ማህትማ ጋንዲ በእጅ የጻፏቸው ማስታወሻዎች በ1.9 ሚሊዮን ዶላር ተሸጡ
በሕንድ የነጻነት ትግል መሪ ማሃትማ ጋንዲ በእጅ የተጻፉ ማስታወሻዎች በሙምባይ ከተማ በተካሄደ ጨረታ በ1.9 ሚሊዮን ዶላር ተሸጡ።
የጋንዲ የቅርብ ሰው እና የነጻነት ታጋይ በነበሩት አናንድ ቲ ሂንጎራኒ ቤተሰቦች እጅ የነበሩት እነዚህ ማስታወሻዎች ከአውሮፓውያኑ 1944 እስከ 1946 ባለው ጊዜ ውስጥ የተጻፉ ናቸው።
ከእውነት፣ ከአመጻ ውጪ ከመሆን እንዲሁም ራስን ከመግዛት ጋር የተያያዙ ሐሳቦች ማስታወሻዎቹ ላይ ሰፍረዋል።
እነዚህን ማስታወሻዎች ለመግዛት የቀረበው የገንዘብ መጠን፣ ለአንድ የሕንድ ታሪካዊ ሰነድ የተሰጠ ከፍተኛው ዋጋ መሆኑን ጨረታውን ያዘጋጀው ‘ሳፍሮንአርት’ የተባለ ተቋም ገልጿል።
የሕንድን ከብሪታኒያን ቅኝ ግዛት ነጻ የመውጣት እንቅስቃሴ በሰላማዊ መንገድ የመሩት ጋንዲ፤ የአገሪቱ አባት ተብለውም ይጠራሉ። የአሁኑ ማስታወሻዎች ግን ግለሰቡ ከፖለቲካዊ መሪነታቸው ጀርባ ስለነበራቸው ግላዊ ማንነት ዕይታ የሚከፍቱ ናቸው።
ጋንዲ፣ ባለቤታቸው ቪድያን በሞት ላጡት ሂንጎራኒ በጻፉት ደብዳቤ የምሬት፣ ማጽናኛ እና የማበረታቻ መልዕክትን አስተላልፈዋል። እነዚህ መልዕክቶች በኋላ ላይ ‘A Thought for the Day’ በሚል ርዕስ በታተመው መጽሐፍ ውስጥ ተካትተዋል።
ከሳፍሮንአርት መሥራቾች አንዱ የሆኑት ዲነሽ ቫዚራኒ፣ እነዚህ የማስታወሻዎች ስብስብ ሰዎች ጋንዲን “በቅርብ እና በግላዊ ግንኙነት መነጽር” እንዲመለከቱ ማስቻሉን ይናገራሉ።
በቀረበው ጨረታ ላይ ደብዳቤዎች፣ በእጅ የተጻፉ ሰነዶች፣ ፎቶግራፎች እና የግል ዕቃዎች ተካትተዋል።
ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ የሚሆን ጊዜን የሚሸፍኑት እነዚህ ስብስቦች፣ የሕንድን የነጻነት ትግል ቁልፍ ጊዜያት እንዲሁም ጋንዲ ከሂንጎራኒ ጋር የነበራቸውን ወዳጅነት ያሳያሉ።