ሁሉንም ነገር ካፈራረሰው ጎርፍ ጋር በረንዳቸው ላይ የተፋጠጡት ቤተሰቦች በመጨረሻ ምን ሆኑ?

ታትሟል
የንባብ ጊዜ: 4 ደቂቃ

ኔፓልን ክፉኛ ያወደመውን የጎርፍ አደጋ የሚያሳዩ አስደንጋጭ ፎቶዎች እና ቪዲዮዎች በስፋት እየተሠራጩ ነው። በማኅበራዊ ሚዲያ የተጋሩት ምሥሎች በኔፓል እና በቲቤት ድንበር አካባቢ የጎርፍ አደጋ ያደረሰውን ሰፊ ውድመት ያሳያሉ።

በማኅበራዊ ሚዲያ በሰፊው ከተሠራጩ ቪዲዮዎች ውስጥ፣ ፈጣን እና ኃይለኛ ደራሽ ጎርፍ ከብዙ ፍርስራሽ ጋር ተደባልቆ አካባቢዎችን እየዋጠ ሲያልፍ ይታያል። በእነዚህ ምሥሎች ውስጥ፣ በጠንካራ የግንባታ ቁሳቁሶች የተሠሩ አንዳንድ ቤቶች እንኳን የውሃውን ኃይለኛ መቋቋም ተስኗቸው፣ እንደ እንጨት ቁራጭ በጎርፉ ተጠርገው ሲወሰዱ ይታያሉ።

ሆኖም ከእነዚህ አስደንጋጭ ቪዲዮዎች መካከል አንድ ሌላ ቪዲዮ በተለየ ሁኔታ የብዙዎችን ትኩረት ስቧል፤ በማኅበራዊ ሚዲያም ስለቪዲዮው የተለያዩ አስተያየቶች እና ጥያቄዎች ተነስተዋል።

በዚህ ቪዲዮ ውስጥ አንድ ወንድ፣ አንዲት ሴት እና ትንሽ ልጅ በአንድ ባለሁለት ወለል ትንሽዬ ሕንፃ በሁለተኛ ፎቅ በረንዳ ላይ ሆነው ከፍተኛ ኃይል ያለው አደገኛ ጎርፍ በአስፈሪ ሁኔታ አካባቢውን እያፈራረሰ ሲገሰግስ ይታያል። በጭቃ የተሞላው የጎርፍ ውሃ ከትላልቅ ድንጋዮች እና ፍርስራሾች ጋር ተቀላቅሎ በዙሪያቸው ይፈስሳል።

የውሃው ኃይለኛ ፍሰት ያለማቋረጥ ከሕንፃው ጋር የሚጋጭ ሲሆን፣ በማንኛውም ቅጽበት ቤቱን ጭምር ጠርጎ ሊወስደው የሚችል ይመስላል። የቤተሰቡ አባላትም ምንም ማድረግ ሳይችሉ የእርዳታ መምጣትን በተስፋ እየጠበቁ ነበር።

አሁን ድረስ በኔፓል በደረሰው የጎርፍ አደጋ የሞቱት ሰዎች ቁጥር ወደ አንድ ሺህ እንደተጠጋ እና ከ4,000 በላይ ሰዎች አስካሁን የደረሱበት እንዳልታወቀ ተነግሯል።

ከጎርፉ በኋላ ዓለም አቀፍ የእርዳታ ድርጅቶች እና የበርካታ አገራት መንግሥታት በኔፓል የሚያካሂዱትን የነፍስ ማዳን እና የእርዳታ ሥራ አጠናክረዋል።

የአውሮፓ ኅብረት፣ ካናዳ፣ አሜሪካ እና ሌሎች በርካታ አገራት ለኔፓል የእርዳታ ቁሳቁሶችን ወይም የገንዘብ ድጋፍ መላካቸውን አስታውቀዋል።

አንድ የተባበሩት መንግሥታት ቃል አቀባይ እንደተናገሩት፣ ከ10,000 በላይ ቤተሰቦች አስቸኳይ የምግብ እና ንጹህ የመጠጥ ውኃ አቅርቦት ይፈልጋሉ።

የቢቢሲ መረጃ ማጣሪያ (ቢቢ ቬሪፋይ) ባደረገው ምርመራ፣ ቪዲዮው በተቀረጸበት ጊዜ እነዚህ ሰዎች በዚያው ሕንፃ ውስጥ ተጠልለው እንደነበሩ ተረጋግጧል።

ቢቢሲ ቬሪፋይ ማንነታቸውን አልገለጸም፤ ሆኖም የቤተሰቡ አባላት በሆነ መንገድ ከአደጋው በሕይወት መትረፋቸውን አስታውቋል። በቪዲዮው ውስጥ በሕንጻው በረንዳ ላይ የቆመ አንድ ሰው እርዳታ ለመጠየቅ ቀይ ቀለም ያለውን ሻሽ ሲያውለበልብ ይታያል።

የጎርፉ ኃይል ከተቀነሰ በኋላ የአካባቢው ነዋሪዎች ሰዎቹን ለመርዳት ወደ ስፍራው ደርሰዋል።

በቪዲዮው ውስጥ ቢያንስ ሦስት ሰዎች ይታያሉ፤ አንድ ወንድ፣ አንዲት ሴት እና ትንሽ ልጅ የምትመስል ሴት ሕፃን ነበሩ። እነርሱ በሕንፃው ሁለተኛ ፎቅ ላይ በረንዳ በሚመስል ክፍል ውስጥ ተጠልለው ነበር።

በዙሪያቸው ጭቃ የተሞላ የጎርፍ ውሃ ይፈስ ነበር፤ ትላልቅ አለቶች እና ፍርስራሾችም ከውሃው ጋር እየተላተሙ በኃይል ሲጓዙ ይታዩ ነበር።

እነዚህ ከባድ ነገሮችም ያለማቋረጥ ከሕንፃው ጋር ይጋጩ ነበር፤ ጎርፉም ቤቱን ጭምር ጠርጎ ሊወስደው የሚሞክር ይመስል ነበር። በሕንፃው ውስጥ ያሉት ሰዎችም ተስፋ ቢስ ሆነው በበረንዳው ላይ ቆመው ይታያሉ።

በሌላ የቪዲዮው ክፍል ውስጥ አንዲት ሴት ወደ ከሕንጻው አናት ላይ ወጥታ እርዳታ ለመጠየቅ ቀይ ሻሽ ስታውለበልብ ትታያለች።

የማኅበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚዎች ምን አሉ?

ኤሪክ ቺን የተባሉ ዓለም አቀፍ ጉዳዮች ተንታኝ ከቪዲዮው የተወሰዱ ምሥሎችን በማጋራት እንዲህ ሲሉ ጽፈዋል "ባለፉት ዓመታት እንደዚህ ያለ አስደንጋጭ ትዕይንት አይተን አናውቅም ማለት ይቻላል። በዚህ አውዳሚ ጎርፍ መካከል አንድ ቤት አሁንም ቆሞ ታይቷል፤ ይህ ጎርፍ በዙሪያው ያለን ሁሉን ነገር አውድሟል።"

በኔፓል እና በቲቤት መካከል ባለው ሸለቆ ውስጥ ጭቃ፣ በረዶ፣ ድንጋይ እና ውሃ የተቀላቀለ ግዙፍ ጎርፍ እየፈሰሰ ባለበት ወቅት፣ አንዳንድ ሰዎች በሕንጻዎች በረንዳዎች እና በቤቶች አናት ላይ ወጥተው ተጠልለው ቆይተዋል።

ይህ ታሪክ የአሃዝና የቁጥር ጉዳይ ብቻ አይደለም፤ ይልቁንም ቀጣዩ የጎርፍ ማዕበል የቀራቸውን የመጨረሻ የመጠለያ ቦታ እንዳያጠፋው በፍርሃት የሚጠባበቅ የአንድ ቤተሰብ ታሪክ ነው።

ኤሪክ ቺን አክለውም "በሕይወት እንዲተርፉ እጸልያለሁ፤ ቀጣዩ የጎርፍ ማዕበል ሳይደርስ የነፍስ አድን ቡድኖች ወደ እነሱ መድረስ እንዲችሉም እመኛለሁ" ብለዋል።

ይህን አስፈሪ ትዕይንት ለመመልከት አስቸጋሪ የሚሆነው የተፈጥሮ አስጨናቂ ኃይል በመሆኑ ብቻ አይደለም።

የኔፓል ባለሥልጣናት እና የአካባቢው ምንጮች እንደሚሉት፣ በቲቤት ውስጥ በሚገኘው "ለሄንዴ ቦትኮሺ" ወንዝ አካባቢ የነበረ አንድ የበረዶ ግግር ክፍል ሲናድ፣ ከፍተኛ መጠን ያለው ፍርስራሽ ወደ ወንዙ ገብቶ ጎርፉን አስከትሏል።

በታችኛው አካባቢ የሚኖሩ ሰዎች ከቻይና ባለሥልጣናት በወቅቱ ትክክለኛ ማስጠንቀቂያ አልደረሳቸውም ይላሉ። እንደ ገለጻቸውም፣ የመጀመሪያዎቹ ማስጠንቀቂያዎች የተሰሙት እርስ በርሳቸው ከሚተዋወቁ የአካባቢው ነዋሪዎች ነበር።

የትሪሹሊ ወንዝ የውሃ መጠን በ30 ደቂቃዎች ውስጥ ወደ 9 ሜትር የሚጠጋ ጭማሪ አሳይቷል። በርካቶች እንደሚሉት፣ ይህ ግማሽ ሰዓት ደኅንነቱ ወደ ተጠበቀ ስፍራ መድረስ እና ሁሉ ነገር ሲፈራርስ እና ተጠርጎ ሲወሰድ በዐይናቸው በመመልከት መካከል ያለውን ወሳኝ ልዩነት ፈጥሮ ነበር።

ቻይና በኋላ ላይ በማስጠንቀቂያው መዘግየት የቀረበባትን ክስ ውድቅ አድርጋለች። እንደ ቻይና አባባል የበረዶ እና የድንጋይ መናድ በጣም ድንገተኛ ስለነበር፣ የወንዝ ክትትል መሣሪያዎች እንኳን ሁኔታውን በትክክል ለመመዝገብ ችግር ገጥሟቸው ነበር።

ሆኖም ከ2025 በዚሁ ወንዝ ላይ ካጋጠመው ጎርፍ በኋላ የተዘጋጀው የድንበር ተሻጋሪ ፈጣን የማስጠንቀቂያ ሥርዓት፣ ይህ አደጋ ከመከሰቱ በፊት ለምን ወደ ተግባር እንዳልተቀየረ የሚቀርበው ጥያቄ አሁንም አልተመለሰም።

ይህ ጉዳይ የቴክኒክ ወይም የአስተዳደር እንከን ብቻ አይደለም። አንዳንድ ሰዎች ለማምለጥ በቂ ጊዜ ያላገኙበት ምክንያት ሕይወታቸውን ሊያድኑ የሚችሉ ዋጋ ያላቸው ደቂቃዎችን ቀድመው አለማወቃቸው ነው።

እንደ ኤሪክ ቺን ገለጻ፣ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ሞተዋል፤ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችም አሁንም ድረስ ደብዛቸው ጠፍቷል። ከእነዚህ መካከል በኤሌክሪክ ማመንጫ ግንባታ ላይ የነበሩ ሠራተኞች፣ የውጭ አገር ቱሪስቶች እና ተራራ ወጪዎችም እንዳሉ ተነግሯል።

ቺን እንደሚሉት፣ በጎርፉ መካከል አሁንም ቆሞ የሚታየው ቤት የተአምር ምልክት ሳይሆን፣ በሕይወት እና በሞት መካከል ያለውን እጅግ ቀጭን መስመር ያሳያል።

"በውስጡ የነበረው ቤተሰብ አሁንም ደኅንነቱ እንዲጠበቅ እጸልያለሁ" ብለዋል ቺን።