ ነበር። የሳውዝ ሳይድ ክሪፕስ መሪ ነው" ሲሉ ፓላል ለዳኞች ተናግረዋል።

"ትዕዛዝ ሰጪው ባቀበለው ሽጉጥ ተኩስ ሲተኮስ፣ እሱ ተጠያቂ እንደሚሆን ምንም ጥርጥር የለውም"።

የዴቪስ ተከላካይ ቡድን፣ በግለሰቡ ላይ የከረበው ክስ ልብ ወለድ እንደሆነ ዳኞቹን ለማሳመን ሞክሯል። ስለራሱ ጀግንነት እና ተግባራት በግነት ያወራው መጽሐፉን ለመሸጥ እና ገንዘብ ለማግኘት በማሰብ ያደረገው እንደሆነ አንስተው ተከራክረዋል።

ጠበቃው ማይክል ሳንፍት፣ ዳኞቹ ደንበኛቸውን መጽሐፍ ለመሸጥ ተረት የተናገረ ውሸታም ነው ብለው እንዲያጣጥሉት በክርክሩ መደምደሚያ ላይ ጠይቋል። ስለድርጊቱ "ማረጋገጫ የለም" ሲሉም አክለዋል።

ይሁን እንጂ መከራከሪያቸው ደንበኛቸውን ጥፋተኛ ከመባል አልታደገም።

ሰኞ ዕለት በነበረው ችሎት ዳኞች የጥፋተኝነት ውሳኔ ላይ ደርሰዋል።

የፍርድ ውሳኔ ለመስጠት በአውሮፓውያኑ ለጥቅምት 13 ተቀጥሯል።

ዴቪስ "ይግባኝ ማለት እንደሚፈልግ" ለፍርድ ቤቱ የገለፀ ሲሆን፣ ይግባኝ ማለት የሚችለው ከቅጣት ውሳኔ በኋላ መሆኑን ዳኛው አስረድተዋል።