የአሜሪካ ጦር በኢራን ወደቦች ላይ የተጣለውን እገዳ ጥሶ ሲጓዝ የነበረ መርከብ ለማስቆም ሚሳዔል መተኮሱን አስታወቀ

የፎቶው ባለመብት, US Central Command
የአሜሪካ ጦር ሄሊኮፕተሮች በኢራን ወደቦች ላይ የተጣለውን እገዳ የጣሰ የጭነት መርከብ ላይ ሚሳዔል ተኩሰው መምታታቸው ተገለጸ።
የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ፣ ሴንቲኮም፣ ኤምኤች-60 የተባለው ሄሊኮፕተር ማክሰኞ ዕለት ሁለት ሚሳዔሎችን ተኩሶ የመርከቡን የሞተር ክፍል መምታቱን አስታውቋል።
መርከቧ የፓናማን ሰንደቅ አላማ የምታውለበልብ የነበረች ሲሆን ወደ ኦማን ባሕረ ሰላጤ ለማቋረጥ እየሞከረች ነበር ተብሏል።
ሴንቲኮም “የመርከቧ የሲቪል ሠራተኞች በአሜሪካ ኃይሎች የተሰጠውን ተደጋጋሚ ማስጠንቀቂያ ችላ በማለታቸው” እርምጃው መወሰዱን ይፋ አድርጓል።
አክሎም መርከቧ “ከእንግዲህ በኋላ ወደ ኢራን አታቋርጥም” ሲል በመግለጫው ላይ ጠቅሷል።
ኢራን በጉዳዩ ላይ አስተያየት አልሰጠችም።
አሜሪካ የካቲት 21/2018 ዓ.ም. በኢራን ላይ ጦርነት ከከፈተች በኋላ ወደ ኢራን ወደቦች የሚገቡ እና የሚወጡ መርከቦች ላይ የእንቅስቃሴ እገዳ ጥላለች።
ቴህራን ለአሜሪካ ጥቃት እና እገዳ ምላሽ ለመስጠት በባህረ ሰላጤው በሚገኙ አገራት ላይ ጥቃት የፈጸመች ሲሆን የሆርሙዝ ወሽመጥንም ሙለ በሙሉ ዘግታለች።
የዓለም አንድ አምስተኛው ነዳጅ የሚጓጓዝበት የባሕር መስመር በመዘጋቱ የነዳጅ ዋጋ ከፍተኛ ጭማሪ አሳይቷል።
አደራዳሪዎቹ ሁለቱን ተፋላሚ ወገኖች ወደ ድርድር ጠረጴዛ ለማምጣት መቸገራቸውን ተናግረዋል።
ኢራን እና አሜሪካ በሰኔ ወር የተፈራረሙት የመግባቢያ ሰነድ በመክሸፉ የተነሳ ዳግም ግጭት አገርሽቷል።
ሴንቲኮም በኤክስ ገጹ ላይ ባጋራው መግለጫ ኤም/ቪ ቬላ የተባለችው ይህች መርከብ ወደ ኢራን ወደብ ለመሻገር ጥረት እያደረገች እንደነበር ጠቅሷል።
በጥቃቱ የደረሰ ጉዳት ወይንም ሞት ስለመኖሩ ያለው ነገር የለም።
የአሜሪካ የእገዳ እርምጃ "ሙሉ በሙሉ በሥራ ላይ መሆኑን" ያስታወሰው መግለጫው፣ እአአ እስከ ነሐሴ 11 ድረስ ሴንትኮም እገዳውን ጥሰው ለማለፍ የሞከሩ 55 የንግድ መርከቦችን አቅጣጫ እንዳስቀየረ፣ ደንቦችን ያላከበሩ 3 መርከቦችን ከአገልግሎት ውጭ ማድረጉን እንዲሁም 2 መርከበኞችን እንደተቆጣጠረ አመልክቷል።
በዓለም አቀፍ ደረጃ ዕውቅና ያገኘው የየመን መንግሥት በበኩሉ በቀይ ባህር ውስጥ በሚገኝ የጭነት መርከብ ላይ በኢራን የሚደገፉት ሁቲዎች በፈጸሙት ጥቃት ስድስት ሰዎች መገደላቸውንና 10 ሰዎች መቁሰላቸውን አስታውቋል።
ሁቲዎች የሳዑዲ አረቢያ ወታደራዊ ቁሳቁሶችን የጫነ መርከብ መምታታቸውን ይፋ አድርገው ነበር። ይህም ቡድኑ የኢራን ጦርነት ከተጀመረ ወዲህ በመርከብ ላይ የፈጸመው የመጀመሪያው ከባድ ጥቃት ሆኖ ተመዝግቧል።












