ዮሚፍ ቀጀልቻ የዓለም የወንዶች ግማሽ ማራቶን ክብረ ወሰንን በ29 ሰከንዶች አሻሻለ

ኢትዮጵያዊው ዮሚፍ ቀጀልቻ ዛሬ እሁድ በአርጀንቲና ዋና ከተማ ቦነስ አይረስ ውስጥ በተካሄደው የዓለም አትሌቲክስ የጎዳና ላይ ውድድር የዓለም የወንዶች የግማሽ ማራቶን ክብረ ወሰንን ሰበረ። ዮሚፍ አሁን ያሻሻለውን የግማሽ ማራቶን ክብረ ወሰንን ከሁለት ዓመት በፊት ስፔን ቫሌንሺያ ላይ በተደረገ ውድድር 57 ደቂቃ ከ30 ሰከንድ በሆነ ጊዜ በማሸነፍ ክብረ ወሰኑን ይዞት ነበር።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. ማህትማ ጋንዲ በእጅ የጻፏቸው ማስታወሻዎች በ1.9 ሚሊዮን ዶላር ተሸጡ

    በሕንድ የነጻነት ትግል መሪ ማሃትማ ጋንዲ በእጅ የተጻፉ ማስታወሻዎች በሙምባይ ከተማ በተካሄደ ጨረታ በ1.9 ሚሊዮን ዶላር ተሸጡ።

    የጋንዲ የቅርብ ሰው እና የነጻነት ታጋይ በነበሩት አናንድ ቲ ሂንጎራኒ ቤተሰቦች እጅ የነበሩት እነዚህ ማስታወሻዎች ከአውሮፓውያኑ 1944 እስከ 1946 ባለው ጊዜ ውስጥ የተጻፉ ናቸው።

    ከእውነት፣ ከአመጻ ውጪ ከመሆን እንዲሁም ራስን ከመግዛት ጋር የተያያዙ ሐሳቦች ማስታወሻዎቹ ላይ ሰፍረዋል።

    እነዚህን ማስታወሻዎች ለመግዛት የቀረበው የገንዘብ መጠን፣ ለአንድ የሕንድ ታሪካዊ ሰነድ የተሰጠ ከፍተኛው ዋጋ መሆኑን ጨረታውን ያዘጋጀው ‘ሳፍሮንአርት’ የተባለ ተቋም ገልጿል።

    የሕንድን ከብሪታኒያን ቅኝ ግዛት ነጻ የመውጣት እንቅስቃሴ በሰላማዊ መንገድ የመሩት ጋንዲ፤ የአገሪቱ አባት ተብለውም ይጠራሉ። የአሁኑ ማስታወሻዎች ግን ግለሰቡ ከፖለቲካዊ መሪነታቸው ጀርባ ስለነበራቸው ግላዊ ማንነት ዕይታ የሚከፍቱ ናቸው።

    ጋንዲ፣ ባለቤታቸው ቪድያን በሞት ላጡት ሂንጎራኒ በጻፉት ደብዳቤ የምሬት፣ ማጽናኛ እና የማበረታቻ መልዕክትን አስተላልፈዋል። እነዚህ መልዕክቶች በኋላ ላይ ‘A Thought for the Day’ በሚል ርዕስ በታተመው መጽሐፍ ውስጥ ተካትተዋል።

    ከሳፍሮንአርት መሥራቾች አንዱ የሆኑት ዲነሽ ቫዚራኒ፣ እነዚህ የማስታወሻዎች ስብስብ ሰዎች ጋንዲን “በቅርብ እና በግላዊ ግንኙነት መነጽር” እንዲመለከቱ ማስቻሉን ይናገራሉ።

    በቀረበው ጨረታ ላይ ደብዳቤዎች፣ በእጅ የተጻፉ ሰነዶች፣ ፎቶግራፎች እና የግል ዕቃዎች ተካትተዋል።

    ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ የሚሆን ጊዜን የሚሸፍኑት እነዚህ ስብስቦች፣ የሕንድን የነጻነት ትግል ቁልፍ ጊዜያት እንዲሁም ጋንዲ ከሂንጎራኒ ጋር የነበራቸውን ወዳጅነት ያሳያሉ።

  2. ዩኬ፣ ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ ጣልያን እና ካናዳ የእስራኤልን የዌስት ባንክ ሰፈራ ፕሮጀክት አወገዙ

    እስራኤል በወረራ በያዘችው ዌስት ባንክ ስትራቴጂያዊ አካል በሆነ ሥፍራ ላይ 1 ሺህ 200 ገደማ ቤቶችን ለመገንባት ያወጣችው ጨረታ ከዋና ዋና የምዕራባውያን አገራት ውግዘት ገጠመው።

    ዩናይትድ ኪንግደም፣ ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ ጣሊያን እና ካናዳ በጋራ ባወጡት መግለጫ፣ ውሳኔውን “ተቀባይነት የሌለው” በማለት የገለጹት ሲሆን እስራኤል ይህንን እቅዷን “በአፋጣኝ እንድታጥፍ” አሳስበዋል።

    በዓለም አቀፍ ሕግ መሠረት የእስራኤል ሰፈራዎች ሕገ ወጥ ናቸው። እስራኤል በዓለም አቀፍ ጫና ምክንያት በኢየሩሳሌም በስተምሥራቅ ሊገነባ የተያዘውን የ'ኢ1' ግንባታ ዕቅድን ለማዘግየት ተገድዳ ቆይታለች።

    ይህ ዕቅድ ዌስት ባንክን በመክፈል፣ የሁለት አገርነት ተስፋን የሚያቀጭጭ እንደሆነ የእስራኤል አጋሮች እና ፍልስጤማውያን ይናገራሉ።

    አውሮፓውያን አጋሮቹ እና ካናዳ ሐሙስ ዕለት ባወጡት መግለጫ ይህ ውሳኔ “ዌስት ባንክ ውስጥ ከፍተኛ አለመረጋጋት፣ ከዚህ ቀደም ባልታየ መጠን ሰፋሪዎች በንጹኃን ላይ ጥቃት እየፈጸሙ ባለበት እንዲሁም በፍልስጤማውያን ኢኮኖሚ ላይ ከፍተኛ ገደቦች በተደረጉበት በዚህ ወቅት፤ መተላለፉ ጉዳዩን ይበልጥ አሳሳቢ ያደርገዋል” ብለዋል።

    ይህ እቅድ አካባቢውን “ከሰላም ከማራቅ ባሻገር እስራኤል ያላትን ዓለም አቀፍ ቁመና ይበልጥ እንደሚሸረሽረው” ገልጸዋል።

    የተባበሩት መንግሥታት ዋና ጸሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ባወጡት ሌላ መግለጫ፣ ይህ የኢ1 ዕቅድ ፍልስጤም ላይ “የሕልውና ስጋት” መጋረጡን አንስተዋል። ቤልጂየምም ተመሳሳይ ሀሳብ አንጸባርቃለች።

  3. አሜሪካ የኢራንን ኢኮኖሚ “የሚያደቅቁ” እና አገዛዙን “የሚያፈርሱ” ማዕቀቦችን እንደምትጥል አስታወቀች

    የአሜሪካ ግምጃ ቤት ኃላፊ ስኮት ቤሰንት የዋሽንግተን አጋር የሆኑ አገራት የኢራንን ኢኮኖሚ “ለማድቀቅ” የሚደረገውን ጥረት እንዲደግፉ ጥሪ አቀረቡ።

    ቤንሰንት፤ “ይሄንን አገዛዝ እናፈርሰዋለን። አጋሮቻችን እና ቀሪው ዓለም ውሳኔ የሚሰጡበት ጊዜ አሁን ነው” ሲሉ ሲኤንቢሲ ለተባለው የአሜሪካ ቴሌቪዥን ጣቢያ ተናግረዋል። “ከእኛ ጋር አልያም ከእኛ ተቃራኒ ናችሁ” ሲሉም ተደምጠዋል።

    የግምጃ ቤት ኃላፊው ይህንን ያሉት፣ የአገሪቱ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለኢራን “የትኛውንም የሕይወት ድጋፍ” የሚያቀርቡ አገራት ላይ “እጅግ ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ መዘዝ” የሚያስከትል እርምጃ እንደሚወሰድ ከተናገሩ በኋላ ነው።

    ቤንሰንት፣ የትራምፕ አስተዳደር ምን አይነት እርምጃዎችን ሊወስድ እያሰበ እንደሆነ አልገለጹም። ነገር ግን የኢራን ኢኮኖሚ ላይ ሊተገበር የታቀደው የጫና ዘመቻ፣ “በከፍተኛ ደረጃ በድጋሚ" ግጭት "የማስጀመር" አስፈላጊነትን እንደሚቀንሰው ተናግረዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን በየካቲት ኢራን ላይ ጥቃት የከፈቱት፣ ይህ አይነቱ እርምጃ ቴህራን የኒውክሌር መሣሪያ እንዳትሰራ እንደሚያደርጋት በመግለጽ ነበር። ኢራን ግን የኒውክሌር መሣሪያ የማልማት እቅድ እንደሌላት በተደጋጋሚ አስታውቃለች።

    ኢራን በእስራኤል፣ በመካከለኛው ምሥራቅ በሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሠፈሮች እንዲሁም የአሜሪካ አገራት በሆኑ የባሕረ ሰላጤው አገራት ላይ ጥቃት በመክፈት ምላሽ ሰጥታለች።

    ከዓለም ነዳጅ እና ፈሳሽ የተፈጥሮ ጋዝ ምርት 20 በመቶው የሚተላለፍበትን ሆርሙዝ ወሽመጥን መዝጋቷም በዓለም ገበያ ላይ መናጋትን አስከትሏል።

    አሜሪካ እና ኢራን ጦርነቱን ለመቋጨት የሚያስችል ድርድር እንዲደረግ በሚል ሚያዝያ እና ሰኔ ላይ ተኩስ አቁም ቢያደርጉም ጥረቱ ፍሬ አላፈራም። ተኩስ አቁሞቹ በተደጋጋሚ የተጣሱ ሲሆን ንግግሮችም ባሉበት ቆመዋል።

    አሁን ላይ ፕሬዝዳንት ትራምፕ ወደ ጦርነት ከመመለስ ይልቅ፣ “እስካሁን የትኛውም አገር ላይ ከተወሰዱት በበለጠ አድቃቂ የሆኑ የኢኮኖሚ እርምጃዎችን” ለመውሰድ እየተዘጋጁ ይመስላል።

    የግምጃ ቤት ኃላፊው ቤንሰንት፣ አዲሶቹ የቅጣት እቅዶች “በዓለም ታሪክ ውስጥ ትልቁ የተቀናጀ ኢኮኖሚያዊ የማግለል” እርምጃ አካል እንደሚሆኑ ተናግረዋል።

    “ከእነርሱ ጋር ንግድ መፈጸም፣ ገንዘብ ማዘዋወር፣ ነዳጃቸውን መግዛት ከቀጠላችሁ... የአሜሪካ ግምጃ ቤት እና የአሜሪካ መንግሥት ሙሉ ኃይል ጉልበታቸውን እናንተ ላይ እርምጃ ለመውሰድ ይጠቀማሉ” ሲሉ የዋሽንግተንን ዓለም አቀፍ የንግድ አጋሮች አስጠንቅቀዋል።

  4. የአሜሪካው ግዙፍ አውሮፕላን ተሸካሚ መርከብ 'ጆርጅ ዋሽንግተን' መካከለኛው ምሥራቅ ደረሰ

    አብርሃም ሊንከንን እንደሚተካ የሚጠበቀው ዩኤስኤስ ጆርጅ ዋሽንግተን የተሰኘው ግዙፍ አውሮፕላን ተሸካሚ መርከብ ረቡዕ ዕለት መካከለኛው ምሥራቅ መድረሱን የአሜሪካ ጦር ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንቲኮም) አስታወቀ።

    ሴንቲኮም በማኅበራዊ ሚዲያ ገጹ ላይ “ጆርጅ ዋሽንግተን እና ሌሎች ጥቃት ፈጻሚ መርከቦች ትናንት ወደ ሴንቲኮም ማዘዣ ከደረሱ በኋላ በመካከለኛው ምሥራቅ በተያዘለትጊዜ ውስጥ እንቅስቃሴውን ጀምሯል” ሲል አስታውቋል።

    ሴንቴኮም የአውሮፕላን ተሸካሚ መርከቡ በአረቢያ ባህር ላይ ሲያቋርጥ የሚያሳይ ፎቶ አጋርቷል።

    መርከቦቹ ቦታ የተቀያየሩት አብርሃም ሊንከን የተሰኘው መርከብ ከኢራን ጦርነት ጋር በተያያዘ ረዘም ላለ ጊዜ በአካባቢው በመቆየቱ የባህር ኃይል አባላቱ ከፍተኛ የአእምሮ ጤና እና የአቅርቦት ችግሮች ካጋጠማቸው በኋላ ነው።

    የዴሞክራቲክ ሴናተር ሪቻርድ ብሉሜንታል ለመከላከያ ሚኒስትር ፒት ሄግሴዝ እና ለዋናው የባህር ኃይል አዛዥ ሁንግ ካኦ የጦር መርከበኞቹን እና ወታደሮቹን በአካባቢው ለረዥም ማቆየት ያስፈለገበትን ምክንያት በሚመለከት ማብራሪያ እንዲሰጡ በደብዳቤ ጠይቀዋል።

    ብሉመንታል የአቅርቦት እጥረት፣ የውሃ ብክለት፣ የቧንቧ ችግሮች፣ የአእምሮ ጤና፣ የደህንነት ስጋቶች እና ከወዳጅ ዘመድ የሚላኩ ጥቅሎች በጉዞ ውስጥ በመዘግየታቸው ዋና ዋና የፖስታ መልዕክቶች መስተጓጎል እንደገጠማቸው ዘርዝረዋል።

    የአሜሪካ ባለሥልጣናት ግን ሪፖርቶቹን ተጋንነዋል በማለት በአውሮፕላን ተሸካሚው ላይ አለ ተብሎ የቀረቡትን የአስተዳደር እና የአቅርቦት ችግሮች ውድቅ አድርገዋል።

    ጆርጅ ዋሽንግተን በጃፓን ዮኮሱካ ውስጥ የነበረ የአሜሪካ የባህር ኃይል ብቸኛ የአውሮፕላን ተሸካሚ መርከብ ሲሆን አብርሃም ሊንከንን ለመተካት ወደ መካከለኛው ምሥራቅ እንዲጓዝ ተደርጓል።

  5. የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የትራምፕ “የኢኮኖሚ ጦርነት” አሜሪካ ላይ ተጨማሪ ሽንፈት ያስከትላል አሉ

    የኢራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ሐሙስ ዕለት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በቴህራን ላይ ይፋ ያደረጉት “ኢኮኖሚ ጦርነት” ዘመቻ ዋሽንግተን ላይ “ተጨማሪ ሽንፈት” የሚያስከትል ነው አሉ።

    አራግቺ በኤክስ ገጻቸው ላይ ” ‘የኢኮኖሚ ጦርነት’ የሚባለው ከአሜሪካ ቀውስ ትኩረትን ለማስቀየር” የተወሰደ እንደሆነ በመግለፅ የአገሪቱ ብሔራዊ ዕዳ 40 ትሪሊዮን ዶላር መድረሱን ከቀውሶቹ አንዱ አድርገው ጠቅሰዋል።

    “ያልተሳኩ ፖሊሲዎችን አቅልሎ መመለከት የበለጠ ሽንፈትን እና የኢራናውያንን ጠላትነት ያመጣል” ያሉት አራግቺ፣ የአሜሪካ “ኢኮኖሚያዊ ሽብርተኝነት” በዓለም አቀፍ ደረጃ ያለውን ምጣኔ ሃብት እና ሉዓላዊነት አደጋ ላይ እንደሚጥል ተናግረዋል።

    የኢራን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ካዜም ጋሪባባዲ በኤክስ ገጻቸው ላይ ዋሽንግተን ወታደራዊ ዓላማዎቿን ማሳካት ባለመቻሏ ወደ “ኢኮኖሚ ጦርነት” ፊቷን አዙራለች ብለዋል።

    “ኢራን ልትሸነፍ መቃረቧን፣ ከውድቀት አፋፍ ላይ መሆኗን ይናገራሉ፤ ነገር ግን አጋሮቻቸው እንዲረዷቸው እየተማጸኑ ነው” ሲሉ ጋሪባባዲ ተናግረዋል።

    “ችግሩ የእነሱ የተሳሳተ ስሌት ነው። ለመሸፋፈን በሞከሩ ቁጥር፣ ለራሳቸው የበለጠ ውድቀት ይፈጥራሉ” ሲል አክለዋል።

    “መከላከያው የጦርነቱን ዓላማዎች ማሳካት አልቻለም፤ እናም አሁን የሚቀጥለውን ውድቀታቸውን ‘ኢኮኖሚያዊ ጦርነት’ ብለው ሰየሙት።”

    የአገሪቱ ከፍተኛ ባለሥልጣናት ይህንን ያሉት ትራምፕ ረቡዕ ዕለት “እስካሁን የትኛውም አገር ላይ ከተወሰደው የምጣኔ ሃብት ጫናዎች በበለጠ አድቃቂ የሆኑ የኢኮኖሚ እርምጃዎች” እንደሚወሰዱ ተናግረዋል።

    ትራምፕ ይህንን ያሉት ለ60 ቀናት ተደርሶ የነበረው የተኩስ አቁም ስምምነት ሰኞ ዕለት ከተጠናቀቀ በኋላ ነው።

    ትራምፕ ረቡዕ ምሽት ባጋሩት የማኅበራዊ ሚዲያ ልጥፍ፣ ይህንን ኢኮኖሚያዊ እርምጃ የሚወስዱት የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ከአሜሪካ ጋር ስምምነት ላይ መድረስ ስላልቻለ መሆኑን ገልጸዋል።

  6. በኤደን ባሕረ ሰላጤ ላይ የምትጓዝ መርከብን ታጣቂዎች አግተው ወደ ሶማሊያ አቅጣጫ መውሰዳቸው ተገለጸ

    የዩናይትድ ኪንግደም ባሕር ትራንስፖርት ደህንነት ኤጀንሲ በኤደን ባሕረ ሰላጤ ላይ እየተጓዘች የነበረች ነዳጅ ጫኝ መርከብ መታገቷን ገለጸ።

    ኤጀንሲው በኤደን ባሕረ ሰላጤ ላይ እየተጓዘች የነበረች ነዳጅ ጫኝ መርከብ ስድስት የታጠቁ ሰዎች አስገድደው ወደ ሶማሊያ አቅራቢያ መውሰዳቸውን አስታውቋል።

    ኤጀንሲው በኤክስ ገጹ ላይ ባወጣው መግለጫ “መርከቧ ላይ ስድስት የታጠቁሰዎች ተሳፍረው ወደ ሶማሊያ እየወሰዷት መሆኑን ማረጋገጫ ደርሶናል” ብሏል።

    ኤጀንሲውአክሎም ባለሥልጣናት ክስተቱንእየመረመሩ መሆኑን ገልጾ አካባቢውን የሚያቋርጡ መርከቦች ጥንቃቄ እንዲያደርጉ እና አጠራጣሪ እንቅስቃሴዎችን ሪፖርት እንዲያደርጉ አሳስቧል።

    መርከቧንያገቱት ቡድኖች እነማን አንደሆነ እስካሁን ድረስ የታወቀ ነገር የለም።

    የየመንሁቲ ቡድን በሐምሌ ወር ከሳዑዲ አረቢያጋር በተያያዙ መርከቦች ላይ እገዳ እንደሚጥል ካወጀ በኋላ የቀጣናው የባህር መስመሮች፣ በተለይም ቀይ ባህር እና የኤደን ባሕረ ሰላጤ፣ ከፍተኛ ውጥረት ገጥሟቸዋል።

    ሳዑዲአረቢያ በኋላ በባብ አል-ማንዳብ ወሽመጥ ውስጥ የመርከብእንቅስቃሴ ነጻነትን ለመጠበቅ በሚል የባህር ኃይል ጥምረት መመስረቷን አስታውቃለች። ጥምረቱ አሜሪካን፣ የመን፣ ኩዌትን፣ ኦማንን፣ ዮርዳኖስን፣ ሱዳንን፣ ሞሮኮን፣ ማልዲቭስን፣ ባንግላዲሽ እና ኒውዚላንድን ያካትታል።

    እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር ከ2015 ጀምሮ ሳዑዲ አረቢያ ዓለም አቀፍ እውቅና ያለው የየመን መንግሥት የሚደግፍጥምረት ስትመራ ቆይታለች።

    ኢራን ደግሞ ከ2014 ጀምሮ ዋና ከተማዋን ሰነዓን ጨምሮ በርካታ የአገሪቱን ከተሞችን የተቆጣጠሩትን ሁቲዎችን በመደገፍ ትከሰሳለች።

    እአአ ከ2008 እስከ 2018 ድረስ በሶማሊያ የባህር ዳርቻ የባህር ላይ ውንብድና በስፋት ተስተውሎ ነበር። በ2023 መጨረሻ አካባቢ በቀጣናው የጸጥታ ውጥረት ሲሰፉ የባሕር ላይ ውንብድና እንደገና ጀምሯል።

    አንዳንድየመከላከያ ጉዳዮችን የሚተነትኑ ባለሙያዎች የየመን የሁቲ ታጣቂዎች በቀይ ባሕር ላይ የሚደረገውን የባህር ላይ ትራንስፖርት ለማስተጓጎል ከባህር ላይ ዘራፊዎች ጋር እየተባበሩ ሊሆን እንደሚችል ይጠራጠራሉ።

    ኢራን፣አሜሪካ በሆርሙዝ የባህር ወሽመጥ ላይ በጣለችው የባህር ላይ እገዳ ምላሽ ለመስጠት እንዲህ ዓይነት እርምጃ እንደምትወስድ አስጠንቅቃ ነበር።

  7. ሩሲያ በዩክሬን ባደረሰችው ጥቃት ቢያንስ 13 ሰዎች ተገደሉ

    ሩሲያ በዩክሬን መዲና ኪቭ ላይ ባደረሰችው ጥቃት ቢያንስ 13 ሰዎች ተገደሉ።

    የዩክሬን ጠቅላይ ሚኒስትር እንደተናገሩት ተጨማሪ 40 ሰዎች ጉዳት ደርሶባቸዋል።

    የዩክሬን መዲና የአየር መቃወሚያ ሚሳዔል እጥረት እንደገጠማትም ገልጸዋል።

    የአገሪቱ የድንገተኛ ጊዜ መሥሪያ ቤት እንዳለው፤ ትናንት ምሽት በመኖሪያ ሕንጻዎች እንዲሁም መጋዘን ላይ ጥቃቶች ተፈጽመዋል። በተጨማሪም የሕጻናት ሆስፒታል እና ትምህርት ቤቶች ተጎድተዋል።

    የዩክሬን ፕሬዝዳንት ቮሎድሚር ዜሌንስኪ እንደተናገሩት ከሆነ ሰዎች የተገደሉት የአየር መቃወሚያ ሚሳዔል እጥረት በመከሰቱ ነው።

    ዩክሬን የአየር መቃወሚያ ሚሳዔል የምታገኘው ከምዕራባውያን አገራት ነው።

    የቪቭ ከንቲባ ቪታሊ ክሊትሽኮ “የአየር መቃወሚያ ሚሳዔል እና የተተኳሾች ድጋፍ እንፈልጋለን” ሲሉ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

    የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች ከሕንጻ ፍርስራሾች ሥር በሕይወት የተረፉ ሰዎችን ለማግኘት እየሞከሩ ነው።

  8. ኢራን በቀጣይ ጦርነት የሚከፈት ከሆነ “የበለጠ አውዳሚ መሣሪያ” እንደምትጠቀም አስጠነቀቀች

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ፣ አገሪቱ ላይ ማንኛውም አይነት አዲስ ጦርነት የሚከፈት ከሆነ፣ ከዚህ ቀደም ጥቅም ላይ ከዋሉት “ይበልጥ ዘመናዊ እና አውዳሚ መሣሪያዎች” እንደሚጠቀም አስጠነቀቀ።

    የአብዮታዊ ዘቡ ቃል አቀባይ ብርጋዴር ጄነራል ሆሴን ሞሄቢ፣ ሌላ ጦርነት የሚቀሰቀስ ከሆነ የኢራን መሣሪያ “በእርግጠኝነት ከዚህ ቀደም ከነበረው የተለየ ይሆናል” ማለታቸውን ታስኒም የዜና ወኪል ዘግቧል።

    ጥቅም ላይ የሚውሉት “ተተኮሾች ዘመናዊነት፣ ዒላማን የመምታት ትክክለኛነት፣ ሜሳዔል የሚወነጨፍበት ርቀት እንዲሁም ሌሎች ወታደራዊ አቅሞች ላይ” ለውጥ ሊኖር እንደሚችል ጠቁመዋል።

    ኢራን ወታደራዊ አቅሟን ለማሳደግ እንዲሁም ዒላማን የመምታት ትክክለኛነታቸው የጨመረ፣ አውዳሚ ኃይል እና የቴክኖሎጂ ውስብስብነት ያላቸው መሣሪያዎችን ለመስራት የምታደርገውን ጥረት እንደቀጠለች ቃል አቀባዩ ገልጸዋል።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ይህንን ያለው ሰኔ ላይ የተፈረመው እና በሳምንታት ጊዜ ውስጥ የተጣሰው የሁለት ወራት ተኩስ አቁም ሰኞ ዕለት ከተጠናቀቀ በኋላ ነው። ሁለቱ አገራት ጀምረው የነበረው ድርድር ባለበት እንደቆመ ነው።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ለኢራን እገዛ በሚያደርግ ወይም ከአገሪቱ ጋር ግንኙነት የሚኖረው ማንኛውም አገር ላይ “እጅግ ግዙፍ ኢኮኖሚያዊ መዘዝ” የሚያመጣ እርምጃ እንደሚወስዱ አስጠንቅቀዋል።

    የኢራን ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ይህ የትራምፕ እርምጃ፣ ”ከአሜሪካ ቀውስ ትኩረትን ለማስቀየር” የተወሰደ እንደሆነ በመግለፅ አጣጥለዋል። የአሜሪካ ብሔራዊ ዕዳ 40 ትሪሊዮን ዶላር መድረሱን ከቀውሶቹ አንዱ አድርገው ጠቅሰዋል።

    ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ካዜም ጋሪባባዲ በበኩላቸው፣ አሜሪካ “የኢኮኖሚ ጦርነት” የከፈተችው “ወታደራዊ ጦርነት ስላልሰራላት ነው” በማለት እርምጃቸውን ተችተዋል።

  9. ትራምፕ ኢራንን የሚረዳ ማንኛውም አገር ላይ “ግዙፍ ኢኮኖሚያዊ መዘዝ” የሚያስከትል እርምጃ እንደሚወስዱ ዛቱ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አሜሪካ ለኢራን እገዛ በሚያደርግ ወይም ከአገሪቱ ጋር ግንኙነት የሚኖረው ማንኛውም አገር ላይ “እጅግ ግዙፍ ኢኮኖሚያዊ መዘዝ” የሚያመጣ እርምጃ እንደምስወስድ አስጠነቀቁ።

    ፕሬዝዳንቱ በትሩዝ ሶሻል የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ባሰፈሩት በዚህ ማስጠንቀቂያ ላይ ተጨማሪ ዝርዝር አልሰጡም፤ የትኛውንም አገርም በስም አልጠቀሱም።

    ነገር ግን “እስካሁን የትኛውም አገር ላይ ከተወሰዱት በበለጠ አድቃቂ የሆኑ የኢኮኖሚ እርምጃዎች” እንደሚወሰዱ ተናግረዋል።

    ትራምፕ ይህንን ያሉት ለ60 ቀናት ተደርሶ የነበረው የተኩስ አቁም ስምምነት ሰኞ ዕለት ከተጠናቀቀ በኋላ ነው። አሜሪካ እና እስራኤል በየካቲት ወር የጀመሩት ጦርነት ሊቋጭ እንደሚሆነ የሚያመለክት ዲፕሎማሲያዊም ሆነ ወታደራዊ እንቅስቃሴ አልታየም።

    የአሁኑ የትራምፕ እርምጃ ከቴህራን ጋር የንግድ ግንኙነት ባላቸው የውጭ ባንኮች እና ኩባንያዎች ላይ ማዕቀብ እንዲጣል ያደረገው ‘ኦፕሬሽን ኢኮኖሚክ ፊዩሪ’ ዘመቻ አካል ይመስላል።

    ትራምፕ ረቡዕ ምሽት ባጋሩት የማኅበራዊ ሚዲያ ልጥፍ፣ ይህንን ኢኮኖሚያዊ እርምጃ የሚወስዱት የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ከአሜሪካ ጋር ስምምነት ላይ መድረስ ስላልቻለ መሆኑን ገልጸዋል።

    “የፋይናንስ ተቋማቱ፣ ንግዶቹ፣ አየር ማረፊያዎቹ ወይም የመንግሥት ተቋማቱ ለኢራን የትኛውንም አይነት የሕይወት መስመር እንዲሰጡ የሚፈቅድ ማንኛውም አገር ራሱ እጅግ ግዙፍ ኢኮኖሚያዊ መዘዝ ይገጥመዋል” ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

    እነዚህ አገራት ምን አይነት ቅጣት እንደሚጠብቃቸው ግን በግልጽ አልጠቀሱም።

    ትራምፕ ቀጥለውም፣ “የነዳጅ ዝውውር፣ የገንዘብ ልውውጥ መስመሮች፣ የገንዘብ ዝውውሮች፣ የምንዛሬ ተቋማት፣ መርከብ መዝጋቢዎች… ሁሉም አሁን መቆም አለበት። ማን እንደሆናችሁ ታውቃላችሁ” ብለዋል።

    ይህ ማስጠንቀቂያ የተሰጠው፣ የአሜሪካ ወዳጅ የሆነችው የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ከኢራን የተሰነዘረባትን የሚሳዔል ዛቻ ተከተሎ ከአገሪቱ ጋር ያላትን የፋይናንስ እና የኢኮኖሚ ግንኙነት በሙሉ እንደምታቋርጥ ባስታወቀች ማግሥት ነው።

    የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች መከላከያ ሚኒስቴር ኢራን የመርከቦችን ዒላማ በማድረግ ሁለት ባለስቲክ ሚሳዔሎችን ማስወንጨፏን ገልጾ ነበር። ሁለቱም ሚሳዔሎች ባሕር ላይ ወድቀዋል።

    የኢራን ተቋማት ለረጅም ጊዜያት ገንዘብ ለማዘዋወር ሲጠቀሙ የቆዩት፣ በዱባይ የፋይናንስ ሥርዓት ውስጥ የሚገኙ የምንዛሬ ተቋማት እና መዝገብ ላይ ብቻ ያሉ ኩባንያዎችን ነው።

  10. ኢራን በአውሮፓ የሚገኙ የአሜሪካ ዒላማዎችን እመታለሁ በማለቷ ኔቶ ምላሽ ሰጠ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ መልሰው ከኢራን ጋር ጦርነት የሚገቡ ከሆነ ኢራን፣ አውሮፓ ውስጥ የሚገኙ የአሜሪካ ወታደራዊ ተቋማትን እንደምትመታ መዘገቡን ተከትሎ ኔቶ ምላሽ ሰጠ።

    ጋብ ያለው ጦርነት ከተባባሰ ኢራን በአውሮፓ ውስጥ ያሉ የአሜሪካ ወታደራዊ ዒላማዎችን ልትመታ እንደምትችል ፋይናንሻል ታይምስ የተባለው ጋዜጣ ዘግቧል።

    አሜሪካ ዋነኛ አባል የሆነችበት የሰሜን አትላንቲክ ጦር ቃልኪዳን አገራት ማኅበር (ኔቶ) አንድ ባለሥልጣን ለዚህ ዛቻ በሰጡት ምላሽ፣ ድርጅቱ የትኛውንም ስጋት ለመጋፈጥ ዝግጁ መሆኑን ገልጸዋል። ሁሉንም አጋሮቹን ለመከላከል አስፈላጊውን እርምጃ ይወስዳል ብለዋል።

    ስማቸው ያልተጠቀሰው የኔቶ ባለሥልጣን "የኔቶ የአየር መከላያ ሥርዓት ከዚህ ቀደም ኢራን በተለያዩ ጊዜያት ወደ ቱርክ ሚሳዔሎችን ባስወነጨፈችበት ጊዜ በተሳካ ሁኔታ ጥቃቱን መከላከሉን" አስታውሰው፤ "ጥቃቶችን የማስቀረት እና የመከላከል አቋማችን ጠንካራ እና ውጤታማ ነው” ብለዋል።

    ፋይናንሻል ታይምስ ጋዜጣ ለኢራን መንግሥት ቅርብ የሆኑ ምንጮችን ጠቅሶ እንደዘገበው ትራምፕ ጦርነቱን የሚቀጥሉ ከሆነ “ኢራን በጦርነቱ የሚፈጠረውን ጫና ከፍ ለማድረግ የሚያስችሉ አማራጮችን እየፈተሸች” እና በአውሮፓ ያሉ የአሜሪካ ወታደራዊ ተቋማትን ዒላማ ለማድረግ እያጤነች ነው።

    የኢራን ኃይሎች ባለፈው ወር የአሜሪካ አውሮፕላኖች ከአየር ኃይል ሰፈራቸው ነዳጅ እንዲሞሉ ፈቃድ እንደሰጠችው ቤልጂየም ባሉ የደቡባዊ የአውሮፓ አገራት የሚገኙ የአሜሪካ ወደታራዊ ተቋማትን እየገመገሙ መሆኑን የጋዜጣው ምንጮች ገልጸዋል።

  11. የእስራኤል ጦር በአምስት ዓመቷ ፍልስጤማዊት ግድያ ላይ የወንጀል ምርመራ እንዲካሄድ አዘዘ

    የእስራኤል ጦር ዓለም አቀፍ ውግዘትን ባስከተለው፣ ጋዛ ውስጥ በአምስት ዓመቷ ሂንዳ ራጃብ ላይ የተፈጸመ ግድያ ላይ የወንጀል ምርመራ እንዲካሄድ አዘዘ።

    የፍልስጤማዊቷ ሕጻን ግድያ ትኩረትን ያገኘው ከሁለት ዓመት በፊት ከስድስት የቤተሰብ አባላት ጋር እየተጓዙ ሳለ በመኪናቸው ላይ በእስራኤል ወታደሮች ተኩስ ከተከፈተባቸው በኋላ ለአደጋ ጊዜ ሠራተኞች እየቃተተች ስትናገር የተቀረጸው ቪዲዮ ከተሠራጨ በኋላ ነው።

    ሕጻኗ በርካታ የቤተሰቧ አባላት ከተገደሉበት ጥቃቱ ተርፋ የነበረ ቢሆንም፣ ኋላ ላይ ግን ከዘመዶቿ እና እርዳታ ሊሰጡ በአምቡላንስ ከመጡ ሁለት ሐኪሞች ጋር አስከሬኗ ተገኝቷል።

    የእስራኤል ጦር ባወጣው መግለጫ፣ በመረጃዎች ላይ ምርመራ መደረጉን ጠቅሷል። ይህንን ተከትሎም “የጦር ሠራዊቱ የወንጀል ምርመራ ክፍል በክስተቱ ላይ የወንጀል ምርመራ እንዲያደርግ ተወስኗል” ብሏል።

    የእስራኤል ጦር ሂንድ እና ቤተሰቦቿ ይጓዙበት በነበረው ተሽከርካሪ ላይ ተኩስ መከፈቱን ሲያምን ለመጀመሪያ ጊዜ ነው። ከዚህ ቀደም የእስራኤል ሠራዊት አደርኩት ባለው ምርመራ አንድም ወታደሩ ጥቃቱ በተፈጸመበት ስፍራ ላይ እንዳልነበረ ተናግሮ ነበር።

    ሕጻኗ ሂንድ ራጃብ እና ቤተሰቦቿ ተኩስ የተከፈተባቸው፣ ከጋዛ ጦርነት የቦምብ ድብደባ ለመሸሽ እየተጓዙ በነበረበት ወቅት ነው።

    በጥቃቱ በርካታ የቤተሰቧ አባላት ሲገደሉ፣ ሂንድ ከፍልስጤም ቀይ ጨረቃ ማኅበር ለተደረገላቸው ጥሪ ምላሽ ሰጥታ ነበር። በስልክ ለሚያናግራት ሰው እንዲያድናት ስትለምን የሚሰማው ድምጿ ከባድ ተኩስ ተሰምቶ ተቋርጧል።

    የሕጻኗን ሕይወት ለማትረፍ የሞከረው አምቡላንስም በከባድ መሳሪያ ተመትቶ የሂንድ፣ የቤተሰቦቿ እና የአምቡላንሱ ሠራተኞች አስከሬን በኋላ ላይ ተገኝቷል።

  12. ላይቤሪያ አሜሪካ የምታባርራቸውን 1,200 የውጭ አገር ዜጎች ለመቀበል ተስማማች

    ላይቤሪያ፣ አሜሪካ በሚቀጥለው አንድ ዓመት ውስጥ ከግዛቷ ከምታስወጣቸው የውጭ ዜጎች ውስጥ እስከ 1,200 ያህሉን ለመቀበል ተስማማች።

    ሕገ ወጥ ባላቸው ስደተኞች ላይ የሚወስደውን እርምጃ አጠናክሮ የቀጠለው የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተደዳር፣ ከላይቤሪያ ጋር የደረሰው ስምምነት እስካሁን ከፈጸማቸው ትልቅ ስምምነቶች አንዱ ነው።

    ከዚህ ቀደም በተፈጸሙ ተመሳሳይ ስምምነቶች ሦስተኛ አገራት ሲቀበሉ የነበሩት፣ ወደራሳቸው አገር እንዳይባረሩ የሚከለክል ሕጋዊ ከለላ ያላቸውን ስደተኞች ነው። ወደ ላይቤሪያ የሚላኩት ስደተኞች ተመሳሳይ ሕጋዊ ጥበቃ ያላቸው ይሆኑ እንደሆን አልታወቀም።

    የአገሪቱ የማስታወቂያ ሚኒስትር ጄሮሊንሜክ ፒያህ፣ “ወደ ላይቤሪያ የሚመጡትን ሰዎች የምንቀበላቸው እንደ እንግዳ እንደሆነ መንግሥት አጽንኦት መስጠት ይፈልጋል” ብለዋል።

    የዚህ ስምምነት አካል የሆነው 20 ሰዎችን የያዘ የመጀመሪያ ቡድን ነገ ሐሙስ ወደ አገሪቱ እንደሚገባ የገለጹት ሚኒስትሩ፣ ስደተኞቹ ላይቤሪያ ከደረሱ በኋላ ወደፈለጉት ቦታ መሄድ ወይም የጥገኝነት ጥያቄ ማቅረብ እንደሚችሉ ተናግረዋል።

    እንደ ፒያህ ገለጻ፣ ከአሜሪካ ከተባረሩት ሰዎች መካከል ወንጀለኞች አልያም በአሜሪካ ወይም በላይቤሪያ ክስ የተመሠረተባቸው ሰዎች የሉም።

    ስደተኞቹን የምንቀበላቸው “ላይቤሪያ ከስደት፣ ከጦርነት እንዲሁም ከሌሎች ዓይነት ግጭቶች ጥበቃ እና ከለላ ለሚሹ ሁሉ መጠጊያ በማቅረብ ረገድ ባላት የረጅም ጊዜ ልምድ መሠረት ነው” ብለዋል።

    ወደ ላይቤሪያ የሚመጡት ሰዎችን ዜግነት የተመለከተ መረጃ አልተሰጠም።

    ባለፈው ዓመት ጥር ላይ ወደ ሥልጣን የመጣው የፕሬዝዳንት ትራምፕ አስተዳደር ፣ በርካታ ሰዎችን ወደ “ሦስተኛ አገራት” አባርሯል።

    እንደ ጋና፣ ኢኳቶሪያል ጊኒ፣ ኢስዋቲኒ፣ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ እና ሴራሊዮን ያሉ በርካታ የአፍሪካ አገራት አሜሪካ በሕጋዊ ከለላ ምክንያት ወደ አገራቸው ልታባርራቸው የማትችላቸውን ሰዎች ለመቀበል ስምምነት ፈርመዋል።

    አሜሪካ ግለሰቦቹን ወደ ሦስተኛ አገር ለመላክ የሚደረሱት ስምምነቶች ሕጋዊ ናቸው የሚል አቋም አላት።

    የመብት ተሟጋች ቡድኖች ግን ስምምነቶቹ ግልጽነት የጎደላቸው እንደሆኑ እንዲሁም ስደተኞቹ ሦስተኛው ተቀባይ አገር ጋር ከደረሱ በኋላ ወደ አገራቸው እንዲመለሱ እንደሚደረጉ በመግለጽ ተችተዋል።

  13. ዩኤኢ ከኢራን ጋር ያላትን የንግድ ግንኙነት ማቆሟን አስታወቀች

    የተባበሩት አረብ ኤሚሬትስ፣ ከኢራን ጋር ያላትን ሁሉንም የንግድ እንቅስቃሴዎች፣ የንግድ ልውውጦች እና የገንዘብ ዝውውሮች ሌላ መግለጫ እስኪሰጥ ድረስ አገደች።

    አገሪቱ ይህን እርምጃ የወሰደችው፣ ሁለት ከኢራን የተተኮሱ ባሌስቲክ ሚሳዔሎች የገልፍ የባሕር ላይ ትራፊክን ዒላማ ማድረጋቸውን ካሳወቀች በኋላ ነው።

    ረቡዕ ዕለት በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ይፋ የሆነው ይህ ውሳኔ፣ በቀጣናው እየተስፋፋ ያለው ወታደራዊ ግጭት በኢራን እና በባሕረ ሰላጤው ጎረቤቶቿ መካከል ባለው የኢኮኖሚ ግንኙነት ላይ እየተንፀባረቀ ስለመሆኑ የቅርብ ጊዜ ማሳያ ነው።

    ይህ እገዳ በቀጣናዊ እና ዓለም አቀፍ ሰላም እና ጸጥታ ላይ ተፅእኖ ያሳደሩ ለውጦችን ተከትሎ የተወሰነ መሆኑን አቡ ዳኢ አስታውቃለች።

    ከኢራን ተተኮሱ ከተባሉት ሁለት ሚሳዔሎች ውስጥ አንዱ በኢሚሬትስ ክልል ውስጥ ባለ የውሃ አካል ላይ የወደቀ ሲሆን ሌላው ደግሞ ከውሃ ክልሏ ውጭ ባለ ውሃ ላእ መውደቁን ሚኒስቴሩ ገልጿል። ምንም እንኳን ሚሳዔሎቹ መርከብ ባይመቱም፣ በባሕር ትራፊክ ላይ ያነጣጠሩ ናቸው ተብሎ ተገምግሟል።

    ኢራን በተባበሩት አረብ ኤሚሬትስ የቀረበባትን ክስ አስተባብላለች። የአገሪቱ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኢስማኤል ባጋይ፣ ክሱን “መሠረተ ቢስ” ነው ብለዋል። ከ“መልካም ጉርብትና” ጋር የሚቃረኑ መሆናቸውንም የገለፁት ቃል አቀባዩ፣ የቀጣናው አገራት በቴህራን ላይ ከሚሰነዘሩ “መሠረተ ቢስ” ክሶች እንዲቆጠቡ አሳስበዋል።

    ክስተቱ “በሀሰተኛ ባንዲራ” የሚደረግ እንቅስቃሴ ሊሆን እንደሚችል በመጥቀስ፣ የቀጣናውን ፀጥታ ለመገምገም የሚደረግ ማንኛውም ሙከራ፣ በኢራን የተፈረጁ የአሜሪካ እና የእስራኤልን “የተንኮል ድርጊቶች” ግምት ውስጥ ማስገባት እንዳለበት ገልፀዋል።

    ይህ አለመግባባት የተፈጠረው፣ የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች በግጭቱ እና በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ካለው የመርከብ እንቅስቃሴ መስተጓጎል ጋር የተያያዙ ችግሮችን እየተጋፈጠች ባለችበት ወቅት ነው።

    የዩኤኢ የአሁኑ እርምጃ፣ ሁለቱ አገሮች የጠለቀ የኢኮኖሚ ግንኙነት ያላቸው እደመሆኑ ከዲፕሎማሲያዊ አለመግባባት ያለፈ መዘዝ ሊኖረው የሚችል ነው።

  14. አሜሪካ በዓለም አቀፉ ወንጀለኞች ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት እና ከፍተኛ ጠበቃ ላይ ማዕቀብ ጣለች

    የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ በዓለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት (አይሲሲ) ፕሬዚዳንት እና ከፍተኛ ጠበቃ ላይ ማዕቀብ መጣሉን ተናገሩ።

    ይህ እርምጃ የትራምፕ አስተዳደር የጦር ወንጀሎችን ለመመርመር ከ120 በላይ በሆኑ አባል አገራት ሥልጣን የተሰጠውን ፍርድ ቤት "ለማፍረስ" የሚያደርገው ዘመቻ አካል ነው።

    ሩቢዮ እንዳሉት አሜሪካ የአይሲሲ ፕሬዝዳንት በሆኑት ጃፓናዊቷ ቶሞኮ አካኔን እና ሴነጋላዊቷ የአይሲሲ ከፍተኛ ጠበቃ አብዱላዬ ሴዬ ላይ ማዕቀብ የጣለችው “የዓለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት ሥልጣንን ለመቀበል ባልተስማሙ አገራት የመንግሥት ባለሥልጣናት ላይ ሕጋዊ እርምጃ በመውሰዳቸው” ነው።

    የዓለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት ከሠራተኞቹ ጎን እንደሚቆም እና ሩቢዮ ይፋ ያደረጓቸው እርምጃዎች "የሕግን የበላይነት ያዳክማሉ" ብሎ እንደሚያምን ተናግሯል።

    ሩቢዮ ፍርድ ቤቱን “ሙስኛ፣ ከፍተኛ ፖለቲካዊ ተጽዕኖ ያለበት፣ ሥልጣኑን ያላግባብ የሚጠቀም እና ከሕጋዊ ሥልጣኑ ወሰን የሚያልፍ” ሲሉ ወንጅለውታል።

    በተጨማሪም አገራት ራሳቸውን የማስተዳደር ሥልጣን ላይ ፍርድ ቤቱ የሚያደርገውን ጣልቃ ገብነት አሜሪካ እንደማትቀበል ተናግረዋል።

    ፕሬዝዳንት ትራምፕም ሆኑ ዋይት ሐውስ እስካሁን ድረስ ስለ ማዕቀቡ ምንም ዓይነት አስተያየት አልሰጡም።

    የትራምፕ አስተዳደር እስካሁን ድረስ ዘጠኝ ዳኞችን እና ዋና አቃቤ ሕግን ጨምሮ ቢያንስ 11 የዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት ባለሥልጣናት ላይ ማዕቀብ ጥሏል።

    ማዕቀቦቹ ንብረቶች እንዳይንቀሳቀሱ የሚያደርጉ፣ ጉዞ የሚያግዱ እና ከአሜሪካ ኩባንያዎች የሚሰጡ አገልግሎቶችን የሚከለክሉ ናቸው።

    እነዚህ ማዕቀቦች የተጣሉት ፍርድ ቤቱ በአፍጋኒስታን በሚገኙ የአሜሪካ ወታደሮች ላይ ባደረገው ምርመራ እና ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁን ጨምሮ በጋዛ በተፈጸሙ የጦር ወንጀሎች ከፍተኛ የእስራኤል ባለሥልጣናት ላይ ባወጣው የፍርድ ቤት ማዘዣ ላይ የበቀል እርምጃ ለመውሰድ ነው።

    ኔታንያሁ የጦር ወንጀሎችን ክሶች ውድቅ አድርገው ፍርድ ቤቱን በፀረ-አይሁድ ስሜት የሚመራ ሲሉ ከስሰዋል። አሜሪካም ሆነች እስራኤል የዓለም አቀፍ ፍርድ ቤቱ አባል አይደሉም።

  15. አሜሪካ በኢራን ላይ የኒውክሌር መሣሪያ የምትጠቀም ከሆነ ቴህራን የአጸፋ ምላሽ ትሰጣለች ሲሉ አንድ የፓርላማ አባል ተናገሩ

    አሜሪካ በኢራን ላይ የኒውክሌር ጦር መሣሪያ የምትጠቀም ከሆነ ቴህራን በዓይነት ምላሽ ትሰጣለች ሲሉ የአገሪቱ የፓርላማ አባል ተናገሩ።

    የኢራን ፓርላማ የብሔራዊ ደህንነት እና የውጭ ፖሊሲ ኮሚሽን አባል የሆኑት ፋዳ ሆሴይን ማሌኪ ይህንን አስተያየት የሰጡት፥ ከኢራኑ የዜና አውታር 'ካባር ኦንላይን' ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ወቅት ነው።

    አሜሪካ በኢራን ላይ የኒውክሌር ጥቃት የመሰንዘሯ ዕድል ምን ያህል እንደሆነ የተጠየቁት ማሌኪ” ትራምፕ በቂ ጥንቃቄ ያልተደረገበት እርምጃ ሊወስዱ አይችሉም ብዬ በድፍረት አልናገርም። ነገር ግን እንዲህ ያለውን ነገር ለማድረግ ይደፍራሉ ብዬም አላስብም፤ ምክንያቱም እንዲህ ዓይነት እርምጃ ዓለምን ወደ አደገኛ ጦርነት ሊከት ይችላል” ብለዋል።

    “እንዲህ ዓይነት እርምጃ ከተወሰደ፣ የኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክም ምላሽ ይሰጣል፤ ምላሹም በኢራን ላይ ጥቅም ላይ ከዋለው የጦር መሣሪያ ዓይነት ጋር ተመጣጣኝ ይሆናል” ሲሉ ተናግረዋል።

    አሜሪካ በኢራን ላይ የኒውክሌር ጦር መሳሪያ ብትጠቀም ኢራንም የኒክሌር ጦር መሳሪያ ትጠቀማለች ማለት ስለመሆኑ የተጠየቁት ማሌኪ "አሜሪካ ማንኛውም ነገር ብትጠቀም፣ ኢራን ምላሽ ትሰጣለች” ብለዋል።

    ማሌክ ኢራን የኒውክሌር ጦር መሣሪኣ አላት ብለው አልተናገሩም።

    ፕሬዚዳንት ትራምፕ ማክሰኞ ዕለት ከኢራን ጋር እየተካሄደ ያለ ንግግር አለመኖሩን እንዲሁም የተያዘ ቀጠሮም እንደሌለ ተናግረዋል።

    አማቻቸው እና የመካከለኛው ምሥራቅ ልዩ ልዑክ የሆኑት ጃሬድ ኩሽነር ለፎክስ ኒውስ እንደተናገሩት ኢራን ለአሜሪካ “ስሜት የሚሰጥ” መደረደሪያ ስላላቀረበች ከአሜሪካ ጋር ስምምነት ላይ ለመድረስ “ፍላጎት አላሳየችም” ብለዋል።

    አሜሪካ እና ኢራን ስድስት ወር ሊሞላው ጥቂት ቀናት በቀሩት ጦርነት ውስጥ ከስምምነት ላይ መድረስ ያልቻሉ ሲሆን የሆርሙዝ ወሽመጥን በመቆጣጠር ረገድም እሰጥ አገባ ውስጥ ናቸው።

    ማሌኪ አሜሪካ ተጨማሪ ወታደራዊ እርምጃ የምትወስድ ከሆነ ኢራን “በርካታ አማራጮች” እንዳሏት በመግለጽ “ተመጣጣኝ እና ከዚያም የከፋ ምላሽ” እንሰጣለን ሲሉ ዝተዋል።

    ማሌኪ እንደተናገሩ “የኢራን በርካታ የጦር መሳሪያዎችና ወታደራዊ አቅሞች እስካሁን ይፋ አልተደረጉም።”

    እንዲሁም ኢራን ከነበረችበት የመከላከል አቋም ወደ “የማጥቃት አቅም” መሸጋገሯን ገልጸዋል።

    ቴህራን እና ዋሺንግተን ከስምምነት ላይ ሊደርሱ አለመቻላቸውን በተመለከተም፥ ትራምፕ በመግባቢያ ሰነዱ ላይ የሰፈሩ ግዴታዎችን ባለማክበራቸው የተነሳ መሆኑን ማሌኪ ተናግረዋል።

    አሜሪካ ከዚህ ቀደም የፈረመቻቸውን ግዴታዎች ሳታከብር ወደ ድርድር አንመለስም ያሉት ማሌኪ የሆርሙዝ ወሽመጥም ሳይከፈት ይቀራል ብለዋል።

    አገራቸው ከኦማን ጋር የምታደርገው ንግግር የተናጠል መሆኑን እና የአሜሪካ ተሳትፎን እንደማትፈልግም ተናግረዋል።

  16. ከሥልጣን የተነሱት የዩክሬን መከላከያ ሚኒስትር ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ እንዲካሄድ ጠየቁ

    የቀድሞው የዩክሬን የመከላከያ ሚኒስትር ማይካኢሎ ፌዶሮቭ በጦርነት ጊዜ ምርጫ እንዲካሄድ ጥሪ አቀረቡ።

    ሩሲያ ከአራት ዓመት ተኩል በፊት ዩክሬንን ሙሉ በሙሉ ከወረረች ወዲህ በአገሪቱ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ተካሄዶ አያውቅም።

    ይህም ለቮሎዲሚር ዘሌንስኪ ፕሬዝዳንትነት ትልቁ ፈተና እንደሆነ በሰፊው ይታሰባል።

    የ35 ዓመቱ ፌዶሮቭ ማክሰኞ ዕለት በዩቲዩብ ላይ ባጋሩት መልዕክት "ዲሞክራሲ በሩሲያ ታግቶ ሊያዝ አይችልም" ሲሉ ተናግረዋል። አክለውም ዩክሬን የምትታገለው "ነፃ የአውሮፓ መንግሥት ሆነን ለመቀጠል ስለምንፈልግ" ነው ብለዋል።

    ጦርነቱ ከተጀመረበት ከ2022 ጀምሮ ዩክሬን በወታደራዊ ሕግ ሥር እየተዳደረች ትገኛለች። ይህም በአገሪቱ የሚደረግ ምርጫ ለጊዜው ታግዶ እንዲቆይ አድርጓል።

    በመከላከያ ሚኒስትርነት በተሾሙ በስድስተኛ ወራቸው ከሥልጣናቸው የተባረሩት ፌዶሮቭ ባስተላለፉት የቪዲዮ መልዕክት ላይ የዜሌንስኪን ስም አልጠቀሱም።

    ዜሌንስኪ የመከላከያ ሚኒስትሩን ከሥልጣን ባነሱበት ወቅት ከፍተኛ ተቃውሞ ገጥሟቸው የነበረ ሲሆን አሁን በቪዲዮው ላይ ስለተላለፈው መልዕክትም ምንም ያሉት ነገር የለም።

    ፌዶሮቭ በሥልጣን ላይ ሳሉ በጣም ተወዳጅ የመከላከያ ሚኒስትር የነበሩ ሲሆን ሚኒስቴሩን በማነቃቃት፣ ሙስናን በመዋጋት እና በግንባር የሚካሄደውን የውጊያ አፈጻጸም ለመተንተን እና ለማሻሻል የሚያስችል መረጃን በመጠቀም ምስጋና ተችሯቸው ነበር።

    ከሥልጣናቸው ለመባረራቸው ምክንያቱ በእርሳቸው እና በሠራዊቱ ዋና አዛዥ ኦሌክሳንድር ሲርስኪ መካከል ከተፈጠረ ውጥረት ጋር የተያያዘ እንደሆነ በሰፊው ተወርቷል።

    በጥቂት ቀናት ውስጥ በአዲስ ሚኒስትር የተተኩት ፌዶሮቭን የዩክሬን ፕሬዚዳንት እንዲመልሷቸው የሚጠይቁ በርካታ ባለሥልጣናት ጫና ፈጥረው ነበር።

    ፌዶሮቭ ቪዲዮውን ከማጋራታቸው ከሰዓታት ቀድም ብሎ ዘሌንስኪ የዬቭኒ ክማራን በመከላከያ ሚኒስትርነት መምረጣቸውን አስታውቀዋል።

    ፌዶሮቭ በቪዲዮው ላይ በቀጣይ የፖለቲካ ሕይወታቸው ምን ሊመስል እንደሚችል ፍንጭ አልሰጡም።

  17. እስራኤል የሶሪያ የአየር ኃይል ጦር ሠፈር ላይ ጥቃት መፈጸሟን አሜሪካ አወገዘች

    እስራኤል በቱርክ ድንበር አቅራቢያ የሚገኝ የሶሪያ ወታደራዊ ጦር ሠፈር ላይ ጥቃት መፈጸሟ ከተሰማ በኋላ ዩናይትድ ስቴትስ ባልተለመደ መልኩ ተችታለች።

    አሜሪካ በጦር ሠፈሩ ላይ የተፈጸመውን ድብደባ “አላስፈላጊ የሆነ ውጥረት” የሚፈጥር በማለት ያለምንም በቂ ምክንያት ሁኔታዎችን የሚያባበብስ ጥቃት መሆኑን ገልጻለች።

    እስራኤል በአቡ ዱሁር የአየር ኃይል ጦር ሠፈር ላይ በፈጸመቻቸው ስምንት ድብደባዎች የአውሮፕላን መንደርደሪያዎችን እና መጋዘኖችን ማጥቃቷን የሶሪያ ቴሌቪዥን ዘግቧል።

    በጥቃቱ በሰው ላይ የደረሰ ጉዳት ስለመኖሩ አልተገለፀም።

    እስራኤል ስለፈጸመችው ጥቃት በቀጥታ አስተያየት ባትሰጥም፥ የቱርክ ወታደሮች የአየር ኃይል ጦር ሠፈሩን እንዲጠቀሙ በመፍቀድ የተደረሰውን የደህንነት መግባቢያ ለመጣስ “ጫፍ ደርሳ ነበር” ስትል ሶሪያን ወንጅላታለች።

    ሶሪያ እና ቱርክ የእስራኤል ጦር ጥቃቶቹን መፈጸሙን በመግለጽ በቀጣናው ውጥረት እንዲባባስ ያደርጋል ሲሉ ገልጸዋል።

    በሶሪያ እና ኢራቅ የዶናልድ ትራምፕ ልዩ ልዑክ ሆነው የተሾሙት እና በቱርክ የአሜሪካ አምባሳደር የሆኑት ቶም ባራክ በማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው በለጠፉት መልዕክት ጥቃቱን አውግዘዋል።

    "በአቡ አል-ዱሁር የአውሮፕላን ማረፊያ ላይ የተፈጸሙትና የተረጋገጡት የእስራኤል ጥቃቶች፣ ለቀጣናዊ መረጋጋት አስተዋጽኦ የማያደርጉ እና አላስፈላጊ የሆነ ውጥረት የሚፈጥሩ ድርጊቶች በመሆናቸው ከፍተኛ ስጋት አለን" ሲሉ ባራክ በኤክስ ገጻቸው ላይ ጽፈዋል።

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ቢሮ ባወጣው መግለጫ ደግሞ “እስራኤል እና ሶሪያ በደህንነት ጉዳዮች ላይ አሁን ያለውን ሁኔታ ለመጠበቅ ተስማምተዋል። ሶሪያ የቱርክ ወታደሮች ከአሌፖ አቅራቢያ በሚገኝ የአየር ማረፊያ እንዲሰፍሩ በመፍቀድ ይህንን ሁኔታ ለመጣስ ተቃርባ ነበር” ብሏል።

    የሶሪያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በበኩሉ “ምክንያት ሊቀርብለት የማይችል የትንኮሳ ተግባር” በማለት “የቀጣናው ደህንነት እና መረጋጋትን” አደጋ ላይ የሚጥል ብሎታል።

    ቱርክ ጦሯ ከድንበሩ በ70 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ወደሚገኘው ወደ አቡ ዱሁር የአየር ኃይል ጦር ሠፈር ስለመንቀሳቀሳቸው ምንም ማረጋገጫ አልሰጠችም።

    ነገር ግን እስራኤል ስጋት ይደቅናል ስትል የሰጠችውን መግለጫ ውድቅ አድርጋለች።

    የቱርክ የኮሚኒኬሽን ዳይሬክቶሬት፣ የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ያቀረባቸው ክሶች ሐሰተኛ እና እስራኤል በሶሪያ ላይ የምታደርሰውን ጥቃት ቅቡልነት ለመስጠት የተደረጉ መሆናቸውን ገልጿል።

    ቱርክ ጥቃቶቹ የሶሪያን ሉዓላዊነት እና የግዛት መብት የሚጥሱ መሆናቸውን አስታውቃለች።

  18. እስራኤል በሶሪያ ያደረሰችውን ጥቃት አሜሪካ አወገዘች

    በሰሜን ምዕራብ ሶሪያ፣ ኢድሊብ ግዛት በሚገኝ ወታደራዊ አውሮፕላን ማረፊያ ላይ እስራኤል የፈጸመችውን ጥቃት አሜሪካ አወገዘች።

    እስራኤል ያደረሰችውን ጥቃት “አላስፈላጊ ግጭትን ማባባስ” ስትል አሜሪካ አውግዛለች።

    በሶሪያ እና ኢራቅ የአሜሪካ ልዩ ልዑክ ቶም ባራክ ብዙም ባልተለመደ ሁኔታ በዋይት ሀውስ በሰጡት መግለጫ፤ ሁሉም ወገኖች ከወታደራዊ ግጭት ይልቅ ለንግግር ቅድሚያ እንዲሰጡ አሳስበዋል።

    የሶሪያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቀደም ሲል ባወጣው መግለጫ በኢድሊብ በሚገኘው የአየር ኃይል መቀመጫ የተፈጸመውን ጥቃት “ምክንያት አልባ” ሲል አውግዟል።

    በጥቃቱ የአውሮፕላን ማረፊያው መንደርደሪያ፣ የጥገና እና ክምችት ክፍሎች ላይ ጉዳት ደርሷል።

    በጥቃቱ የተጎዱ ሰዎች ስለመኖራቸው ሪፖርት አልተደረገም። እስራኤልም እስካሁን ድረስ አስተያየት አልሰጠችም።

  19. “ትራምፕ ስለ ሆርሙዝ ወሽመጥ ያላቸውን ቅዠት በቅርቡ እናስተካክለዋለን”- ኢራን

    ዶናልድ ትራምፕ የሆርሙዝ ወሽመጥን “አዲስ የአሜሪካ ግዛት” ማለታቸውን ተከትሎ የኢራን የውጭ ጉዳይ ምክትል ሚኒስትር ካዚም ጋሪባባዲ “ቅዠታም” ሲሉ ፕሬዝዳንቱን ወርፈዋል።

    “ዶናልድ ትራምፕ የፐርዥያ ባሕረ ሰላጤን በትክክል መጻፍ እንደተማሩት ሁሉ ስለ ሆርሙዝ ወሽመጥ ያላቸውን ቅዠትም በቅርቡ እናስተካክለዋለን” ሲሉ ጽፈዋል።

    ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያቸው በለጠፉት ምሥል ላይ የሆርሙዝ ወሽመጥን አክብበው “የአሜሪካ አዲስ ግዛት” ሲሉ ጽፈዋል።

    የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ምክትል ሚኒስትርም ይሄንን ምሥል በድጋሚ አጋርተዋል።

    በሌላ በኩል የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ መሐመድ ባጋር ጋሊባፍ በበኩላቸው አሜሪካ የመግባቢያ ሰነዱን ስምምነቶች ካልተገበረች የሆርሙዝ ወሽመጥ እንደማይከፈት አስታውቀዋል።

  20. ፕሬዝዳንት ትራምፕ የሆርሙዝ ወሽመጥ “የአሜሪካ አዲስ ግዛት ነው” አሉ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያቸው በለጠፉት ምሥል ላይ የሆርሙዝ ወሽመጥን አክብበው “የአሜሪካ አዲስ ግዛት” ሲሉ ጽፈዋል።

    ትራምፕ ከሦስት ቀናት በፊት “በቅርቡ የሆርሙዝ ወሽመጥ የአሜሪካ ግዛት ተብሎ ይታወጃል” ብለው ነበር።

    “ኢራንን አሸንፈን ስንጨርስ የሆርሙዝ ወሽመጥ የአሜሪካ ግዛት መሆኑን አውጃለሁ” ሲሉም ተናግረዋል።

    ከፕሬዝዳንቱ ንግግር በኋላ ዋል ስትሪት ጆርናል አስተያየታቸውን የጠየቃቸው የዋይት ሐውስ ባለሥልጣን የትራምፕ ንግግር “ቀልድ” መሆኑን ገልጸዋል።

    የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባዔ መሐመድ ባጋር ጋሊባፍ በበኩላቸው አሜሪካ የመግባቢያ ሰነዱን ስምምነቶች ካልተገበረች የሆርሙዝ ወሽመጥ እንደማይከፈት አስታውቀዋል።

    የኢራን ዋነኛ ተደራዳሪ ጋሊባፍ እንደተናገሩት አሜሪካ የጣለችው የባሕር ላይ እገዳ እንዲሁም የነዳጅ እና ንብረቶች ማዕቀብ ካልተነሳ፣ በሁሉም ግንባሮች ወታደራዊ እርምጃ ካልተገታ የሆርሙዝ ወሽመጥ አይከፈትም።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ የሆርሙዝ ወሽመጥን በተመለከተ በኢራን እና በኦማን መካከል የሚደረገው ድርድር እስከሚጠናቀቅ ድረስ እየተጠበቀ መሆኑን ኳታር አስታወቃለች።

    የኳታር የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ ማጂድ አንሳሪ እንዳሉት የሆርሙዝ ወሽመጥን በተመለከተ የሚደረሰው ስምምነት በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ድርድር እንዲቀጥል ያግዛል።

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ባለው ፍጥጫ ምክንያት ከፍተኛ መጠን ያለው የነዳጅ እና የጋዝ ምርት የሚተላለፍበት ሆርሙዝ ለመርከቦች እንቅስቃሴ አደገኛ ሆኗል።

    በዚህም ምክንያት በወሽመጡ በኩል ለማለፍ የሞከሩ መርከቦች ላይ ጥቃት እየተፈጸመ ሲሆን፣ የመርከቦች እንቅስቃሴም በከፍተኛ ሁኔታ ቀንሷል።