ፕሬዝዳንት ባይደን የ6 ትሪሊየን ዶላር ዕቅድ አውጡ

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ጆ ባይደን የ2022 የበጀት ዕቅዳቸው 6 ትሪሊየን ዶላር እንዲሆን ሲያረቁ፤ በዕቅዱ በዓመቱ ከፌዴራል በጀት ጉድለት ጋር በተያያዘ በየዓመቱ ከአንድ ትሪሊየን ዶላር በላይ ይጨምራል፡፡
ባለፈው ዓመት በዶናልድ ትራምፕ ከቀረበው የ4.8 ትሪሊየን ዶላር ዕቅድ የሚበልጥ ሲሆን የመሰረተ ልማት ማዘመኛ እና የተስፋፋ ማኅበራዊ የደኅንነት መረብን እንደሚያካትት ተስፋ ተደርጓል፡፡
ሐሳቡ ለኮንግረሱ የሚሰጥ ሲሆን እንዲተገበር ድጋፍ ይፈልጋል፡፡
ከጸደቀም አሜሪካን ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ ወጪዋን ታይቶ በማይታወቅ መልኩ ከፍ ያደርገዋል፡፡
በጀቱ ፕሬዚዳንቱ ቅድሚያ የሚሰጡትን ነገሮች የሚያሳይ ፍንጭ ይሰጣል፡፡ በዚህም ባይደን ያቀረቡት ሐሳብ ተዛማጅ የሆነ የወጪ ደረጃዎች እና የተስፋፋ መንግሥት ራዕይ እንዳላቸው የሚያንፀባርቅ ነው፡፡
ባይደን በጀቱ "በቀጥታ በአሜሪካ ሕዝብ ላይ የሚውል እና የአገራችንን ኢኮኖሚ የሚያጠናክር እና በረዥም ጊዜም አጠቃላይ ኢኮኖሚውን የሚያሻሽል ነው" ብለዋል፡፡
የፕሬዚዳንት ባይደን ዕቅዶች ለመንገዶች፣ ድልድዮች፣ የብሮድባንድ ኢንተርኔት እና የውሃ ዘርፍ ተጨማሪ ገንዘብን ያካትታሉ፡፡
የአዲሱ የወጪ ጭማሪ በመጪዎቹ 10 ዓመታት ለሦስት እና ለአራት ዓመት ሕጻናት ነጻ የቅድመ ትምህርት ቤት ለማቅረብ 200 ቢሊዮን ዶላር ይመድባል። 109 ቢሊዮን ዶላር ደግሞ ሁሉም አሜሪካውያኖች የሁለት ዓመት ነጻ የኮሚኒቲ ኮሌጅ እንዲያገኙ ያግዛል፡፡
ዴሞክራቱ ፕሬዝዳንት በርካታ የግብር ጭማሪዎችን እና ሌሎች ገቢ ለማሳደግ የሚያስችሉ ዘዴዎችን ቢያቀርቡም ዕቅዱ በሚቀጥሉት ጥቂት ዓመታት ውስጥ የብድር ዕዳውን ወደ ከፍተኛ ደረጃ ያሳድገዋል፡፡
በሪፐብሊካኖች ከፍተኛ ነው የተባለለት በጀት በኋይት ሃውስ ቃል አቀባይ ጄን ሳኪ "ከጊዜ በኋላ በተሻለ የፋይናንስ ደረጃ ላይ ያደርሰናል" ተብሎለታል፡፡
ኮንግረሱ አዳዲስ የወጪ ሒሳቦችን ለማፅደቅ እስከ መስከረም መጨረሻ ድረስ ጊዜ አለው፡፡ አዲሱን በጀት ማሳለፍ ካልቻሉ የመንግሥት ሥራ በከፊል ሊዘጋ ይችላል፡፡
ዴሞክራቶች በምክር ቤቱ ውስጥ ጠባብ የአብላጫ ድምፅ አላቸው።












