ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
በኔፓል እና ቲቤት ድንበር ላይ በተከሰተ ድንገተኛ ጎርፍ 160 ሰዎች ሲሞቱ በመቶዎች የሚቆጠሩ ጠፉ
በኔፓል እና በቲቤት ድንበር ላይ መንደሮችን ጠርጎ የወሰደ እንዲሁም መንገዶችን ያፈራረሰ ድንገተኛ ጎርፍ እና የመሬት ናዳ ምክንያት ቢያንስ 160 ሰዎች ሕይወታቸው አለፈ።
አደጋው በተከሰተበት አካባቢ የነበሩ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ደግሞ የደረሱበት አልታወቀም።
ጎርፉ ረቡዕ ጠዋት ላይ ከኔፓል ዋና ከተማ ካትማንዱ በስተሰሜን በሚገኘው ራሱዋ ግዛት ነው የተከሰተው።
የጎርፉ አደጋው የተነሳው፣ በአካባቢው በተከሰተ የመሬት መንቀጥቀጥ ምክንያት የበረዶ ግግር ተንዶ ወደ ብሆቴ ኮሺ ወንዝ በመፍሰሱ እንደሆነ የመጀመሪያ ደረጃ መረጃዎች አመልክተዋል።
በሁለቱም የድንበር አካባቢዎች የፍለጋ ስራው የቀጠለ ሲሆን፣ በሚቀጥሉት ቀናት ውስጥ የሟቾች ቁጥር በከፍተኛ መጠን ይጨምራል ተብሎ ይጠበቃል።
ራስ ገዝ የሆነችው ቲቤትን የሚትቆጣጠረ የቻይና መንግሥት መገናኛ ብዙኃን፣ ከፍተኛ ጉዳት መድረሱን ገልጿል። የኔፓል ባለሥልጣናት ከፍተኛ መጠን ያለው ሞት እና ውድመት እንደሚኖር ገምተዋል።
ከ28 አገራት የተውጣጡ 466 የውጭ ዜጎችን ጨምሮ 579 ጎብኚዎች የደረሱበትን ለማወቅ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ባለሥልጣናት ተናግረዋል።
ፖሊስ እንደገለፀው፣ ከጠፉት ጎብኚዎች መካከል 113ቱ ኔፓላውያን፣ 54ቱ ከአሜሪካ የሄዱ፣ 33ቱ የዩናይትድ ኪንግደም ዜጎች ናቸው።
በቲቤት በኩል ደግሞ ሦስት ሰዎች መሞታቸውን እና 265 ሰዎች መጥፋታቸውን የቻይና ብሔራዊ ሚዲያ ዘግቧል። ከጠፉት መካከል ከዩኬ የሄዱ 12 ጎብኚዎችን ጨምሮ አሜሪካውያን፣ ማሌዢያውያን፣ ደቡብ አፍሪካውያን እና ህንዳውያን ይገኙበታል።
'አልፒን ኢኮ ትሬክ' የተባለ የኔፓል አስጎብኚ ድርጅት፣ በኔፓል-ቲቤት ድንበር ላይ ሲያስጎበኛቸው የነበሩ 12 ብሪታንያውያን መጥፋታቸውን አረጋግጧል።
የድርጅቱ ኃላፊ ራም ኩማር አዲካሪ፣ ሁለት የአየርላንድ እና አራት የደቡብ አፍሪካ ዜጎችም ጠፍተዋል ተብሎ እንደሚገመት ተናግረዋል።
የጠፉት ብሪታኒያውያን እድሜያቸው ከ13 እስከ 65 እንደሆነ በፒኤ የዜና ወኪል የተጋራው የጉዞ መረጃ ያመለክታል።
ከቲቤት ወደ ኔፓል ከሚፈሰው ከብሆቴ ኮሺ ወንዝ በታች የሚገኙ በርካታ ስፍራዎች በከፍተኛ ማስጠንቀቂያ ውስጥ የሚገኙ ሲሆን፣ በአካባቢው የመንገዶች ፣ የመገናኛ አውታሮች እና የኃይል አቅርቦት አገልግሎቶች ተቋርጠዋል።
ከኔፓል የወጡ የተረጋገጡ ቪዲዮዎች፣ በጎርፉ ድልድይ ተሰብሮ ሲወሰድ፣ ብዙ ፎቆች ያሉት ህንጻ ሲወድቅ እና በርካታ ህንጻዎች ያሉት ከተማ ሲወድም አሳይተዋል።
ከኔፓል ዋና ከተማ ካትማንዱ በስተሰሜን ምዕራብ 25 ኪሎ ሜትር ላይ በምትገኘው ትሪሹሊ ባዛር ስለተከሰተው አደጋ የሚያሳዩ ቪዲዮዎችን ቢቢሲ ቬሪፋይ አረጋግጧል።
ከቪዲዮዎቹ አንዱ፣ የትሪሹሊ ወንዝ በድንገት ከልክ በላይ ሲሞላ እንዲሁም መጠኑ እና ፍጥነቱም እየጨመረ ሲሔድ ያሳያል። ቀጥሎም ድልድይ እና ህንጻዎችን ሲደረምስ የሚያሳይ ነው።
አጠቃላይ ቁጥራቸው ባይታወቅም በአደጋው በርካታ በወንዙ አቅራቢያ የሚገኙ ህንጻዎች ተጠርገው ተወስደዋል። አንዳንዱም ወድመዋል ወይም በደለል ተሞልተዋል።
በካትማንዱ የሚገኝ ዪ ሊያንግ የተባለ ቻይናዊ የቢዝነስ ሰው፣ በአካባቢው የነበሩ 7 የጭነት መኪኖቹ ከኔፓላውያን ሰራተኞች ጋር አድራሻቸው መጥፋቱን ለቢቢሲ ተናግሯል።
የኔፓል ጦር ቃል አቀባይ ራጃርም ባስኔት፣ ከማይሉንግ መንደር ብቻ የጠፉ 115 ሰዎችን የመፈለግ ስራ መቀጠሉን ለቢቢሲ ገልፀዋል።
የኔፓል የአገር ውስጥ ጉዳዮች ሚኒስቴር ደግሞ በቲሙሩ፣ ስያብሩቤሲ እና ቤትራዋቲ መንደሮችም የብዙ ሰዎች ሕይወት ጠፍቶ ሊሆን እንደሚችል አስታውቋል። ጎርፉ በትሪሹሊ የውሃ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክት ላይም ጉዳት አድርሷል።
በቲቤት በኩል ስላለው የጉዳት መጠን ግልጽ መረጃ የለም።
የህንድ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ፣ የኔፓል አቻቸውን ቤሌንድ ሻህን ማናገራቸውን በጠቀሱበት የኤክስ መልዕከታቸው፣ "በዚህ አስቸጋሪ ወቅት ህንዳውያን ከኔፓል ወንድሞቻቸው እና እህቶቻቸው ጋር እንደሚቆሙ" ገልፀዋል።
የኔፓል የአደጋ ጊዜ ባለሥልጣን፣ በወንዞች ዳርቻ ላይ የሚኖሩ ሰዎች ንቁ እንዲሆኑ እና ጥንቃቄ እንዲያደርጉ አስጠንቅቋል።
የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ሺሺር ክሃናል፣ 26 ፖሊሶች፣ 9 የታጠቁ የፖሊስ አባላት እና 44 ወታደሮች መጥፋታቸውን ለፓርላማው ገልፀዋል።
ጠዋት 2፡37 ላይ የተከሰተ የመሬት መንቀጥቀጥ ያስከተለው የበረዶ ግግር ናዳ ለደረሰው ጉዳት መንስዔ መሆኑንም ተናግረዋል።
አደጋው የደረሰበት ራሱዋ ግዛት፣ ባለፈው ዓመትም ከቻይና በኩል በተከሰተ የበረዶ ግግር ፍንዳታ ሳቢያ 18 ሰዎች የሞቱበት ነው።