ይህ ዝቅተኛ ዳታን በመጠቀም ጽሑፍ ብቻ የሚቀርብበት የቢቢሲ አማርኛ ድረ ገጽ ነው
በዛምቢያ ምርጫ ላይ አቤቱታ የሚቀርብበት የጊዜ ገደብ ሲቃረብ የአገሪቱ ፍርድ ቤቶች ተዘጉ
በቅርቡ በተካሔደው ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ውጤት ላይ አቤቱታ ለማቅረብ ተያዘው የጊዜ ገደብ እየቀረበ በመጣበት በአሁኑ ወቅት በዛምቢያ ዋና ከተማ ሉሳካ እና በሌሎችም የአገሪቱ ክፍሎች የሚገኙ የፍርድ ቤቶች መዘጋታቸው ታወቀ።
በአንዳንድ ፍርድ ቤቶች ባለጉዳዮች እንዳይገቡ ለመከላከል ባልተለመደ ሁኔታ ፖሊሶች መቆማቸው ሪፖርት ተደርጓል።
የተቃዋሚ ዕጩው ብራያን ሙንዱቢሌ በምርጫውን 38 በመቶ ድምጽ በማግኘት ሁለተኛ ደረጃ ላይ መቀመጣቸው ከተገለፀ በኋላ፣ የተዛቡ ሁኔታዎች መኖራቸውን በመጥቀስ እንደሚከራከሩ ተናግረዋል። ፕሬዝዳንት ሃካይንዴ ሂቺሌማ 60 በመቶ ድምጽ በማግኘት ለሁለተኛ ጊዜ አሸንፈዋል።
በውዝግብ በተሞላው የድኅረ ምርጫ ወቅት፣ ታዋቂ የተቃዋሚ ፓርቲ አባል በጥይት መግደላቸውን እና ሌሎችም መታሰራቸውን ተከትሎ ሙንዱቢሌ በስጋት ምክንያት ተደብቀው ይገኛሉ።
ሰኞ በፕሬዝዳንታዊ ምርጫው ውጤት ላይ አቤቱታ የሚቀርብበት የመጨረሻው ቀን ነው። አቤቱታው ለመስከረም 1 በታቀደው የሂቺሌማ በዓለ-ሲመት ላይ ተጽዕኖ ሊያሳድር እንደሚችል ይታመናል።
ሰኞ ዕለት ወደ ፍርድ ቤቶች የሄዱ ጠበቆች እንዲወጡ እየተደረጉ ነበር።
አንድ ጠበቃ ለቢቢሲ እንደተናገረው፣ ሦስት የታጠቁ ሰዎች መኪናው ጋር ቀርበው ራሳቸውን ካስተዋወቁት በኋላ አካባቢውን ለቅቆ እንዲሔድ አዘውታል።
የተዘጉት ፍርድ ቤቶች በሉሳካ የሚገኘውን ከፍተኝ ፍርድ ቤት፣ ሕገ-መንግሥታዊውን ፍርድ ቤት የሚያካትተውን ጠቅላይ ፍርድ ቤት እና በርካታ አካባቢያዊ ፍርድ ቤቶችን ያካትታሉ።
ፍርድ ቤቶቹ መቼ እንደሚከፈቱ የሚታወቅ ነገር የለም። ቢቢሲ የዛምቢያ ፖሊስን እና የፍትህ አካላትን አስተያየት ጠይቋል።
ፍርድ ቤቶች "በደኅንነት ምክንያቶች" በመዘጋታቸው ሁሉም ሠራተኞች ወደ ሥራ እንዳይገቡ በመግለፅ አንድ የፍትህ አስተዳደር ባለሥልጣን ትዕዛዝ መስጠታቸውን በመጥቀስ የአካባቢው ሚዲያዎች ዘግበዋል።
በአንዳንድ የተቃዋሚ ፓርቲዎች በኦንላይን የተጋራው የባለሥልጣኑን ትዕዛዝ የያዘው ደብዳቤ፣ በስጋትነት የተጠቀሰውን የደኅንነት ሁኔታ በዝርዝር አይገልፅም።
አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች የፍትህ ሥርዓቱን ነፃነት ጥያቄ ውስጥ በማስገባት ስለ ፍርድ ቤቶቹ መዘጋት ስጋታቸውን ገልፀዋል።
የተቃዋሚው ድምጽ የሆኑት ኢማኑኤል ምዋምባ፣ እርምጃው ሙንዱቢሌ የፕሬዝዳንታዊ ምርጫ አቤቱታቸውን እንዳያቀርቡ ለመከላከል ያለመ ነው ሲሉ ተችተዋል።
የዛምቢያ የሕግ ማኅበር፣ የፍርድ ቤቶች መዘጋት እና በሉሳካ በሚገኙ ፍርድ ቤቶች መግቢያ በር ላይ ከባድ የጦር መሳሪያ የታጠቁ ወታደሮች መኖራቸው እንደሚያሳስበው አስታውቋል።
ስለ ፍርድ ቤቶች መዘጋት እና እስከመቼ እንደሚቆይ ለሕዝቡም ይህን በተመለከተ ለሕግ ባለሞያዎች ምንም ዓይነት መደበኛ ማብራሪያ እንዳልተሰጠም ገልጿል።
"የፍርድ ቤቶቹ መዘጋት በተለይ አስቸኳይ የፍትህ ጣልቃ ገብነት በሚያስፈልጋቸው ሰዎች የፍትህ ጥያቄ ላይ ቀጥተኛ አንድምታ አለው" ሲል ማኅበሩ በሰጠው መግለጫ አስታውቋል።
ፍርድ ቤቶች በተዘጉበት ሁኔታ ውስጥ ለሂቺሌማ በዓለ-ሲመት የሚደረገው ዝግጅት ቀጥሏል።