ኢራን በሆርሙዝ ጉዳይ ከኦማን ጋር የምታደርገው ድርድር የመጨረሻው ምዕራፍ ላይ መሆኑን አስታወቀች
ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል የሚደረገውን የመርከቦች ጉዞ በተመለከተ ከኦማን ጋር ስምምነት ላይ መድረሷን ገለጸች።
የቴህራን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ እስማኤል ባጋኢ "የመጨረሻው ምዕራፍ ላይ" እንደሆነ ስለገለጹት ስምምነት ዝርዝር መረጃ ከመስጠት ተቆጥበዋል።
ይሁን እንጂ ከኦማን የተደረሰው ስምምነት በወሽመጡ የሚደረግ ጉዞ ደኅንነቱ የተጠበቀ ለመሆኑ ዋስትና እንዳልሆነ አንስተዋል። ቃል አቀባዩ ይህንን ያሉት አሜሪካ የኢራን ወደቦች ላይ የጣለችው የጉዞ እገዳ የወሽመጡ የደኅነት ሁኔታን ተፅዕኖ ውስጥ እንደከተተው በመጥቀስ ነው።
አሜሪካ እና ኦማን የስምምነት ዕቅዱን በተመለከተ አስተያየት አልሰጡም።
ቴህራን በወሽመጡ የሚያልፉ መርከቦች ላይ እጥለዋለሁ የምትለው ክፍያ ኢራን እና አሜሪካን ካላስማሙ ጉዳዮች አንዱ ነው።
ኢራን በወሳኙ የባሕር መስመር የሚያልፉ መርከቦች ከሚይዙት ጭነት ዋጋ ውስጥ ከ5% እስከ 7% ክፍያ መሰብሰብ እንደምትፈልግ አንድ ከፍተኛ የኢራን ባለሥልጣን ለሮይተርስ ተናግረዋል።
ኦማን ከኢራን ጋር በምታደርገው ንግግር የክፍያ መጠኑ 3% ገደማ እንዲሆን ጠይቃለች። የአሜሪካ ፍላጎት ደግሞ ምንም አይነት ክፍያ እንዳይኖር ነው።
የሮይተርስ ዘገባ እንደሚያሳየው፤ የቀረበው ስምምነት ቴህራን ወደ ፋርስ ባሕረ ሰላጤ የሚገቡ መርከቦች ጉዞ ላይ ቁጥጥር እንዲኖራት ያደርጋል።
የካቲት ላይ አሜሪካ እና እስራኤል በኢራን ጥቃት ከከፈቱበት ጊዜ አንስቶ ቴህራን ከዓለም አቀፉ የነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ ምርት ውስጥ 20 በመቶ ገደማው የሚተላለፍበትን የሆርሙዝ ወሽመጥ ዘግታለች።
ማክሰኞ ዕለት የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ወሽመጡ “በቅርቡ” የማይከፈት ከሆነ ኢራን “እጅግ በከባዱ እንደምትመታ” አስጠንቅቀዋል።
ትራምት ማስጠንቀቂያውን የሰጡት፣ ከፍተኛ የአሜሪካ ባለሥልጣናት ከኢራን ጋር የሚደረጉ ንግግሮች በዚህ ሳምንት መጨረሻ በሆርሙዝ የሚደረግ ጉዞን በድጋሚ ለማስጀመር በሚያስችል ደረጃ ማሻሻል እንዳሳዩ ከተናገሩ በኋላ ነው።
ኢራን ግን ከአሜሪካ ጋር እየተነጋገረች እንዳልሆነ እና ለመደራደርም እቅድ እንደሌላት በተደጋጋሚ ገልጻለች።
ሁለቱ አገራት እና አሸማጋዮች በሚያደርጓቸው ውይይቶች ውስጥ አንዱ ቁልፍ ጉዳይ የሆርሙዝ ወሽመጥ መከፈት ነው።
የኢራን ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ በሰጡት መግለጫ፣ በሆርሙዝ የሚያልፉ መርከቦች የሚከተሉትን ትክክለኛ “መስመር” በተመለከተ ከኦማን ጋር ስምምነት ላይ መደረሱን አስታውቀዋል።
“በአሜሪካ በኩል ሆርሙዝ ወሽመጥን ደኅንነቱ ያልተጠበቀ የሚያደርጉት ምክንያቶች አሁንም አሉ” ያሉትን ቃል አቀባዩ የዋሽንግተንን ”የባሕር እገዳ እንዲሁም በኢራን እና በጥቅሞቿ የሚቃጡት ሌሎች ተንኳሽ እና ዛቻ የተሞላባቸው እርምጃዎችን” በዋነኝነት ጠቅሰዋል።
ስምምነት የተደረሰበት የባሕር መስመር ጊዜያዊ እና ከሁለት እስከ አራት ወራት ክፍት ሆኖ ሊቆይ የሚችል መሆኑን የኢራን የውጭ ጉዳይ ምክትል ሚኒስትር ካዜም ጋሪባባዲ ‘ኢርና’ ለተሰኘው ለኢራን መንግሥት ዜና ወኪል ተናግረዋል።