ቀጥታ, አሜሪካ በኢራን ወደቦች ላይ የጣለችውን እገዳ ላልተወሰነ ጊዜ ልታራዝም እንደምትችል አስታወቀች

አሜሪካ ሐሙስ ዕለት በኢራን ወደቦች ላይ የጣለችውን እገዳ ላልተወሰነ ጊዜ በማራዘም የምጣኔ ሃብት ጫናውን ልታጠናክር አንደምትችል ተናገረች። አሜሪካ ይህንን ያለችው በሁለቱ አገራት መካከል ይደረጋል ተብሎ የሚጠበቀው ድርድር ባለመሳካቱ ውጥረት ባየለበት እና የዓለም የነዳጅ ዘይት አቅርቦት እየቀነሰ በመጣበት ወቅት ነው። የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር የሆኑት ፒት ሄግሴት ለጋዜጠኞች ጦሩ በኢራን ላይ የተጣለውን እገዳ ለማስቀጠል በቀጣናው መቆየት የሚያስችል አቅም አለው ብለዋል።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. የአሜሪካ ጦር በኢራን ወደቦች ላይ የተጣለውን እገዳ ጥሶ ሲጓዝ የነበረ መርከብ ለማስቆም ሚሳዔል መተኮሱን አስታወቀ

    የአሜሪካ ጦር ሂሊኮፕተር

    የፎቶው ባለመብት, US Central Command

    የአሜሪካ ጦር ሄሊኮፕተሮች በኢራን ወደቦች ላይ የተጣለውን እገዳ የጣሰ የጭነት መርከብ ላይ ሚሳዔል ተኩሰው መምታታቸው ተገለጸ።

    የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ፣ ሴንቲኮም፣ ኤምኤች-60 የተባለው ሄሊኮፕተር ማክሰኞ ዕለት ሁለት ሚሳዔሎችን ተኩሶ የመርከቡን የሞተር ክፍል መምታቱን አስታውቋል።

    መርከቧ የፓናማን ሰንደቅ አላማ የምታውለበልብ የነበረች ሲሆን ወደ ኦማን ባሕረ ሰላጤ ለማቋረጥ እየሞከረች ነበር ተብሏል።

    ሴንቲኮም “የመርከቧ የሲቪል ሠራተኞች በአሜሪካ ኃይሎች የተሰጠውን ተደጋጋሚ ማስጠንቀቂያ ችላ በማለታቸው” እርምጃው መወሰዱን ይፋ አድርጓል።

    አክሎም መርከቧ “ከእንግዲህ በኋላ ወደ ኢራን አታቋርጥም” ሲል በመግለጫው ላይ ጠቅሷል።

    ኢራን በጉዳዩ ላይ አስተያየት አልሰጠችም።

    አሜሪካ የካቲት 21/2018 ዓ.ም. በኢራን ላይ ጦርነት ከከፈተች በኋላ ወደ ኢራን ወደቦች የሚገቡ እና የሚወጡ መርከቦች ላይ የእንቅስቃሴ እገዳ ጥላለች።

    ቴህራን ለአሜሪካ ጥቃት እና እገዳ ምላሽ ለመስጠት በባህረ ሰላጤው በሚገኙ አገራት ላይ ጥቃት የፈጸመች ሲሆን የሆርሙዝ ወሽመጥንም ሙለ በሙሉ ዘግታለች።

    የዓለም አንድ አምስተኛው ነዳጅ የሚጓጓዝበት የባሕር መስመር በመዘጋቱ የነዳጅ ዋጋ ከፍተኛ ጭማሪ አሳይቷል።

    አደራዳሪዎቹ ሁለቱን ተፋላሚ ወገኖች ወደ ድርድር ጠረጴዛ ለማምጣት መቸገራቸውን ተናግረዋል።

    ኢራን እና አሜሪካ በሰኔ ወር የተፈራረሙት የመግባቢያ ሰነድ በመክሸፉ የተነሳ ዳግም ግጭት አገርሽቷል።

    ሴንቲኮም በኤክስ ገጹ ላይ ባጋራው መግለጫ ኤም/ቪ ቬላ የተባለችው ይህች መርከብ ወደ ኢራን ወደብ ለመሻገር ጥረት እያደረገች እንደነበር ጠቅሷል።

    በጥቃቱ የደረሰ ጉዳት ወይንም ሞት ስለመኖሩ ያለው ነገር የለም።

    የአሜሪካ የእገዳ እርምጃ "ሙሉ በሙሉ በሥራ ላይ መሆኑን" ያስታወሰው መግለጫው፣ እአአ እስከ ነሐሴ 11 ድረስ ሴንትኮም እገዳውን ጥሰው ለማለፍ የሞከሩ 55 የንግድ መርከቦችን አቅጣጫ እንዳስቀየረ፣ ደንቦችን ያላከበሩ 3 መርከቦችን ከአገልግሎት ውጭ ማድረጉን እንዲሁም 2 መርከበኞችን እንደተቆጣጠረ አመልክቷል።

    በዓለም አቀፍ ደረጃ ዕውቅና ያገኘው የየመን መንግሥት በበኩሉ በቀይ ባህር ውስጥ በሚገኝ የጭነት መርከብ ላይ በኢራን የሚደገፉት ሁቲዎች በፈጸሙት ጥቃት ስድስት ሰዎች መገደላቸውንና 10 ሰዎች መቁሰላቸውን አስታውቋል።

    ሁቲዎች የሳዑዲ አረቢያ ወታደራዊ ቁሳቁሶችን የጫነ መርከብ መምታታቸውን ይፋ አድርገው ነበር። ይህም ቡድኑ የኢራን ጦርነት ከተጀመረ ወዲህ በመርከብ ላይ የፈጸመው የመጀመሪያው ከባድ ጥቃት ሆኖ ተመዝግቧል።

  2. የሊቢያ ወታደራዊ ደኅንነት ኃላፊ መኪና ላይ በተጠመደ ቦምብ ተገደሉ

    ፋውዚ ማንሱ

    የፎቶው ባለመብት, Libya National Army / X

    የሊቢያ ብሔራዊ ወታደራዊ ደኅንነት ኃላፊ ፋውዚ ማንሱሪ መኪናቸው ላይ በተጠመደ ቦምብ መገደላቸውን የአገሪቱ ጦር አስታወቀ።

    ጦሩ ዛሬ ማክሰኞ ባወጣው መግለጫ እንደገለጸው፤ ደቡባዊ ሊቢያን የሚቆጣጠው ጦር ወታደራዊ ደኅንነት ኃላፊ የተገደሉት ሰኞ ዕለት ነው።

    ወታደራዊ ባሥልጣኑ ከመስጊድ ከወጡ በኋላ መኪናቸው ላይ የተጠመደ ቦምብ ፈንድቶ መገደላቸውን መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።

    ፍንዳታው የተከሰተው በምሥራቅ ሊቢያ ቤንጋዚ ግዛት ነው።

    ከሙአመር ጋዳፊ ውድቀት በኋላ ሊቢያ በእርስ በርስ ጦርነት እና ባለመረጋጋት መፈተኗን ቀጥላለች።

    የመንግሥታቱ ድርጅት ዕውቅና የሰጠው በአብደልሐሚድ ዘይባ የሚመራው የትሪፖሊ መንግሥት እና የቤንጋዚ ጦር አዣዥ ኻሊፋ ሐፍታር አገሪቱን ለመቆጣጠር ፍልሚያ ላይ ናቸው።

    የሊቢያ ጦር ባወጣው መግለጫ ግድያውን “የከዳተኞች የወንጀል ድርጊት” ብሎታል። “ሽብርተኛነት እና ሊቢያን ለማወክ የሚደረግ ጥረትን” መዋጋት እንደሚቀጥልም አስታውቋል።

  3. ኢራን እና አሜሪካ ‘አንዳች ስምምነት ላይ’ ለመድረስ መቃረባቸውን ፓኪስታን መግለጿ ተዘገበ

    ቴህራን

    የፎቶው ባለመብት, Anadolu via Getty Images

    ኢራን እና አሜሪካ “አንዳች ስምምነት ላይ” ለመድረስ መቃረባቸውን ፓኪስታን መግለጿን ብሉምበርግ ዘገበ።

    ሮይተርስ የዜና ወኪል እንደዘገበው፤ የፓኪስታን መከላከያ ሚኒስቴር ካዋጃ አሲፍ ከብሉምበርግ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ ሁለቱ አገራት ሰላም ለማውረድ “ስምምነት ወይም መግባባት” ላይ ለመድረስ ተቃርበዋል ብለዋል።

    ሚኒስቴሩ “ሁኔታው በድጋሚ ቅርጽ እየያዘ ነው። ወደ ሰላም ለመቃረብ ስምምነት ወይም በሁለቱም ወገኖች በኩል የጋራ መግባባት አለ” ብለዋል።

    ይህ ዜና የተሰማው ኢራን ከአሜሪካ ጋር ድርድር እየተካሄደ እንደሚገኝ በቅርቡ ማስታወቋን ተከትሎ ነው። ንግግሩ በአሸማጋዮች በኩል መቀጠሉን ቴህራን ገልጻለች።

  4. የሶሪያ ፍርድ ቤት ባሽር አል-አሳድ በሌሉበት በሞት እንዲቀጡ ወሰነ

    ባሽር አል-አሳድ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የሶሪያ ፍርድ ቤት ከሥልጣናቸው የተወገዱት ባሽር አል-አሳድ በሌሉበት በሞት እንዲቀጡ ውሳኔ አሳለፈ።

    አምባገነኑ አል-አሳድ በአገሪቱ የእርስ በርስ ጦርነት ወቅት የጦር ወንጀሎች እና በሰብአዊነት ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች በመፈጸም ጥፋተኛ ተብለዋል።

    አል-አሳድ በአውሮፓውያኑ 2024 ከሥልጣን መወገዳቸውን ተከትሎ ከቤተሰባቸው ጋር ሆነው ከደማስቆ ወደ ሞስኮ ከሸሹ በኋላ የፍርድ ቤት ውሳኔ ሲተላለፍባቸው የአሁኑ ለመጀመሪያ ጊዜ ነው።

    የአል-አሳድ የአጎት ልጅ የሆነው የቀድሞው የደቡብ ሶሪያ፣ ዴራ ግዛት የፖለቲካ ደኅንነት ኃላፊ አቴፍ ናጂብም ሞት ተፈርዶበታል።

    የእስረኞች ልብስ አድርጎ በፍርድ ቤት ውሳኔው ሲተላለፍ ተገኝቷል።

    ዴራ ግዛት የአል-አሳድን አገዛዝ የጣለው ተቃውሞ መነሻ በመሆን ትታወቃለች።

    በአውሮፓውያኑ የካቲት 2011 ታዳጊዎች ግድግዳ ላይ ፀረ መንግሥት ተቃውሞ በመጻፍ መከሰሳቸው መጠነ ሰፊ ተቃውሞ አስነስቷል። የፀጥታ ኃይሎችም ከፍተኛ እርምጃ ወስደዋል።

    ይህ እርምጃ አገር አቀፍ ተቃውሞ አቀጣጥሏል። በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተገድለዋል።

    የሶሪያ ጊዜያዊ አስተዳደር ከ50 ዓመታት በላይ ከአል-አሳድ አስተዳደር ጋር ትስስር ያላቸውን ሰዎች ፍርድ ቤት እያቀረበ ነው።

  5. የዓለም የጤና ድርጅት ‘ኢቦላ ቫይረስ ቀድሞናል፤ እኛ እየተከተልነው ነው’ ሲል አስጠነቀቀ

    የጤና ባለሙያዎች

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ሰሞነኛው የዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ የኢቦላ ወረርሽኝ የተከሰተው በሽታው በይፋ ከመታወጁ ቢያንስ ከሦስት ወራት በፊት በመሆኑ፣ የጤና ባለሥልጣናቱ ቀድሞ የተሰራጨውን በሽታ ለመቆጣጠር አሁንም እየጣሩ መሆኑን የዓለም ጤና ድርጅት ገለጸ።

    ግንቦት ላይ ወረርሽኝ መሆኑ ከታወጀበት ጊዜ አንስቶ ከ1 ሺህ 900 በላይ ሰዎች የሞቱበት ይህ ክስተት፣ በሟቾች ብዛት ሁለተኛው የኢቦላ ወረርሽኝ ሆኗል።

    የበሽታው የሥርጭት መጠን አሁንም ከፍተኛ መሆኑ ቫይረሱን ለመቆጣጠር እየጣሩ ላሉት ባለሥልጣናት ተጨማሪ ስጋትን ፈጥሯል።

    አሁን የተከሰተው ‘ቡንዲቡግዮ’ የተባለ የኢቦላ ዝርያ የተነሳው የደኅንነት ስጋት ካለበት የዴሞክራቲክ ኮንጎ ምስራቃዊ ክፍል ነው። የአካባቢው የጸጥታ ችግር በሽታውን ለመቆጣጠር የሚደረገውን ጥረት አስተጓጉሏል።

    ይህንን ዝርያ ለማከም ጥቅም ላይ እንዲውል የጸደቀ ክትባት ወይም መድኃኒት አለመኖሩም ተጨማሪ ተግዳሮት ነው።

    የዓለም ጤና ድርጅት የአፍሪካ ዳይሬክተር ዶ/ር መሐመድ ጃናቢ “ቫይረሱን እየተከተልን ነው፤ ነገር ግን ቀድሞናል” ሲሉ የወረርሽኙ ማዕከል በሆነችው ቡኒያ ከተማ በተካሄደ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ተናግረዋል።

    ዳይሬክተሩ፣ ቫይረሱ የካቲት ላይ እንደጀመረ እና በወቅቱ ወባ ወይም ታይፎይድ ነው በሚል ሕክምና ሲሰጥ እንደነበር የሚያሳይ ጥናት መኖሩን ጠቅሰዋል።

    የጸጥታ ችግሩ የጤና ባለሙያዎችን ሥራ የገደበ አንድ ጉዳይ መሆኑን ያነሱት ዶ/ር ጃናቢ፣ በዚህም ምክንያት ሕክምና እያገኙ ያሉት 30 በመቶ ገደማ ታካሚዎች እንደሆኑ እና ሌሎቹ ቤታቸው ውስጥ ሕይወታቸው እያለፈ መሆኑን ገልጸዋል።

    ሐዘንተኞች አስከሬንን የሚነኩበት ባሕላዊ የቀብር ሥነ ሥርዓት መኖሩ እንዲሁም አንዳንድ ሰዎች የጤና ባለሙያዎች ላይ ያላቸው ጥርጣሬም በተጨማሪ ተግዳሮትነት ተነስቷል።

    እስካሁን 4 ሺህ 294 ሰዎች በበሽታው መያዛቸው የተረጋገጠ ሲሆን የ1 ሺህ 960 ታማሚዎች ሕይወት ማለፉን የኮንጎ ጤና ሚኒስቴር አስታውቋል።

    በኢቦላ ታሪክ ከፍተኛ የሟቾች ቁጥር የተመዘገበው በአውሮፓውያኑ ከ2014 እስከ 2016 ባሉት ዓመታት ነበር። በወቅቱ በምዕራብ አፍሪካ በተከሰተው ወረርሽኝ የ11 ሺህ 325 ሰዎች ሕይወት አልፏል።

  6. በካናዳ 'ቀበቶ አላስርም' ባለ ሕፃን ምክንያት በረራ ተሰረዘ

    የፖርተር አየር መንገድ አውሮፕላን

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    በካናዳ ቀበቶ አላስርም ባለ ሕፃን ምክንያት በረራ ከተሰረዘ በኋላ በአውሮፕላን ከሚጓዙ ሕፃናት ጋር በተያያዘ የሚወሰዱ የደኅንነት እርምጃዎች ውዝግብ አስነሱ።

    ፖርተር አየር መንገድ እንደገለፀው አውሮፕላኑ ከአምስት ቀናት በፊት ከቪክቶሪያ ወደ ቶሮንቶ ለመብረር ተዘጋጅቶ የነበረ ቢሆንም አንድ ሕፃን ወንበር ላይ ቆሞ ቀበቶ አላስርም በማለቱ በረራው ተስተጓጉሏል።

    የበረራ ሰዓቱ በመዘግየቱ እና ማኮብኮቢያው ከመዘጋቱ በፊት አውሮፕላኑ መነሳት ባለመቻሉ ተሳፋሪዎች በማግሥቱ ለመብረር መገደዳቸውንም አየር መንገዱ አስረድቷል።

    ክስተቱ እንደዚህ ዓይነት ሁኔታዎች ሲያጋጥሙ ወላጆች የአየር መንገዱን ሕግ ለማክበር መውሰድ ስላለባቸው እርምጃ እንዲሁም አየር መንገዶችም መስጠት ያላባቸውን ምላሽ በተመለከተ የተለያዩ አስተያየቶች እንዲንሸራሸሩ አድርጓል።

    በርካታ ሰዎች “በአንድ ሕፃን ምክንያት በረራ መስተጓጎል አልነበረበት፤ መውረድ የነበረባቸው ወላጁ እና ልጁ ነበሩ” ብለዋል።

    ሌሎች ደግሞ ሕፃናት በበረራ ወቅት እንደሚፈሩ እና እንደሚጨነቁ በመግለፅ ትዕግስት እንደሚያስፈልግ መክረዋል።

    ፖርተር አየር መንገድ በበኩሉ “ችግሩን ለመፍታት የሕፃኑ ወላጅ እና የበረራ ሰራተኞች ያደረጉት ሙከራ አልተሳካም።” ብሏል።

    “በዚህ ደኅንነቱ ባልተጠበቀ ሁኔታ አውሮፕላኑ መብረር ስላልቻለ ወደ ጣቢያው ተመልሶ ሁለቱ መንገደኞች እንዲወርዱ ተደርጓል።” ሲልም አክሏል።

    የሕፃናት አቪየሽን ደኅንነት ባለሙያ የሆኑት ሊያ ቱሶ፣ "የፖርተር ሰራተኞች በረራውን በመሰረዛቸው የሕፃኑን እና የበረራ ቡድኑን አባላት ጨምሮ የተሳፋሪዎችን ደኅንነት ጠብቀዋል" ሲሉ ለቢቢሲ ገልጸዋል።

    “በተገቢ ሁኔታ እንዳልተቀመጠ ዕቃ ሁሉ ሕፃናትም አውሮፕላኑ በሚነሳበት እና በሚያርፍበት ጊዜ ሊወረወሩ ይችላሉ” ሲሉም በራሳቸውም ሆነ በተሳፋሪዎች ላይ ጉዳት ሊያስከትሉ እንደሚችሉ ተናግረዋል።

  7. ፕሬዝዳንት ትራምፕ ኢራን ለገደለቻቸው እና ላቆሰለቻቸው ሰዎች ካሳ መክፈል አለባት አሉ

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ

    የፎቶው ባለመብት, Bloomberg via Getty Images

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፣ ኢራን “ለገደለቻቸው እና ክፉኛ ላቆሰለቻቸው ሰዎች በሙሉ” ካሳ መክፈል አለባት ሲሉ ቴህራን ላቀረበችው የጦርነት ጉዳት ማካካሻ ጥያቄ ምላሽ ሰጡ።

    ሊባኖስ እና ጋዛን ጨምሮ በሌሎች አገራት ሕዝቦች ላይ ለደረሱ “ጉዳቶች እና ሞቶች” ኢራን ተጠያቂ መሆን እንዳለባትም ተናግረዋል።

    ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ይህንን ያሉት፣ ቴህራን ለአሜሪካ ያቀረበቻቸው ቅድመ ሁኔታዎች ምላሽ እስካላገኙ ድረስ ወሳኙ የባሕር መተለላፊያ ሆርሙዝ እንደማይከፈት ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ላይ ከገለጸች በኋላ ነው።

    አሜሪካ እና እስራኤል በከፈቱት ጥቃት ለደረሰው ጉዳት ከሳ እንዲከፈል እንዲሁም ማዕቀቦች እና ወታደራዊ ዛቻዎች እንዲያበቁ የሚሉት ከቴህራን ጥያቄዎች መካከል ናቸው።

    ትናንት ሰኞ ምሽት ለዚህ ምላሽ የሰጡት የአሜሪካው ፕሬዝዳንት በምላሹ የራሳቸውን ቅድመ ሁኔታ አቅርበዋል። “በመንገድ ዳር ቦንቦች እና በበርካታ ግጭቶች ለገደሏቸው እንዲሁም ክፉኛ ላቆሰሏቸው ለእነዚያ ሁሉ ሰዎች ከኢራን ካሳ እጠይቃለሁ” ብለዋል።

    ከ26 ዓመት በፊት በአውሮፓውያኑ 2000 የመን ውስጥ በአሜሪካ ጦር መርከብ ላይ በደረሰ ፍንዳታ የተገደሉ 17 የአሜሪካ ባሕር ኃይል አባላት እንዲሁም “በውጊያ የተገደሉ በሺህዎች የሚቆጠሩ” ሰዎች ጉዳይ ካሳ ውስጥ መካተት እንዳለበትም ጠቅሰዋል።

    አሜሪካው የፌደራል ወንጀል ምርመራ ቢሮ ኤፍቢአይ፣ ትራምፕ የጠቀሱት 17 ባሕር ኃይል አባላት የተገደሉበት ጥቃት የተፈጸመው በአል ቃኤዳ እንደሆነ ከዚህ ቀደም መግለጹን ሮይተርስ ዘግቧል።

    በተጨማሪም ትራምፕ የኢራን መንግሥት “ባለፉት 50 ዓመታት ውስጥ ለገደላቸው በሺህዎች የሚቆጠሩ ንጹኃን ተቃዋሚዎች ቤተሰቦች” ካሳ መክፈል እንዳለበት ተናግረዋል።

    “ባለፉት አምስት ወራት ውስጥ ተገድለዋል” ያሏቸውን “52,000” ኢራናውያንንም አብረው አንስተዋል።

    ባለፈው ታህሳስ ላይ የኢራን ኢስላማዊ ሪፐብሊክ የተነሳበትን ሕዝባዊ ተቃውሞ ለማፈን በወሰደው እርምጃ በሺህዎች የሚቆጠሩ ሰዎች መገደላቸው ይታወሳል።

    መቀመጫውን በውጭ አገር ያደረገው የኢራን የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች የዜና ወኪል በዚህ ተቃውሞ የተገደሉ ሰዎች ብዛት 6,872 እንደሆነ ገልጾ ነበር።

    በተጨማሪም ትራምፕ “ከኢራን በሊባኖስ፣ ሶርያ፣ የመን እና ጋዛ ሕዝብ ላይ ለደረሰው ጉዳት እና ሞት ኃላፊነት መውሰድ አለባት” ብለዋል።

    ፕሬዝዳንቱ ይህንን ጉዳይ “ወደፊት በሚደረጉ ማንኛውም እና ሁሉም ድርድሮች” ላይ እንዲካተት ለተወካዮቻቸው ትዕዛዝ መስጠታቸውንም አስታውቀዋል።ተጨማሪ ያንብቡ፦ ኢራን ሆርሙዝን ለመክፈት ከትራምፕ የጠየቀቻቸው ስድስት ቅድመ ሁኔታዎች ምንድን ናቸው?

  8. በማሊ የጦር ሠፈርን ለመቆጣጠር በተደረገ ውጊያ በርካቶች መገደላቸው ተነገረ

    የማሊ ጦር መለያ ልብስ

    የፎቶው ባለመብት, AFP via Getty Images

    እሁድ ዕለት በማሊ የሚገኝ የጦር ሠፈርን ለመቆጣጠር የሞከሩ በርካታ እስላማዊ ተዋጊዎች መገደላቸውን አገሪቱ ባለሥልጣናት ተናገሩ።

    ከአል ቃኢዳ ጋር ግንኙነት ያለው ‘ኑስራት አል-ኢስላም ወል-ሙስሊሚን’ የተባለ ጂሃዲስት ቡድን ሳን በተባለ ከተማ ውስጥ የሚገኘው ጦር ሠፈር ላይ ለተከፈተው ጥቃት ኃላፊነቱን የወሰደ ሲሆን ስፍራውን እንደተቆጣጠረም ገልጿል።

    በተመሳሳይ ወታደሮች የተገደሉበት የማሊ ጦር በበኩሉ፣ የጦር ሠፈሩን ቁጥጥር ተነጥቋል መባሉን አስተባብሏል። ወታደሮቹ ግን “በጊዜያዊነት ማፈግፈጋቸውን” ተናግሯል።

    ከአስር ዓመት ገደማ በፊት በአገሪቱ ሰሜናዊ ክፍል የጂሃዲስት ታጣቂዎች እንቅስቃሴን ማየት የጀመረችው ማሊ፣ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ የደኅንነት ሁኔታዋ እየተባባሰ መጥቷል።

    የእሁድ ዕለቱ ጥቃት ንጋት 11 ሰዓት ላይ ተጀምሮ ለሁለት ሰዓታት መቆየቱን እማኞች ‘አርኤፍአይ’ ለተባለው የፈረንሳይ ሬዲዮ ተናግረዋል።

    በሞተርሳይክል እና በእግር ከመጡት አጥቂዎች መካከል የተወሰኑት ወደ ጦር ሠፈሩ ለመግባት ወታደራዊ ዩኒፎርም ለብሰው እንደነበረም ገልጸዋል።

    በተደረገው ውጊያ 10 ወታደሮች መገደላቸውን እና ታጣቂዎቹ ለተነወሰ ጊዜ ካምፑን ተቆጣጥረውት እንደነበር ኤኤፍፒ ዘግቧል።

    ሳን ውስጥ የሚገኘው የ23ኛው ክፍለ ጦር አዛዥ ሌተናንት ኮሎኔል ኤል ኦምራኒ በለቀቁት ቪዲዮ፣ “ጠላት ተወግዷል፣ ጥቃቱም በስኬት ተቀልብሷል። 40 የገደማ አሸባሪዎች ተደምስሰዋል” ብለዋል።

    የሠራዊቱ ወታደሮች “የትም እንዳልሄዱ” እና ወታደራዊ ሠፈሩ በጦሩ ቁጥጥር ስር እንደሆነ የተናገሩት አዛዡ፣ ነዋሪዎች ጥንቃቄ እንዲያደርጉ አሳስበዋል።

    “የ23ኛው [ክፍለ ጦር] ካምፕ ባዶ አይደለም፤ በሠራዊቱ ጥበቃ ሥር ይገኛል” ሲሉም ተደምጠዋል።

    ማሊ ከአውሮፓውያኑ 2012 አንስቶ በታጣቂዎች ጥቃት እየተናጠች ሲሆን፣ የአገሪቱ ሰሜናዊ እና ምሥራቃዊ ሰፊ ክፍሎችም ከመንግሥት ቁጥጥር ውጪ ናቸው።

  9. ዩክሬን በሩሲያ ላይ በፈጸመችው ጥቃት ቢያንስ 13 ሰዎች ተገደሉ

    በሩሲያ ኒዝኔካምስክ ከተማ የሚገኝ ነዳጅ ማጣሪያ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    ዩክሬን በሩሲያዋ ግዛት ታታርስታን ሪፐብሊክ ውስጥ በፈጸመችው የድሮን ጥቃት አንድ ሕጻንን ጨምሮ 13 ሰዎች መገደላቸውን የሞስኮ ባለሥልጣናት ተናገሩ።

    ከትናንት እሁድ ምሽት ጀምሮ የተፈጸመው ድብደባ ሞስኮ ዩክሬን ላይ ሙሉ ጦርነት ከከፈተች ወዲህ ሩሲያ ላይ ተሰንዝረው በርካታ ሰዎችን ከገደሉ ጥቃቶች አንዱ ሆኗል።

    ዩክሬን ከድንበሯ ከ1,100 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኘው ኒዝኔካምስክ ከተማ ላይ ፈጽማዋለች ስለተባለው ጥቃት እስካሁን አስተያየት አልሰጠችም።

    የዩክሬን ጦር ኒዝኔካምስክ ከተማ ውስጥ የሚገኘው ‘ታኔቮ’ የነዳጅ ማጣሪያን መምታቱን ገልጿል። የዩክሬኑ የመከላከያ ቴክኖሎጂ አምራች ‘ፋየርፖይንት’ በበኩሉ ጥቃቱ የተፈጸመው በኩባንያው የተመረቱ ‘ኤፍፒ-1’ ድሮኖች መሆኑን አስታውቋል።

    ጥቃቱ ከሌሊት እስከ ጠዋት ድረስ ለሰዓታት የቆየ እንደነበር የአካባቢው ምንጮች ተናግረዋል።

    ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የተለቀቁ እና ትክክለኛነታቸው የተረጋገጠ ቪዲዮዎች ጭስ እና እሳት ወደ ሰማይ ሲወጣ አሳይተዋል። የአየር ጥቃት ማስጠንቀቂያ ደውል ድምፅም ቪዲዮው ላይ ይሰማል።

    ሩሲያ የኢንዱስትሩ ተቋማት እና የመኖሪያ አካባቢዎች ዒላማ መደረጋቸውን አረጋግጣለች። የሩሲያ የምርመራ ኮሚቴ ባወጣው መግለጫ፤ “በማንኛውም ወታደራዊ ኦፕሬሽን ውስጥ ተሳትፎ የሌላቸው ሰላማዊ ሰዎች ቦታው ላይ ነበሩ” ብሏል። ቢቢሲ ይህንን መረጃ በራሱ አላረጋገጠም።

    ትናንት ሌሊት ከዩክሬን የተላኩ 450 ድሮኖች በሩሲያ አየር መከላከያዎች ተመትተው መውደቃቸው ተገልጿል።

    ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ዩክሬን ከድንበሯ ረጅም ርቀት ላይ የሚገኙ የሩሲያ ዒላማዎች ላይ የተሳኩ ጥቃቶችን ማድረስ ጀምራለች።

    እነዚህ ጥቃቶች ብዙውን ጊዜ ዒላማ የሚያደርጉት መጋዘኖች እና የኃይል መሠረተ ልማቶችን ሲሆን፣ በዚህ ምክንያት የሚገደሉ ሰላማዊ ሰዎች ቁጥርም ጨምሯል።

    ዩክሬን እነዚህ መሠረተ ልማቶች ሩሲያ ለምታካሂደው ጦርነት የገቢ እና የሎጂስቲክ አስተዋጾ ያደርጋሉ የሚል ክስ ታቀርባለች።

  10. በኃይለኛ አውሎ ንፋስ ምክንያት ቻይና አንድ ሚሊዮን ሰዎች ቤታቸውን ለቅቀው እንዲወጡ አደረገች

    'ዶልፊን' አውሎ ንፋስ ዕሁድ አመሻሽ ላይ በምስራቅ ቻይና ሲከሰት

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የምስሉ መግለጫ, 'ዶልፊን' አውሎ ንፋስ እሁድ አመሻሽ ላይ በምሥራቅ ቻይና ተከስቷል

    በቻይና የተከሰተው ‘ዶልፊን' የተባለ ከባድ አውሎንፋስ መሬት መድረሱን ተከትሎ፣ ባለሥልጣናት የፋይናንስ ማዕከል የሆነችውን ሻንጋይን ጨምሮ ከአገሪቱ ምሥራቃዊ አካባቢዎች ከአንድ ሚሊዮን በላይ ሰዎች ቤታቸውን ለቅቀው እንዲወጡ አደረጉ።

    አውሎ ንፋሱ ከፍተኛ ዝናብ ያስከተለ ሲሆን በተከሰተበት ክልል በሙሉ የትራንስፖርት እንቅስቃሴዎችን አቋርጧል። ሰኞ ዕለት ብቻ በሻንጋይ ውስጥ ወደ 1,000 የሚጠጉ በረራዎች ተሰርዘዋል።

    ባለሥልጣናቱ ‘ዶልፊን’ የተባለው አውሎ ንፋስ ወደ ‘ትሮፒካል’ አውሎ ንፋስ ዝቅ ስለማለቱ የገለፁ ቢሆንም፣ ወደ ሰሜን አቅጣጫ እየተጓዘ ያለው አውሎ ንፋሱ እስከ ረቡዕ ድረስ ኃይለኛ ዝናብ፣ ጎርፍ እና የመሬት መንሸራተት አደጋ ሊያስከትል እንደሚችል ማስጠንቀቃቸውን ቀጥለዋል።

    ቻይናን ከመቱት አውሎ ንፋሶች ሁሉ የጎላው ስለሆነው ‘ዶልፊን’ አውሎ ንፋስ፥ የአገሪቱ ባለሥልጣናት ቀደም ሲል ከፍተኛ የጥንቃቄ መልዕክት አስተላልፈው ነበር።

    እሁድ ዕለት ከሰዓት በኋላ በዤጂያንግ ግዛት ዩሁዋን ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ ሲከሰት የንፋሱ ፍጥነት በሰዓት 150 ኪሎ ሜትር እንደነበረ የሜትሮሎጂ ባለሥልጣናት አስታውቀዋል።

    ሰኞ ዕለት ደግሞ በሻንዶንግ፣ ሄናን፣ ሁቤይ፣ አንሁይ፣ ጂያንግሱ፣ ዤጂያንግ ግዛቶች እና በሻንጋይ ከተማ ከፍተኛ ዝናብ እንደሚዘንብ ተተንብዮ ነበር። መንግሥት፣ ህዝቡ ከቤት ውጭ ከሚደረጉ እንቅስቃሴዎች እንዲቆጠብ ሲያሳስቡ በርካታ የቱሪስት መስህቦች ዝግ ሆነው እንዲቆዩ መወሰኑ ታውቋል።

  11. ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ የምትፈጽማቸው ጥቃቶች መቀጠላቸው ተገለፀ

    መርከቦች በሆርሙዝ ላይ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚፈፅማቸው ጥቃቶች መቀጠላቸውን የብሪታንያ የባህር ላይ ንግድ ስራዎች ድርጅት አስታወቀ።

    በሆርሙዝ ወሽመጥ በሚንቀሳቀሱ የንግድ መርከቦች ላይ የሚደረጉ ጥቃቶች በመቀጠላቸው፥ በመካከለኛው ምሥራቅ ያለው የስጋት መጠን "ከባድ" እንደሆነ መቀጠሉን ድርጅቱ አስታውቋል።

    ድርጅቱ እንደገለፀው፣ ባለፈው ቅዳሜ አንድ የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች የነዳጅ መርከብ በውሃ መተላለፊያው ላይ ዒላማ የተደረገ ሲሆን፥ በወሽመጡ በኩል የሚደረገው የንግድ እንቅስቃሴ በጥቂት መርከቦች ብቻ ተወስኖ በ"ዝቅተኛ" ደረጃ ላይ ይገኛል።

    “ለልየታ የሚረዱ የራዲዮ ግንኙነቶችን ማድረግ፣ ድሮኖችን ማብረር እና የንግድ መርከቦችን ዒላማ ያደረገ ክትትልን ጨምሮ የአብዮታዊ ዘቡ ጥቃቶች እና የትንኮሳ እርምጃዎች ቀጥለዋል” ሲል ድርጅቱ ባወጣው የቅርብ ጊዜ ወርሃዊ ሪፖርቱ ገልጿል።

    ሪፖርቱ አክሎም “እነዚህ ድርጊቶች ኢራን ቁልፍ በሆኑ የባህር ላይ ማጓጓዣ መስመሮች ላይ ያላትን ተጽዕኖ የማጠናከር እና በመስመሮቹ በሚያልፉ መርከቦች ላይ ግፊት የማድረግ ፍላጎት እንዳላት የሚያመለክቱ ሆነው ቀጥለዋል” ብሏል። በመርከቦች አቅራቢያ የሚደረጉ የሚሳዔል ጥቃቶች እና ፍንዳታዎችን ጨምሮ ቀጥተኛ ወታደራዊ እንቅስቃሴዎችም ወደ ኦማን በሚወስዱት ደቡባዊ መስመሮች (በሊማ-ኻሳብ-ኩምዛር አካባቢ) መቀጠላቸው ተጠቅሷል።

    የብሪታንያ የባህር ላይ ንግድ ስራዎች ድርጅት፣ ያልተመዘገቡ እና ያልፈነዱ ፈንጂዎች የሚያደርሷቸው አደጋዎችም በሆርሙዝ ወሽመጥ ሊቀጥሉ እንደሚችሉ አስጠንቅቋል።

  12. በሆርሙዝ መከፈት ላይ ስምምነት ባለመደረሱ የነዳጅ ዋጋ መልሶ ጨመረ

    ነዳጅ ማጣሪያ

    የፎቶው ባለመብት, Reuters

    ወሳኙ የሆርሙዝ ወሽመጥ ስለመከፈቱ በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ስምምነት ለመድረስ የሚያስችል ሁኔታ ባለመኖሩ የነዳጅ ዋጋ ቅዳሜ እና እሁድ ከነበረበት ጭማሪ አሳየ።

    አሜሪካ የባሕር ላይ መተላለፊያ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲከፈት ብትፈልግም ኢራን ግን ከዚያ በፊት መሟላት ያለባቸው ስድስት ጉዳዮችን አቅርባለች።

    ሮይተርስ እንደዘገበው ዛሬ ሰኞ ማለዳ በእስያ ገበያ ላይ የብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ በበርሜል ወደ አንድ ዶላር የሚጠጋ ጭማሪ አሳይቶ 84.46 ዶላር ሲሆን፣ የአሜሪካ ዌስት ቴክሳስ ድፍድፍ ነዳጅ በበርሜል 61 ሳንቲም ጨምሮ 78.79 ሆኗል።

    ኢራን እና ኦማን የሆርሙዝ ወሽመጥን መልሶ ለመክፈት ከስምምነት ይደርሳሉ በሚል ተስፋ ባለፈው ሳምንት የነዳጅ ዋጋ ከሰባት ፐርሰንት በላይ ቅናሽ አሳይቶ ነበር።

    አሜሪካ በኢራን ላይ የምትፈጽመውን ጥቃት ተከትሎ ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ ላይ ቁጥጥር በማድረግ ጥቃቶችን በመፈጸሟ የመርከቦች እንቅስቃሴ ተገትቶ ቆይቷል። በዚህም የነዳጅ ዋጋ ላይ ተጽእኖ ተፈጥሮ ቆይቷል።

  13. እስራኤል የትራምፕን ባለ 15 ነጥብ የጋዛ ሰላም ዕቅድ ውድቅ ማድረጓን ኔታንያሁ ተናገሩ

    ትራምፕ እና ኔታንያሁ

    የፎቶው ባለመብት, Getty Images

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ የአሜሪካውፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ያቀረቡትን ባለ 15 ነጥብ የጋዛ ሰላም ዕቅድ ውድቅ ማድረጋቸውን ገለጹ።

    ኔታንያሁ የሰላም ዕቅዱን ውድቅ ለማድረግ የሰጡት ምክንያት በቅድሚያ ሐማስ ትጥቅ መፍታት አለበት የሚል ነው።

    የትራምፕ የሰላም ቦርድ ባለፈው ወር ሐማስ እና ሌሎች በጋዛ የሚገኙ ታጣቂ ቡድኖች “ሙሉ በሙሉ ትጥቅ እንዲፈቱ” ከስምምነት ላይ መደረሱን ተናግሮ ነበር።

    ነገር ግን ሐማስ ከባድ መሣሪያዎቹን የሚያስረክበው እስራኤል “ማንኛውም ጥቃትን” ስታቆም እና ወታደሮቿን ከጋዛ ስታስወጣ መሆኑን ተናግሯል።

    እስራኤል በጥቅምት ወር የመጀመርያው የተኩስ አቁም ከተደረሰ በኋላ በጋዛ ጥቃት መፈጸሟን ቀጥላለች።

    ኔታንያሁ እሁድ ዕለት ለተሰበሰበው ካቢኔያቸው “እስራኤል ባለ 15 ነጥብ ሰነዱን ውድቅ አድርጋለች” ተናግረዋል።

    የእስራኤል ጦር “ሐማስ በትክክል ትጥቅ እስኪፈታ ድረስ [ከጋዛ] አይወጣም፤ እንዲሁም በዜጎቻችን እና በወታደሮቻችን ላይ የሚቃጣን ማንኛውም ስጋት ይቀለብሳል” ሲሉ ተናግረዋል።

    እሁድ ዕለት የሐማስ ባለሥልጣን ለቢቢሲ በሰጡት ምላሽ ቡድኑ ለስምምነቱ ያለውን ቁርጠኝነት "እንደገና ያረጋግጣል"፤ እንዲሁም የ15 ነጥብ ዕቅዱን ተግባራዊ ለማድረግ "በቁም ነገር እና በኃላፊነት ስሜት ለመሳተፍ" ዝግጁ ነው ብለዋል።

    በተጨማሪም አደራዳሪዎች “ስምምነቱን ሁሉም አካላት ተግባራዊ ማድረጋቸውን አንዲያረጋግጡ” ጥሪ አቅርበዋል።

    እስራኤል ዕቅዱን ውድቅ ማድረጓ መስከረም ወር ላይ ትራምፕ ያቀረቡት የጋዛ ዕቅድ ችግር እንደገጠመው ማሳያ ተደርጎ ተቆጥሯል።

    ዕቅዱ የሰላም ቦርድ መመስረትን፣ የሐማስ ትጥቅ መፍታትን፣ የእስራኤል ወታደሮች ከጋዛ መውጣትን እና የጋዛን መልሶ ግንባታ የያዘ ነው።

    የኔታንያሁ አቋም ብዙዎችን ያስገረመ አልነበረም። ግን ይህንን አቋማቸውን ለማሳወቅ ትንሽ ጊዜ ወስደዋል።

    የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር በትራምፕ ዕቅድ ደስተኛ አለመሆናቸው በግልጽ የሚታወቅ ነው። ነገር ግን በተመሳሳይ ጊዜ የቅርብ አጋራቸውን ማስቆጣት አለመፈለጋቸው አቋማቸውን ለማዘግየታቸው እንደምክንያት ከተጠቀሱት ነገሮች መካከል አንዱ ነው።

    ትራምፕ "ዘላቂ ሰላምና ደህንነት ለማምጣት ትልቅ እርምጃ" ብለው የጠሩትን ነገር ካሳወቁ ከአንድ ሳምንት በላይ ሆኖታል ።

    ሐማስ ትጥቅ ለመፍታት የተስማማው ለመጀመሪያ ጊዜ ሲሆን እንደ ቅድመ ሁኔታ ያስቀመጠው ደግሞ እስራኤል ጦሯን ከጋዛ ማስወጣት እንዳለባት ነው።

    እሁድ ዕለት ኔታንያሁ እርሳቸው በሥልጣን ላይ እያሉ ይህ እንደማይሆን ለማሳየት ቆርጠው የተነሱ አስመስሏቸዋል።

    ሐማስ መጀመሪያ ትጥቅ መፍታት እንዳለበት የተናገሩት ጠቅላይ ሚኒስትሩ “የይስሙላ ትጥቅ መፍታት” ሊሆን እንደማይችል ተናግረዋል።

    ኔታንያሁ ከአሜሪካ ባለሥልጣናት ጋር ወደፊት እንዴት መቀጠል እንደሚቻል እየተወያዩ መሆኑን ተናግረዋል።

    “ሀሳቦች አሏቸው፤ አንዳንዶቹ ተቀባይነት ያላቸው ሲሆኑ ሌሎቹ ደግሞ ቅቡልነት የሌላቸው ናቸው፤ እናም በእነዚህ ጉዳዮች ላይ እንዴት አቋም መያዝ እንዳለብን እናውቃለን” ብለዋል።