ትራምፕ ከኢራን ጋር “በፍጥነት” ስምምነት ለመድረስ ሲባል የታቀዱ ጥቃቶች እንዲቋረጡ ማድረጋቸውን ተናገሩ

ዶናልድ ትራምፕ “በፍጥነት” ስምምነት መድረስ እንዲቻል፣ ኢራን ላይ የሚፈጸመው ጥቃት እንዲቆም ማድረጋቸውን አስታወቁ። እንደ ፕሬዝዳንቱ ገለጻ የሚደረሰው ስምምነት ሆርሙዝ ወሽመጥ ወዲያውኑ እንዲከፈት እንዲሁም “ኢራን [የደቀነችው] የኒውክሌር ስጋት” እንዲቆም የሚያደርግ ነው።

ጭምቅ ሃሳብ

የቀጥታ ሽፋን

  1. በፔሩ የቱሪስት አውሮፕላን ተከስክሶ 13 ሰዎች ሞቱ

    ፔሩ ውስጥ ቱሪስቶችን ጭኖ ሲበርር የነበረ አነስተኛ አውሮፕላን ተከስክሶ፣ በውስጡ የነበሩት 13 ሰዎች በሙሉ ሕይወታቸው ማለፉን የአገሪቱ ባለሥልጣናት እና መገናኛ ብዙኃን ገለጹ።

    ‘ሴስና ካራቫን ሲ-208’ የተባለው አውሮፕላን ቅዳሜ ዕለት የተከሰከሰው ‘ናዝካ ላይንስ’ በተሰኘው አርኪኦሎጂ ስፍራ በኩል እየበረረ በነበረበት ወቅት ነው። አውሮፕላኑ 11 ተሳፋሪዎች እና ሁለት ፓይለቶች ይዞ ነበር።

    ከተሳፋሪዎቹ መካከል ሁለት ጀርመናውያን፣ ሁለት የስፔን ዜጎች እና ሰባት ጣሊያናውያን ቱሪስቶች እንደነበሩ የፔሩ የመንግሥት የዜና ወኪል ዘግቧል። አደጋው የደረሰበት ምክንያት እስካሁን አልታወቀም።

    በደቡባዊ ፔሩ የሚገኘው ‘ናዝካ ላይንስ’፣ በበረሃ አሸዋ ላይ የተሳሉ ጥንታዊ የእንስሳት ስዕሎች የሚታዩበት እና በዩኔስኮ የዓለም ቅርስነት የተመዘገበ ታዋቂ የቱሪስት ስፍራ መስህብ ነው።

    ብዙውን ጊዜ ቱሪስቶች ስዕሎቹ ምን ያህል ስፋት ያለው ስፍራ ላይ እንዳረፉ ለመመልከት በአነስተኛ አውሮፕላኖች ይበራሉ።

    የፔሩ ፖሊስ አመራሩ ሜጀር ጆርጅ አንደራዴ "ከአደጋው አስከፊነት የተነሳ በሕይወት የተረፈ ሰው የለም። እስካሁን የአራት ሰዎችን አስከሬን አግኝተናል" ማለታቸውን ኤኤፍፒ ዘግቧል።

    ‘ፒስኮ’ በተባለው የፔሩ ከተማ ከሚገኝ አየር ማረፊያ የተነሳው አውሮፕላን የተከሰከሰው ፑዌብሎ ቪየሆ የተባለው ክልል ውስጥ ነው።

    የዜና ወኪሉ ሮይተርስ ባወጣው አንድ ቪዲዮ ላይ የእሳት አደጋ ሠራተኞች ከስብርባሪዎች ጭስ የሚወጣበት የአደጋ ስፍራ ላይ ውሃ ሲረጩ ያሳያል።

    ‘ዴ ናስካ’ ግዛት አስተዳደር ባወጣው መግለጫ አውሮፕላኑ ‘ኤሮዲያና’ የተሰኘው የፔሩ የአገር ውስጥ አየር መንገድ ንብረት መሆኑን አስታውቋል።

    አየር መንገዱ በበኩሉ ጉዳዩ "የሚመለከታቸው ባለሥልጣናት ከሚያወጧቸው መመሪያዎች ጋር በተጣጣመ መልኩ የበረራ መርሃ ግብሩን እንደሚገመግም" መግለጹን ሮይተርስ ዘግቧል።

    ይህ ታዋቂ የቱሪስት መስህብ ባለፉት አስርት ዓመት ውስጥ ሌሎች የአውሮፕላን አደጋዎችንም አስተናግዷል።

    በአውሮፓውያኑ 2022 አንድ አነስተኛ የቱሪስት አውሮፕላን በናዝካ ላይስ በኩል ሲበርር ተከስክሶ ሰባት ተሳፋሪዎች ሞተዋል።

    2010 ላይ ደግሞ ሌላ የቱሪስት አውሮፕላን ወድቆ ተሳፍረው የነበሩ ስድስት ሰዎችን ገድሏል።

  2. በሞስኮ ሬስቶራንት ውስጥ ቦምብ ፈንድቶ ሦስት ሰዎች መገደላቸው ተገለጸ

    በሩሲያ ዋና ከተማ ሞስኮ በሚገኝ የጣሊያን ሬስቶራንት፤ ቤት ውስጥ የተሠራ ቦምብ ፈንድቶ ሦስት ሰዎች መገደላቸውን እና 21 ሰዎች መቁሰላቸውን የአገሪቱ የመንግሥት መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    በከተማዋ ማዕከል አቅራቢያ ፍንዳታ ያጋጠመው በአገሪቱ ሰዓት አቆጣጠር ምሽት 2 ሰዓት ገደማ እንደሆነ የጸጥታ ባለሥልጣናት ገልጸዋል።

    የሩሲያ ብሔራዊ ፀረ ሽብር ኮሚቴ እንዳስታወቀው፤ ፈንጂውን ያዘችው ሴት ወደ ሬስቶራንት ለመግባት ስትሞክር የምግብ ቤቱ ጥበቃ አስቁሟታል። ይሁን እንጂ ቦምቡ በመፈንዳቱ ፈንጂውን የያዘችው ሴት፣ ጥበቃውን እና የምግብ ቤቱ ደምበኛ ተገድለዋል።

    በስታሊን ዘመን ከተገነቡት ታዋቂ የሞስኮ ሰማይ ጠቀስ ፎቆች በአንዱ ላይ የሚገኘው ሬስቶራንቱ፤ በሰዓቱ አንድ የግል ዝግጅት እያስተናገደ እንደነበር ተገልጿል።

    ባለሥልጣናት፣ ለዚህ ዝግጅት የተጋበዙ ሰዎችን ዝርዝር ይፋ አላደረጉም፤ የጥቃቱ ዒላማ እንደነበር የሚታመነው ማን እንደሆነም አላሳወቁም።

    በቦታው የነበሩ እማኞች በበኩላቸው ከፍንዳታው በኋላ በደም የተሸፈኑ ሰዎች ከሥፍራው ሲወጡ መመልከታቸውን ተናግረዋል።

    መጀመሪያ ላይ የወጡ ዘገባወች፤ ፍንዳታው ያጋጠመው በሬስቶራንቱ ማብሰያ ክፍል ውስጥ እንደሆነ ጠቅሰው ነበር። ሬስቶራንቱ ቆይቶ ባወጣው መግለጫ ግን "ውጭ ላይ ችግር እንደነበር" ገልጿል።

    ምግብ ቤቱ አቅራቢያ የሚገኘው ኩድሪንስካያ አደባባይ ለአጭር ጊዜ ዝግ ተደርጎ ነበር። በርካታ ሰዎች በምሽት ለሚደረግ ጉዞ ብስክሌቶቸቻውን በመያዝ በአቅራቢያው ተሰብስበው የነበረ ቢሆንም ዕቅዳቸው ተሰርዟል።

    የሩሲያው 'አርአይኤ' ዜና ወኪል በለቀቀው አንድ ቪዲዮ ላይ በከፍተኛ ሁኔታ የታጠቁ የጸጥታ አካላት በሥፍራው መገኘታቸውን እና ቦታው ለሕዝብ ተዘግቶ እንደነበር ይታያል።

    ባለፉት ዓመታት በርካታ የሩሲያ ከፍተኛ ወታደራዊ አመራሮች ሞስኮ ውስጥ እና በመዲናዋ ዙሪያ ተገድለዋል። የሩሲያ መንግሥት ለእነዚህ ጥቃቶች ተጠያቂ የሚያደርገው ጦርነት የገጠማትን ዩክሬንን ነው።

  3. ትራምፕ ከኢራን ጋር “በፍጥነት” ስምምነት እንዲደረስ ሲባል የታቀዱ ጥቃቶች እንዲቋረጡ ማድረጋቸውን ተናገሩ

    የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ “በፍጥነት” ስምምነት ሊደረስ የሚችልበት ዕድል በመኖሩ ኢራን ላይ የሚፈጸመው ጥቃት እንዲቆም ማድረጋቸውን አስታወቁ።

    ትራምፕ ትሩዝ ሶሻል በተሰኘው የማኅበራዊ ሚዲያ ገጻቸው ላይ ባሰፈሩት ጽሑፍ፣ “በፍጥነት ስምምነት ላይ መድረስ እንዲቻል የጥቃት እርምጃው እንዲቋረጥ” መወሰናቸውን አስታውቀዋል።

    እንደ ፕሬዝዳንቱ ገለጻ የሚደረሰው ስምምነት ሆርሙዝ ወሽመጥ ወዲያውኑ እንዲከፈት እንዲሁም “ኢራን [የደቀነችው] የኒውክሌር ስጋት” እንዲቆም የሚያደርግ ነው። እዚህ ውሳኔ ላይ የተደረሰው ከእስራኤል ጋር በመተባበር መሆኑንም ተናግረዋል።

    ትራምፕ ይህንን ውሳኔያቸውን ይፋ ያደረጉት፣ የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ዋሽንግተን በሳምንቱ መጨረሻ ኢራን ላይ አዲስ እና ከባድ ጥቃቶችን ለመፈጸም እንዳቀደች የሚገልጹ ዘገባዎችን ካወጡ በኋላ ነው።

    ትራምፕ እርምጃውን ከማሳወቃቸው አስቀድሞ ኢራን "አሜሪካ ውጥረቱን እያባባሰች ነው" የሚል ክስ አቅርባ ነበር። ከዋሽንግተን ጋር የሚተባበር ማንኛውም የቀጣናው አገር "በጦርነቱ ነበልባል ይዋጣል" በማለትም አስጠንቅቃለች።

    የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ባጋሩት ልጥፍ፣ አሜሪካ “ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወዲህ ታይቶ በማይታወቅ ወታደራዊ አስፈሪነት፣ ጥንካሬ እና ኃይል ኢራን እስላማዊ ሪፐብሊክ ላይ እርምጃ ለመውሰድ ተዘጋጅታ እና ታጥቃ” እንደነበር ገልጸዋል።

    ነገር ግን ኢራን እና ሌሎች የመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ስምምነት ላይ እንዲደረስ ለማድረግ ሲባል ጥቃቱ “እንዳይፈጸም መጠየቃቸውን” ተከትሎ እርምጃውን መሰረዛቸውን ተናግረዋል።

    “የስምምነቱ ወሰኖች ስምምነት ተደርሶባቸው” ሲሉም የንግግር ሂደቱ ወደፊት መጓዝ እንደቻለ ጠቁመዋል።

    አክለውም፤ የተደረሰው መግባባት “የሆርሙዝ ወሽመጥን ወዲያው፣ ሙሉ በሙሉ እና በጠቅላላ መክፈትን እንዲሁም የኢራንን የኒውክሌር ስጋት ማስቆምን ያካትታል” በማለት ጽፈዋል።

    ይሁን እንጂ እስካሁን በኢራን በኩል ለዚህ የትራምፕ ገለጻ የተሰጠ ምላሽ የለም።

  4. የሳዑዲ አረቢያ የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር ዛሬ ሦስት ኢትዮጵያውያን በሞት መቀጣታቸውን አስታወቀ

    ሳዑዲ አረቢያ ዛሬ በአሲር ግዛት ሦስት ኢትዮጵያውያንን በሞት መቅጣቷን አስታወቀች።

    ሦስቱ ኢትዮጵያውያን ወደ ሳዑዲ አረቢያ ግዛት “ሃሺሽ ለማስገባት ተባብረዋል” ተብለው መከሰሳቸውን የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር በመግለጫው ላይ አመልክቷል።

    ሟቾቹ በቁጥጥር ሥር ከዋሉ በኋላ በተደረገባቸው ምርመራ ጥፋተኛ ሆነው መገኘታቸውን የገለጸው ሚኒስቴሩ፣ ፍርድ ቤቱ በሞት እንዲቀጡ ውሳኔ ማሳለፉን ጠቅሷል።

    ተከሳሾች ወደ አገሪቱ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ቢሉም ውሳኔው መጽናቱንና ቅጣቱ መፈጸሙን ጨምሮ አስታውቋል።

    የሞት ቅጣቱ ዛሬ ቅዳሜ ሐምሌ 25፣ 2018 ዓ.ም በአሲር ግዛት መፈጸሙን ሚኒስቴሩ ባወጣው መግለጫ ላይ ጠቅሷል።

    ሰኞ ዕለት ሐምሌ 20፣ 2018 ዓ.ም. እንዲሁ የሳዑዲ አረቢያ የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር አምስት ተጨማሪ ኢትዮጵያውያንን በሞት መቅጣቱን አስታወቆ ነበር።

    በያዝነው ዓመት የመጀመሪያዎቹ ሰባት ወራት ብቻ 17 ኢትዮጵያውያን በሞት ተቀጥተዋል።

    ከዚህ ቀደም ሂዩማን ራይትስ ዎች ሐሚስ ሙሻይት በተባለው እስር ቤት ቢያንስ 63 ኢትዮጵያውያን ከአደንዛዥ ዕጽ ጋር በተያያዘ የሞት ቅጣት እንደተጋረጠባቸው በማስጠንቀቅ መግለጫ አውጥቶ ነበር።

    የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ሐምሌ 6፣ 2018 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ የኢትዮጵያ መንግሥት ከሳዑዲ አረቢያ የሚመለከታቸው አካላት ጋር "የሕግ ሒደት ላይ ያሉ እና የፍርድ ውሳኔ የተላለፈባቸው" ኢትዮጵያውያንን በተመለከተ "ከሚመለከታቸው" የአገሪቱ ባለሥልጣናት ጋር "በቅርበት እየተነጋገረ" መሆኑን አስታውቋል።

    በተጨማሪም ሪያድ ውስጥ በሚገኘው ኤምባሲ እና በጅዳ ቆንስላ ጽሕፈት ቤት አማካኝነት "አስቸጋሪ ሁኔታዎች ለገጠሟቸው የኢትዮጵያውያን ዜጎች ሰብአዊነትን ከግምት ያስገባ" እርምጃ እንዲወሰድ የሚደረገው ጥረት መቀጠሉን ገልጿል።በሳዑዲ የሞት ፍርድ የሚጠብቃቸው ኢትዮጵያውያን በጭንቀት ከእስር ቤት ለቢቢሲ ደውለው ያጋሩት ታሪክ

  5. በዮርዳኖስ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ዜጎቹ መካከለኛው ምሥራቅን ለቅቀው እንዲወጡ አሳሰበ

    በዮርዳኖስ የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ ቅዳሜ ዕለት በቀጣናው ያለው ውጥረት ከተባባሰ ዜጎች ከመካከለኛው ምሥራቅ ለመውጣት እንዲያስቡ አሳሰበ።

    "በአሁኑ ወቅት በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኙ አሜሪካውያን ጥንቃቄ እንዲያደርጉ እና ንቁ እንዲሆኑ ያስፈልጋል። እንዲሁም የበረራ ስረዛዎች፣ ለጊዜው የአየር ክልል መዘጋት እና ሊያጋጥሙ የሚችሉ የጉዞ መስተጓጎሎችን ለመጋፈጥ ዝግጁ መሆን አለባቸው" ሲል ኤምባሲው በይፋዊ የኤክስ ገጹ ላይ የደኅንነት ማስጠንቀቂያ አውጥቷል።

    እንዲሁም ከመካከለኛው ምሥራቅ ውጭ ያሉ አሜሪካውያን “ወደ ቀጣናው እና ወደ አካባቢው የሚያደርጉትን ጉዞ ሊያስቡበት እንደሚገባ” መክሯል።

    ኤምባሲው “ኢራን እና ኢራንን የሚደግፉ ቡድኖች በባሕር ማዶ የሚገኙ የአሜሪካን ንብረቶች ሊያጠቁ ይችላሉ” ሲል አስጠንቅቆ፣ በመካከለኛው ምሥራቅ ያለውን ሁኔታ “ያልተረጋጋ” ሲል ገልጾታል።

    “በአማን የሚገኘው የአሜሪካ ኤምባሲ፣ ሁሉም አሜሪካውያን በዮርዳኖስ ውስጥ ወደሚገኙ የጦር ሠፈሮች ከመጓዝ እንዲቆጠቡ” ያሳሰበ ሲሆን ዜጎችም የሚሰጡ ማስጠንቀቂያዎችን እንዲከታተሉና ከአገሪቱ ባለሥልጣናት የሚሰጡ መመሪያዎችን እንዲከተሉ አሳስቧል።

    ይህ ማስጠንቀቂያ የተሰጠው በአሜሪካ እና በኢራን መካከል ያለው ውጥረት በከፍተኛ ሁኔታ በተባባሰበት ወቅት ሲሆን፣ ዋሽንግተን በዚህ ሳምንት መጨረሻ በኢራን ላይ አዳዲስ ጥቃቶችን ለመፈጸም ዕቅድ እንዳላት ሲቢኤስ ከባለስልጣናት ያገኘውን መረጃ ጠቅሶ ዘግቧል።

    ቅዳሜ ዕለት ኩዌት የመንግሥት ተቋምንና የሲቪል ተሽከርካሪዎችን ዒላማ ያደረጉ የኢራን ድሮኖችን እንዳከሸፈች እና አንድ የጭነት መኪና በሆርሙዝ የባሕር ወሽመጥ አቅራቢያ በኦማን የባሕር ዳርቻ ባልታወቀ ሚሳኤል እንደተመታ ገልጻለች። በሁለቱም ክስተቶች ምንም ዓይነት ጉዳት አልደረሰም ተብሏል።

  6. በኦማን የባሕር ዳርቻ ሁለት ነዳጅ ጫኝ መርከቦች ላይ ጥቃት ተፈጸመ

    በኦማን ባሕር ዳርቻ ሁለት የነዳጅ ጫኝ መርከቦች ምንነታቸው ባልታወቁ ተወንጫፊዎች መመታታቸውን የዩናይትድ ኪንግደም ባሕር ትራንስፖርት አስታወቀ።

    እንደ ዩኬ ባሕር ትራንስፖርት መረጃ የመጀመሪያው ጥቃት የተፈጸመው በሰሜን ምሥራቅ ኦማን የባሕር ዳርቻ በምትገኘው ሊማ በቅርብ ርቀት ላይ ነው።

    ዩኬኤምቲኦ፣ ነዳጅ ጫኝ መርከቡ “ምንነቱ ባልታወቀ ተወንጫፊ ተመትቶ የሞተር ክፍሉ ላይ ጉዳት ደርሶበታል” ብሏል።

    በጥቃቱ የሞቱ ሰዎች አለመኖራቸውን እና ምንም ዓይነት አካባቢያዊ ውድመት አለመድረሱን ጨምሮ አስታውቋል።

    በኦማን ሰሜን ምሥራቅ ድንበር ኻሳብ በሚባል ሥፍራ ደግሞ ሁለተኛ ጥቃት መድረሱን ድርጅቱ ጨምሮ አስታውቋል።

    የመርከቧ ሠራተኞች ትልቅ ፍንዳታ መስማታቸውን፤ ነገር ግን ምንም ዓይነት ጉዳት አለመድረሱን ተናግረዋል።

    ሊማ እና ኻሳብ የተባሉት ሥፍራዎች በኦማን ሙሳንዳም ባሕረ ገብ መሬት የሚገኙ ሲሆን ሥፍራው ወደ ሆርሙዝ ወሽመጥ የሚገቡ መርከቦችን ለመቆጣጠሪያነት የሚያገለግል ነው።

  7. በኢራን የኤነርጂ መሠረተ ልማቶች ላይ ያነጣጠረ አዲስ መጠነ ሰፊ ጥቃት መታቀዱ ተሰማ

    የአሜሪካ ጦር በዚህ ሳምንት መጨረሻ በኢራን ላይ አዲስ ጥቃት ለመክፈት እየተዘጋጀ መሆኑን ስማቸውን ያልጠቀሷቸውን ምንጮች ዋቢ አድርገው የአሜሪካ መገናኛ ብዙኃን ዘገቡ።

    ለሲቢኤስ መረጃ የሰጡ ምንጮች ጥቃቱ የኢራን የኃይል መሠረተ ልማቶች ላይ ሊያተኩር እንደሚችል ጠቅሰው፤ ነገር ግን ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ይሁንታ መስጠት አለባቸው ብለዋል።

    የእስራኤል ጦር ከረዥም ጊዜ በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ በጥቃቱ ላይ ሊሳተፍ እንደሚችል አክሲዮስ ዘግቧል።

    አርብ ዕለት በካምፕ ዴቪድ ለጋዜጠኞች ጥያቄ ምላሽ የሰጡት ፕሬዚዳንት ትራምፕ “ክፉኛ እንደበድባቸዋለን” ብለዋል።

    “የሆነ ጊዜ ‘ከዚህ በላይ መቀበል አንችልም’ ማለት መቻል አለባቸው” ሲሉም አክለዋል።

    በዓለም አቀፉ ሕግ መሠረት ሰላማዊ ዜጎች የሚጠቀሙበትን መሠረተ ልማት ማጥቃት የጦር ወንጀል ነው።

    የእስራኤል መከላከያ ሚኒስትር እዝራኤል ካትዝ ማክሰኞ ዕለት “የኢራንን የኤነርጂ ተቋማት ለመደብደብ በጣም እንፈልጋለን” ብለው ነበር።

    ቻናል 14 ከተባለ የእስራኤል መገናኛ ብዙኃን ጋር በነበራቸው ቆይታ “[ኢራን] ጎረቤት አገራት ላይ ጥቃት ልትፈጽም እና ዓለም አቀፍ ቀውስ ሊከሰት ይችላል በሚል ስጋት አሜሪካ እስካሁን ይሁንታዋን አልሰጠችም” ሲሉ መናገራቸውን ዘ ታይምስ ኦፍ እስራኤል ዘግቧል።

    “እኛን በሚመለከት ግን [ኢራንን] አርባ ዓመት ወደ ኋላ ለመመለስ ተዘጋጅተናል” ብለዋል።

    የፔንታጎን ቃል አቀባይ ሺን ፓርኔል በየትኞቹ ዒላማዎች ላይ ጥቃት እንደሚፈጸም ከመናገር ተቆጥበዋል።

    ፓርኔል ለሲቢኤስ ኒውስ በሰጡት መግለጫ “የጦር መሥሪያ ቤቱ ምን ጊዜም የፕሬዚዳንቱን ትዕዛዝ በመጣበት ቅጽበት ለመፈጸም በተጠንቀቅ ነው ያለው” ብለዋል።

    አንድ የኢራን ባለሥልጣን በመሠረተ ልማቶች ላይ የሚፈጸም ጥቃት “የእብደት” ምልክት ነው በማለት አገራቸው የአጸፋ ምላሽ ለመስጠት ዝግጁ መሆኗን መናገራቸውን አል-ጃዚራ ዘግቧል።

    ባለሥልጣኑ አክለውም የኢራን ምላሽ “የጽዮናዊያን መንግሥት ወሳኝ መሠረተ ልማቶችን እና በቀጣናው የሚገኙ የአሜሪካ የኤነርጂ ተቋማትን” እንደሚያካትት ተናግረዋል።

  8. ሐማስ “በትክክል” ትጥቅ ሳይፈታ ወታደሮቻቸው ከጋዛ እንደማይወጡ አንድ የእስራኤል ባለሥልጣን ተናገሩ

    አንድ ከፍተኛ የእስራኤል ባለሥልጣን በጋዛ ያለው የፍልስጤም ታጣቂ ቡድን ሐማስ "በትክክል ትጥቅ ሳይፈታ" ወታደሮቻችን ካሉበት ሥፍራ አይወጡም አሉ።

    ይህ በእንዲህ እንዳለ ሐማስ ከባድ የጦር መሳሪያዎቼን ለማስረከብ እስራኤል "ሁሉንም ዓይነት ጥቃቶች" ማቆም እንዲሁም ጦሯን ከጋዛ ማስወጣት አለባት ብሏል።

    ይህ የሆነው ዶናልድ ትራምፕ የሰላም ቦርዱ በጋዛ ውስጥ ሐማስን እና ሌሎች የታጠቁ ቡድኖችን "ሙሉ በሙሉ ትጥቅ ለማስፈታት" ስምምነት ላይ መድረሱን ከተናገሩ በኋላ ነው።

    አርብ ዕለት ትራምፕ እስራኤል በቀረበው ስምምነት "በጣም ደስተኛ" እንደሆነች በመግለጽ "ለመካከለኛው ምሥራቅ ትልቅ እርምጃ" ሲሉ ገልጸውታል። ሆኖም የእስራኤል የቀኝ ክንፍ ሚኒስትር ኢታማር ቤን ጂቪር ረቂቁን "ተቀባይነት የለውም" ሲሉ ውድቅ አድርገውታል።

    ይህ በአሜሪካ አደራዳሪነት ከስምምነት የተደረሰው የተኩስ አቁም ዕቅድ ሁለተኛ ምዕራፍ አካል ሲሆን ይህም በጋዛ ላይ የሚደረገውን ጦርነት ለማስቆም ያለመ ነው።

    ባለፈው ዓመት መስከረም ወር ይፋ የተደረገው ባለ 20 ነጥብ ዕቅድ፣ የስምምነቱን አፈፃፀም የሚቆጣጠር የሰላም ቦርድ መመስረትን፣ እንዲሁም ሐማስን ትጥቅ ማስፈታት፣ የእስራኤል ወታደሮችን ማስወጣት እና የጋዛን መልሶ ግንባታ ያካትታል።

    ትራምፕ አርብ ዕለት በካምፕ ዴቪድ በተካሄደው የካቢኔ ስብሰባ ላይ ሐማስ ትጥቅ ለመፍታት በመስማማቱ ከእስራኤል ጋር "መግባባት ላይ መድረሳቸውን" ገልጸው "እስራኤል በዚህ በጣም ደስተኛ ነች" ብለዋል።

    ሐማስ የእስራኤል ጦር ከጋዛ ከመውጣቱ በፊት ትጥቅ ይፈታ እንደሆነ የተጠየቁት ትራምፕ በቀጥታ ምላሽ ባይሰጡም ጋዛ "በጣም ውስብስብ ሁኔታ ውስጥ ትገኛለች" ብለዋል።

    ሐማስ የጦር መሳሪያዎቹን ለሰላም ቦርድ እንደሚያስረክብም አክለዋል።

    የእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ ስለአዲሱ ዕቅድ እስካሁን አስተያየት አልሰጡም።

    ነገር ግን አንድ ከፍተኛ የእስራኤል ባለሥልጣን እንዳሉት የአገሪቱ አቋም አሁንም "የእስራኤል የመከላከያ ሠራዊት ሐማስን በትክክል ትጥቅ ማስፈታት ካልቻለ ከአሁኑ ቢጫ መስመር አይወጣም" የሚል ነው።

  9. ትራምፕ ስለ ሐማስ ትጥቅ መፍታት ከእስራኤል ጋር ‘መግባባት’ ላይ መደረሱን ተናገሩ

    ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ ዛሬ በካምፕ ዴቪድ ባደረጉት ንግግር፤ የሐማስን ትጥቅ መፍታት በተመለከተ ከእስራኤል ጋር “መግባባት” መኖሩን ገለጹ።

    “እስራኤል በጣም ደስተኛ ናት” ሲሉም ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ ሰጥተዋል።

    ቀኝ ዘመሙ የእስራኤል ብሔራዊ ደኅንነት ሚኒስትር ኢታማር ቤን ግቪር በማኅበራዊ ሚዲያቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ፤ የፕሬዝዳንት ትራምፕ የሰላም ቦርድ ይፋ ያደረገው ረቂቅ ስምምነት “በእስራኤል ተቀባይነት የለውም” ብለዋል።

    የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ማርኮ ሩቢዮ በበኩላቸው ሐማስ ሙሉ በሙሉ ትጥቅ ለመፍታት መስማማቱ “ሌላ ትልቅ እርምጃ ነው” ብለዋል።

    “ብዙ ሰዎች ይሆናል ብለው ያልጠበቁት ነገር ነው። መሆን ነበረበት። መስማማታቸው ትልቅ ስኬት ነው” ሲሉም ተናግረዋል።

    በስምምነቱ መሠረት የእስራኤል ወታደሮች የጋዛ ሰርጥን ለቅቀው እንደሚወጡ ተገልጿል።

    የእስራኤሉ ሚኒስትር ግን አገራቸው በጋዛ ያሉ ዒላማዎችን “መምታት መቀጠል እንዳለባት” ተናግረዋል።

    ሐማስ ደግሞ ከባድ የጦር መሣሪያዎቹን የሚያስረክበው እስራኤል “ሁሉንም ዓይነት ወረራዎች ካቆመች” እና ጦሯን ከጋዛ ካስወጣች እንደሆነ አስታውቋል።

    ትራምፕ ሐማስ ትጥቅ ለመፍታት መስማማቱ “ለመካከለኛው ምሥራቅ ትልቅ እርምጃ ነው” ብለዋል።

    ቅድሚያ የሚሰጠው ለሐማስ ትጥቅ መፍታት ነው ወይስ ለእስራኤል ጦር ከጋዛ ሰርጥ መውጣት? በሚል ከጋዜጠኛ ለቀረበላቸው ጥያቄ ግን ምላሽ አልሰጡም።

    ስምምነቱ ይተገበር እንደሆነ ተጠይቀው፤ በጋዛ ያለው ሁኔታ “እጅግ ውስብስብ ነው” ብለዋል። “ሰዎቹ ውስብስብ እና ከባድ ናቸው። በብዙ ነገር ድንቅ ናቸው፤ በብዙ መንገድ ደግሞ ድንቅ አይደሉም” ሲሉም ተናግረዋል።

    የሐማስን የጦር መሣሪያ ማን እንደሚረከብ ከቢቢሲ ተጠይቀው፤ የሰላም ቦርድ ኃላፊነቱን ይወስዳል ብለዋል።

    “በድንቅ ሰዎች ነው የሚመራው” ሲሉም ቦርዱን ገልጸዋል።

  10. የእስራኤሉ ሚኒስትር የትራምፕን ስምምነት “ተቀባይነት የለውም” አሉ

    ቀኝ ዘመሙ የእስራኤል ብሔራዊ ደኅንነት ሚኒስትር ኢታማር ቤን ግቪር የፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የሰላም ቦርድ ይፋ ያደረገው ረቂቅ ስምምነት “በእስራኤል ተቀባይነት የለውም” አሉ።

    ሚኒስትሩ በቴሌግራም እና በኤክስ ገጻቸው ባሰፈሩት ጽሑፍ “የአሸባሪው ድርጅት ገዳዮችን የማስወገድ ሒደትን ለማቆም መስማማት፤ ሐማስ እንደ አዲስ ተደራጅቶ ወደ ቀጣዩ ጥቃት እንዲያመራ ያስችላል” ብለዋል።

    ትራምፕ ሐማስ “ሙሉ በሙሉ ትጥቅ ለመፍታት” መስማማቱን ያስታወቁ ሲሆን፤ ትጥቅ መፍታቱ በጋዛ የሚገኙ ሌሎች ታጣቂ ቡድኖችንም የሚጨምር ይሆናል።

    በስምምነቱ መሠረት የእስራኤል ወታደሮችም ሰርጡን ለቅቀው እንደሚወጡ ተገልጿል።

    እስራኤል እስከ አሁን ድረስ ስለ ስምምነቱን አቋሟን በይፋ ሳትገልጽ የቆየች ሲሆን፤ ትራምፕ በበኩላቸው እስራኤል በስምምነቱ መሠረት ከጋዛ ጦሯን የማታስወጣ ከሆነ “በጣም እንደሚያዝኑ” መናገራቸውን አንድ የአሜሪካ ባለሥልጣን ለጋዜጠኞች ገልጸዋል።

    የእስራኤሉ ሚኒስትር አገራቸው በጋዛ ያሉ ዒላማዎችን “መምታት መቀጠል እንዳለባት” ጠቅሰው “ከአካባቢው መፈናቀልን እንደሚደግፉ” ተናግረዋል።

  11. የኢራን አብዮታዊ ዘብ ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን ሆርሙዝ ላይ መምታቱን ገለጸ

    የኢራን አብዮታዊ ዘብ የተቀመጠውን መመሪያ “ጥሰዋል” ያላቸው ሁለት በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ሊያልፉ የሞከሩ ነዳጅ ጫኝ መርከቦችን መምታቱን አስታወቀ።

    ዘቡ ባወጣው መግለጫ ላይ ሁለቱ ነዳጅ ጫኝ መርከቦች የጥቃት ዒላማ የሆኑት “ለደኅንነት አስተማማኝ ባልሆነ እና በሕገወጥ መስመር” በአሜሪካ ሠራዊት “በአየር ታጅበው ባልተፈቀደ መስመር” በሆርሙዝ በኩል ሲጓዙ እንደሆነ አመልክቷል።

    ጨምሮም ሁለቱ መርከቦች ጥቃት ከደረሰባቸው በኋላ “ሌሎች አራት ነዳጅ ጫኝ መርከቦች በፍጥነት አቅጣጫቸውን” ቀይረው ወደመጡበት መመለሳቸውን አሳውቋል።

    አብዮታዊ ዘቡ “ለመርከብ ባለቤቶች እና ለኢንሹራንስ ኩባንያዎች የአሜሪካ ማዕከላዊ ዕዝ የሚያወጣውን ማስታወቂያ እንዳይሰሙ” ማስጠንቀቁን ገልጿል።

    የአሜሪካ ጦር ሠራዊት ማዕከላዊ ዕዝ (ሴንትኮም) ሐሙስ ዕለት በሆርሙዝ ላይ ያሉት ነጻ የመርከቦች መተላለፊያ መመስሮች የደኅንነት ስጋት የለባቸውም በማለት፤ ነገር ግን በወሽመጡ ላይ ለንግድ መርከቦች እና ለሠራተኞቻቸው አደጋ የነበረው የኢራን አብዮታዊ ዘብ ነው ብሎ ነበር።

    ከኢራን አብዮታዊ ዘብ ባሕር ኃይል ጋር ግንኙነት ያለው የኤክስ ማኅበራዊ ሚዲያ አካውንት በእሳት የተያያዙ በርካታ መርከቦችን የሚያሳይ ምሥል በእንግሊዝኛ እና በፋርስ ቋንቋ “የመመሪያ ጥሰት መጨረሻው” ከሚል ጽሁፍ ጋር አጋርቷል።

  12. ሐማስ ከባድ የጦር መሣሪያዎቹን የሚያስረክበው እስራኤል “ወረራ ካቆመች” እንደሆነ አስታወቀ

    ሙሉ በሙሉ ትጥቅ ለመፍታት የተስማማው ሐማስ ከባድ የጦር መሣሪያዎቹን የሚያስረክበው እስራኤል “ሁሉንም ዓይነት ወረራዎች ካቆመች” እና ጦሯን ከጋዛ ካስወጣች እንደሆነ አስታወቀ።

    ሐማስ ባወጣው መግለጫ ድርድሩን ያደረገው “ኃላፊነት በተሞላው መንገድ እና በቀናነት” እንዲሁም “በፍልስጤማውያን ታጣቂዎች መካከል ብሔራዊ መስማማት ተደርሶ” እንደሆነ ጠቁሟል።

    ስምምነቱ ወደ ፊት እንዲቀጥል “መሠረታዊው ቅድመ ሁኔታ” እስራኤል በጋዛ የምታደርሰውን ጥቃት ለመግታት ቁርጠኝነቷን መግለጿ እንደሆነ ሐማስ ተናግሯል።

    ስምምነቱ ዓለም አቀፍ ጥበቃ ሰጪ ኃይሎች እንዲሰማሩ እንደሚጠይቅ ተገልጿል።

    ሐማስ እንዳለው ስምምነቱ ፍልስጤም አገር ሆና የመመሥረት መብቷን የሚያረጋግጥም ነው።

    ሐማስ ከባድ የጦር መሣሪያዎችን የሚያስረክበው በሰላም ቦርዱ ኃላፊነት መሆኑን አስታውቋል።

    እስራኤል ስምምነቱን ስለመቀበሏ እስካሁን የተባለ ነገር የለም።

  13. ሐማስ ትጥቅ ለመፍታት ስለመስማማቱ ማን ምን አለ?

    ሐማስ “ሙሉ በሙሉ ትጥቅ ለመፍታት” መስማማቱን የአሜሪካው ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስታውቀዋል።

    ትጥቅ መፍታቱ በጋዛ የሚገኙ ሌሎች ታጣቂ ቡድኖችንም የሚጨምር ሲሆን፤ የእስራኤል ወታደሮችም ሰርጡን ለቅቀው እንደሚወጡ ተገልጿል።

    ለመሆኑ ሐማስ ትጥቅ ለመፍታት ስለመስማማቱ ማን ምን አለ?

    ትራምፕ- ፕሬዝዳንቱ ያቋቋሙት የሰላም ቦርድ ሐማስ “ሙሉ በሙሉ” ትጥቅ እንዲፈታ ስምምነት ላይ መድረሱን ገልጸዋል።

    “ጋዛ በአዲስ ፍልስጤማዊ መንግሥት የምትመራበት ቁልፍ ደረጃ ላይ ነን” ብለዋል።

    የሐማስ ባለሥልጣን- ከፍተኛው የሐማስ ባለሥልጣን እና የድርድር ቡድኑ አባል ለቢቢሲ እንደገለጹት ውይይቱ “ረዥም እና እጅግ ከባድ” ነበር።

    ሐማስ “የከፍተኛ የጦር መሣሪያዎች ርክክብ እና ክምችት” በእስራኤል ሥር ሳይሆን በፍልስጤማውያን ሥር እንዲሆን አጥብቆ መከራከሩን ገልጸዋል።

    የሰላም ቦርድ አመራር- የሰላም ቦርድ አመራር የሆኑት ኒኮላይ ማልዴኔቭ በማኅበራዊ ሚዲያቸው “የስምምነቱ ይዘት ዋጋ አለው። በቀጣይ ምን ይሆናል የሚለው ደግሞ የበለጠ ዋጋ ይኖረዋል” ብለዋል።

    የእስራኤል መንግሥትስ? እስካሁን ድረስ ከእስራኤል በኩል ምንም አልተባለም።

    ትራምፕ በበኩላቸው እስራኤል በስምምነቱ መሠረት ከጋዛ ጦሯን የማታስወጣ ከሆነ “በጣም እንደሚያዝኑ” መናገራቸውን አንድ የአሜሪካ ባለሥልጣን ለጋዜጠኞች ገልጸዋል።

  14. በ24 ሰዓት ውስጥ ብቻ 49,000 ሰዎች ወደ ስፔን ግዛት መግባታቸውን ባለሥልጣናት ገለፁ

    የስፔን ባለሥልጣናት በሰሜን አፍሪካ ወደ ምትገኘው ሴኡታ 49,000 ያህል ስደተኞች በየብስ እና በባሕር በ24 ሰዓት ውስጥ ገብተዋል ተብሎ እንደሚገመት ተናገሩ።

    ሐሙስ ዕለት ከአካባቢው የወጡ ፎቶዎች እና ተንቀሳቃሽ ምስሎች በሺህዎች የሚቆጠሩ ስደተኞች በዋና ወደ ግዛቲቱ ሲያቋርጡ የታዩ ሲሆን የአካባቢው መገናኛ ብዙኃን ሌሊቱንም መቀጠሉን ተናግረዋል።

    ቢያንስ 18 ሰዎች ወደ ሴኡታ ለመግባት ሲሞክሩ መሞታቸውን ባለሥልጣናቱ ጨምረው ገልጸዋል።

    የስፔን ጠቅላይ ፍርድ ቤት የአገሪቱ ግዛት ወደሆኑት ወደ ሴኡታ ወይንም ሜሊላ ለመድረስ የሚሞክሩ ስደተኞች ወደ ሞሮኮ እንዳይመለሱ ሲል ውሳኔ አሳልፏል።

    ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ስደተኞች ወደ ግዛቲቱ መግባት መጀመራቸውን ተከትሎ የአካባቢው ባለሥልጣናት ማድሪድ ተጨማሪ ወታደሮች ወደ አካባቢው እንድትልክ ጠይቀዋል።

    ነገር ግን ሐሙስ ዕለት በርካታ ስደተኞች በተመሳሳይ ግዜ ከሞሮኮ በመነሳት የሴኡታን ድንበር ጥሰው ገብተዋል።

    ስፔን የሴኡታን እና ሜሊላን ደኅንነት ለማስጠበቅ ወታደሮቿን ያሰማራች ሲሆን ሌሊቱን ከ300 እስከ 400 የሚሆኑ ሰዎች ማቋረጣቸው ተዘግቧል።

    የስፔን ባለሥልጣናት ወደ ሴኡታ የገቡት ሰዎች ቁጥር ከከተማዋ ሕዝብ ከግማሽ በላይ እንደሚሆኑ ገምተዋል።

    በቅርብ ጊዜ መረጃዎች እንደሚያሳዩት የሴኡታ ሕዝብ ቁጥር 83,600 ነው።

    ባለሥልጣናት ባለፉት 24 ሰዓታት ውስጥ ወደ ግዛቲቱ ከገቡ ሰዎች መካከል 7,000 ያህሉ ታዳጊዎች ናቸው።

    የስፔን የአገር ውስጥ ጉዳዮች ሚኒስቴር “በተቻለ ፍጥነት” በሕገ ወጥ መልኩ ድንበር ጥሰው የገቡትን በሙሉ ለመመለስ ከሞሮኮ መንግሥት ጋር እየሰራ መሆኑን አስታውቋል።

    ይህ የአገሪቱ መንግሥት ቁጥር ትክክል ከሆነ እአአ ከግንቦት 2021 ወደ ሴኡታ ያቋረጡ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ስደተኞች ይሆናሉ። ከዚህ ቀደም ወደ ግዛቲቱ በአንድ ጊዜ የገቡ ስደተኞች ቁጥር 10,000 ነው።

    የስፔን ጠቅላይ ሚኒስትር ፔድሮ ሳንቼዝ አርብ ዕለት ሴኡታን ይጎበኛሉ ተብሎ ይጠበቃል።

  15. ለኢራን ሲሰልል ነበር የተባለ ብሪታኒያዊ በቁጥጥር ስር ዋለ

    በቆጵሮስ በሚገኝ የዩናይትድ ኪንግደም የጦር ሠፈር ለኢራን ሲሰልል ነበረ የተባለ ብሪታኒያዊ በቁጥጥር ሥር ዋለ።

    የ44 ዓመቱ ራሻድ ሱልታኖቭ በጦር ሠፈሩ ላይ ቅኝት ሲያደርግ እንደነበር እና ያገኘውን መረጃ ለኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ማጋራቱ ተገልጿል።

    ሱልታኖቭ ከብሪታኒያ በተጨማሪም የአዘርባጃን ዜግነት ያለው ሲሆን በቆጵሮስ ፖሊስ እአአ ሐምሌ 17 በቁጥጥር ስር ከዋለ በኋላ ለብሪታኒያ ተላልፎ እስከሚሰጥ ድረስ በዚያው መቆየቱ ተገልጿል።

    የብሪታኒያ ፖሊስ በብሔራዊ ደኅንነት አዋጁ መሠረት ግለሰቡ ላይ ክስ እንደሚመሰረት አስታውቋል።

    አሜሪካ እና እስራኤል ቴህራን ላይ ጦርነት ከከፈቱ በኋላ በመጋቢት ወር ኢራን በቆጵሮስ በሚገኝ የዩናይትድ ኪንግደም ጦር ሠፈር ላይ የድሮን ጥቃት ፈጽማለች።

    ዩናይትድ ኪንግደም በቆጵሮስ እአአ ከ1950 ጀምሮ የጦር ሠፈር ያላት ሲሆን ከቅርብ ወራት ወዲህ ከኢራን የሚተኮሱ ድሮኖችን እና ሚሳዔሎችን መትቶ ለመጣል ተጠቅማበታለች።

    ግለሰቡ የዩኬ የጦር ሠፈር ላይ ስለላ የፈጸመው እአአ ከግንቦት 11/2025 እስከ ሰኔ 22/2025 ድረስ መሆኑ ተገልጿል።

  16. በግብጽ የደረሰ የድሮን ጥቃት በሲዊዝ ካናል የሚደረግ የመርከቦች እንቅስቃሴ ላይ ስጋት ፈጠረ

    በግብፅ የሜዲትራኒያን ባህር ዳርቻ በሚገኘው የዳሚዬታ ወደብ ላይ በሚገኙ ሁለት የጋዝ ማጓጓዣ መርከቦች ላይ እሳት ያስነሳው የድሮን ጥቃት፣ በስዊዝ ካናል በኩል የሚደረገው የመርከብ እንቅስቃሴ ላይ አዲስ ስጋት ፈጠረ።

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል እየተባባሰ በመጣው ግጭት ወቅት የስዊዝ ካናል ለሳዑዲ ነዳጅ ንግድ ከቀሩት ዋና ዋና መስመሮች አንዱነው።

    በዳሚዬታ ወደብ በሁለት መርከቦች ላይ እሳት እንዲነሳ ያደረገው የድሮን ጥቃት መሆኑን የግብፅ ካቢኔ ሐሙስ ዕለት አስታውቆ ነበር።

    እስካሁን ድረስ ጥቃቱን በተመለከተ ኃላፊነት የወሰደ አካል የለም።

    ወደቡ ሜዲትራኒያን እና ቀይ ባህርን የሚያገናኘው የስዊዝ ካናል አቅራቢያ ይገኛል።

    የድሮን ጥቃት የአሜሪካ ንብረት በሆነው እና 'ኤነርጎስ ዊንተር' በተሰኘ የጋዝ ማከማቻ መርከብ ላይ ከደረሰ በኋላ እሳት የተነሳ ሲሆን ቃጠሎው ወደ ሌላ መርከብ መዛመቱን የዓይን እማኞች ለሮይተርስ ተናግረዋል።

    ኢራን በዳሚዬታ በተፈጸመው ጥቃት ላይ ምንም ዓይነት ተሳትፎ እንደሌላት ገልጻለች።

    "ግብፅ በቀጣናው ውስጥ አስፈላጊ ወዳጅና አጋር ስትሆን፣ ደህንነቷም ለእኛ እጅግ ወሳኝ ነው" ሲሉ የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ ማኅበራዊ ሚዲያ ላይ ጽፈዋል።

    "የቀጣናውን ሰላም ለማናጋት ታቅደው በሚከናወኑ የእስራኤል ሴራዎች እና የማጭበርበሪያ ድርጊቶች ላይ ሁላችንም ንቁ መሆን አለብን።"

    አምስት ወር የሞላው የመካከለኛው ምሥራቅ ጦርነት በሆርሙዝ ወሽመጥ የሚደረግ የመርከቦች እንቅስቃሴን በመግታት የዓለም ኤነርጂ አቅርቦት ላይ ከፍተኛ ጫና ፈጥሯል።

    በኦማን እና በኢራን መካከል የሚገኘው ይህ መተላለፊያ ከግጭቱ በፊት የዓለም አንድ አምስተኛ ነዳጅ እና የተፈጥሮ ጋዝ ይጓጓዝበት ነበር።

    በአሜሪካ እና በኢራን መካከል በሚካሄደው የሰላም ድርድር ወቅት ማነቆ ጉዳዮች መካከል አንዱ የወሽመጡ ጉዳይ ይገኝበታል።

  17. ስለ ሐማስ ትጥቅ መፍታት የምናውቃቸው እና ግልጽ ያልሆኑ ነገሮች

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ሐማስ “ሙሉ በሙሉ ትጥቅ ለመፍታት” መስማማቱን አስታውቀዋል።

    ትጥቅ መፍታቱ በጋዛ የሚገኙ ሌሎች ታጣቂ ቡድኖችንም የሚጨምር ሲሆን የእስራኤል ወታደሮችም ሰርጡን ለቅቀው እንደሚወጡ ተገልጿል።

    ትራምፕ ስምምነቱ የተደረሰው በሰላም ቦርዱ አማካኝነት መሆኑን ገልጸው “ጋዛ በአዲስ የፍልስጤም መንግሥት እንድትመራ ለማድረግ ወሳኝ እርምጃ ነው” ብለውታል።

    ቢቢሲ የተመለከተው ባለ አራት ገጽ ፍኖተ ካርታ ሐማስ ትጥቅ የሚፈታበትን ጊዜያት ያስቀመጠ ሲሆን እስራኤልም ቀስ በቀስ አካባቢውን ለቅቃ ትወጣለች ይላል።

    የአሜሪካ ባለሥልጣናት እያንዳንዱ ምዕራፍ በአግባቡ መፈጸሙ “ይረጋገጣል” ብለዋል።

    አንድ ከፍተኛ የሐማስ ባለሥልጣን ቡድኑ በዕቅዱ ላይ መስማማቱን ገልጸው ይፋዊ መግለጫ እንደሚሰጥ ለቢቢሲ ገልጸዋል።

    አንድ የአሜሪካ ባለሥልጣን ደግሞ እስራኤል ጋዛን ለቅቆ ለመውጣት የማትስማማ ከሆነ ትራምፕ “በጣም ቅር ይሰኛሉ” ሲሉ ተደምጠዋል።

    እስራኤል በስምምነቱ ላይ ያላት አቋም ወይንም በድርድሩ ላይ ተሳታፊ ስለመሆኗ እስካሁን የተባለ ነገር የለም።

    የእስራኤል ጦር አካባቢውን ሙሉ በሙሉ ለቅቆ ሲወጣም የሰላም ቀጣና ያደራጅ እንደሆነ አልታወቀም።

    የሐማስ ጦር መሣሪያዎችንም ማን ተረክቦ እንደሚያስተዳድራቸው በስምምነቱ ላይ አልተቀመጠም።

    የትጥቅ መፍታት ሂደቱም ሆነ የእስራኤል ጦር ለቅቆ መውጣት እንዴት እንደሚረጋገጥም በዝርዝር አልቀረበም።

  18. ትራምፕ የሰላም ዕቅድ ካቀረቡ በኋላ ሐማስ ሙሉ በሙሉ ትጥቅ ለመፍታት መስማማቱን ገለፁ

    የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ሐማስ ትጥቅ ለመፍታት መስማማቱን እና ጋዛን ከወታደራዊ እንቅስቃሴ ነጻ እንደሚያደርግ አስታወቁ።

    ትራምፕ ሐሙስ ዕለት ምሽት ከስምምነት ላይ መደረሱን ይፋ ያደረጉ ሲሆን ይህም ያቀረቡትን የሰላም ዕቅድ ወደ ተግባር ለማስገባት ከፍተኛ እምርታ ነው ተብሏል።

    በዚህ ስምምነት መሠረት ጋዛ በአሜሪካ የሚመራው የሰላም ቦርድ በሚቆጣጠረው የፍልስጤም የቴክኖክራቶች መንግሥት መተዳደር ትጀምራለች።

    ሐሙስ ዕለት ትራምፕ በትሩዝ ሶሻል ማኅበራዊ ድረ ገጻቸው ላይ “ይህ ለዘላቂ ሰላም እና ደኅንነት ወሳኝ እርምጃ ነው” ሲሉ ጽፈዋል።

    አክለውም “ይህ ስምምነት፣ በመጨረሻም የፍልስጤምን ሕዝብ ለመርዳት ከሰላም ቦርድ ጋር በቅርበት የሚሰራ አዲስ የፍልስጤም መንግሥት ጋዛን እንዲያስተዳድር ለማድረግ ወሳኝ እርምጃ ነው” ሲሉ ጽፈዋል።

    በሥምምነቱ መሠረት የእስራኤል ወታደሮች አካባቢውን ለቅቀው ይወጣሉ።

    ስምምነቱ የተደረሰው የሐማስ ባለሥልጣናት፣ የሰላም ቦርዱ አባላት፣ የግብጽ፣ ኳታር እና ቱርክ አደራዳሪዎች በተገኙበት ነው።

    የሐማስ ባለሥልጣናት ትጥቅ በመፍታት እና የእስራኤል ጦር የጋዛ ሰርጥን ለቅቆ እንዲወጣ ከስምምነት መደረሱን አረጋግጠዋል።

    ባለሥልጣናቱ የሰላም ቦርዱ እና አደራዳሪዎቹ እስራኤል በስምምነቱ ላይ ለተዘረዘሩት ነጥቦች ተገዢ እንድትሆን እንደሚያደርጉ ያላቸውን እምነት ተናግረዋል።

    የሐማስ የድርድር ቡድን አባል የሆኑት ጋዚ ሃማድ፣ ቡድኑ "በጋዛ ሰርጥ የሚገኙ ሕዝቦቻችንን ከግድያ እና ከመፈናቀል ለመታደግ ሲባል" ስምምነቶችን እያደረጉ መሆኑን ተናግረዋል።

    እስራኤል እስካሁን ድረስ በጉዳዩ ላይ ምንም ዓይነት አስተያየት አልሰጠችም።

    በሚያዚያ ወር ሐማስ በትራምፕ የቀረበውን የሰላም ቦርድ ጥረት ጋር በተያያዘ የቀረበውን ትጥቅ የመፍታት ቅድመ ሁኔታ ውድቅ አድርጎ ነበር።

    የአሜሪካ ባለሥልጣናት ሐማስ ትጥቅ ከፈታ በኋላ እስራኤል ከጋዛ ለመውጣት ትስማማ እንደሆን ተጠይቀው ሲመልሱ “እስራኤልን የምንጠይቃት፣ በመጀመሪያ ደረጃ ከተስማሙበት የ20 ነጥብ ዕቅድ ውጪ ሌላ ነገር አይደለም፤ ስለዚህም ዕቅዱን እንደሚያከብሩት ሙሉ እምነት አለን" ሲል ምላሽ ሰጥተዋል።

    እስራኤል በ20 ነጥብ ዕቅዱ መሠረት ላለመውጣት ከወሰነች፣ ትራምፕ "እጅግ እንደሚያዝኑ" ባለሥልጣኑ ጨምረው ገልጸዋል። እስራኤል ጥሩ አጋርነቷን እንደምትቀጥል እንደሚያምኑም ባለሥልጣኑ አብራርተዋል።

    ትራምፕ በበኩላቸው “የትጥቅ ማስፈታት ሂደቱ ሲጠናቀቅ የእስራኤል ኃይሎች አካባቢውን ለቅቀው ይወጣሉ፤ እንዲሁም ዓለም አቀፉ ኃይል፣ ጋዛ ለነዋሪዎቿም ሆነ ለጎረቤቶቿ ደህንነቷ የተጠበቀ ቦታ እንዲሆን ኃላፊነቱን ለመረከብ ከአዲሱ የፍልስጤም ፖሊስ ኃይል ጋር በጋራ ይሠራል” ብለዋል።

    ዶናልድ ትራምፕ በማኅበራዊ ድረ ገጻቸው ላይ አደራዳሪዎቹን ግብጽ፣ ኳታር እና ቱርክን አመስግነዋል።

    የፈረንሳይ ዜና ወኪል የግብጽ መገናኛ ብዙኃንንን ጠቅሶ ካይሮ ሁለተኛውን ዙር የተኩስ አቁም ስብሰባ እንደምታዘጋጅ ዘግቧል።

  19. የኢራን አብዮታዊ ዘብ ኩዌት በሚገኝ የአሜሪካ አየር ኃይል ሰፈር ላይ ጉዳት ማድረሱን ገለጸ

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ ዛሬ ሐሙስ ጠዋት ኩዌት ውስጥ በሚገኘው አሊ አል-ሳሌም የአሜሪካ አየር ኃይል ጦር ሰፈር ላይ ፈጸምኩት ባለው ጥቃት ጉዳት ማድረሱን አስታወቀ።

    በጥቃቱ የእሳት ቃጠሎ ተነስቶ ሁለት የድሮኖች መጠለያዎች እንዲሁም ለወታደራዊ አውሮፕላኖች እና ሄሊኮፕተሮች የሚውል የነዳጅ ማከማቻ እንደወደመ ገልጿል።

    ነገር ግን እስካሁን ይህን የአብዮታዊ ዘቡን ጥቃት እና አደረስኩት ያለውን ጉዳት በተመለከተ ከኩዌትም ሆነ ከአሜሪካ ባለሥልጣት ወይም ከገለልተኛ ወገን የተሰጠ ማረጋገጫም ሆነ ማስተባበያ የለም።

    የኢራን እስላማዊ አብዮታዊ ዘብ የሕዝብ ግንኙነት ክፍል ጥቃቱ “ዘመቻ ናስር 2” የተባለ መሆኑን እና የአሜሪካ ኃይሎች በቀጣናው ለመኖራቸው የተሰጠ ምላሽ መሆኑን ገልጿል።

    ነገር ግን ለጥቃቱ ጥቅም ላይ ስለዋሉት የጦር መሳሪያ ዓይነቶች፣ ስለደረሰው የውድመት መጠን ወይም በሰው ላይ ስለደረሰ ጉዳት ምንም ዝርዝር መረጃ አልሰጠም።

    አብዮታዊ ዘቡ በኩዌት ሰሜን ምዕራብ ክፍል ውስጥ በሚገኘው የአሜሪካ ኃይሎች በሚገኙበት አሊ አል-ሳሌም አየር ኃይል ሰፈር ላይ ቀደም ሲል ጥቃት ፈጽሞ በአሜሪካ መገልገያዎች ላይ ከፍተኛ ጉዳት ማድረሱን ገልጾ ነበር።

    ኢራን በአሜሪካ ለሚፈጸምባት ጥቃት በመካከለኛው ምሥራቅ አገራት ውስጥ በሚገኙ የአሜሪካ ጦር ሠራዊት ሰፈሮች ላይ ተደጋጋሚ የድሮን እና የሚሳዔል ጥቃቶችን እየፈጸመች ነው።

    በተለይም በዮርዳኖስ፣ ኩዌት እና ባህሬን ውስጥ ያሉት የአሜሪካ ጦር ሰፈሮች ከባድ ጉዳት ያደረሱ ጥቃቶች እንደተፈጸሙባቸው ተዘግቧል።

  20. ቻይና ለኢራን በመቶዎች የሚቆጠሩ ሚሳዔሎችን ልትሸጥ ነው መባሉን አስተባበለች

    ቻይና ለኢራን በመቶዎች የሚቆጠሩ ከትከሻ ላይ የሚወነጨፉ የአየር መቃዋሚያ ሚሳዔሎችን ልታቀርብ ነው መባሉን መከላከያ ሚኒስቴሯ አስተባበለ።

    የጦር መሳሪያ ሽያጩን በተመለከተ ስለቀረበው ሪፖርት የተጠየቁት የቻይና የመከላከያ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ጂያንፍ ቢን በሰጡት ምላሽ “ሐሰት” ሲሉ፣ የአገሪቱ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ደግሞ ዘገባውን “መሠረተ ቢስ” ብሎታል።

    ሮይተርስ ጉዳዩን በቅርበት የሚያውቁ ሦስት ምንጮችን ጠቅሶ ቻይና በጥቂት ሳምንታት ውስጥ የመጀመሪያዎቹን ከ300 እስከ 400 የሚደርሱ ቻይና ሠራሽ የአየር መከላከያ መሳሪያዎችን ለኢራን እንደምታቀርብ ዘግቦ ነበር።

    በስምምነቱ ኪውደብሊው-12 እና ኤፍኤን-16 የተባሉ ሚሳዔሎችን ጨምሮ ዋጋቸው ከ60 እስከ 70 ሚሊዮን ዶላር የሚያወጡ የጦር መሳሪያዎችን ቻይና ለኢራን እንደምታቀርብ ገልጿል።

    የመጀመሪያዎቹ የጦር መሳሪያዎች በምዕራብ ቻይና ከምትገኘው ከተማ ኡሩምኪ ተነስተው በፓኪስታን በኩል ወደ ኢራን እንደሚጓጓዙ የሮይተርስ ምንጮች ተናግረዋል።

    ፓኪስታን በበኩሏ በእንዲህ ዓይነቱ የጦር ማሳሪያ ዝውውር ውስጥ እጇ እንደሌለበት በመግለጽ ዘገባውን “የፈጠራ እና የተዛባ” ብለዋለች።

    ኪውደብሊው-12 እና ኤፍኤን-16 የአየር መከላከያ ማሳሪያዎች ከምድር ወደ አየር የሚወነጨፉ እና በዝቅተኛ ከፍታ የሚበሩ የአውሮፕላኖችን፣ የሄሊኮፕተሮችን እንዲሁም የድሮኖችን ሙቀት በመከተል ዒላማቸውን የሚመቱ ናቸው።

    ኢራን ከቻይና መሳሪያዎቹን ስለመግዛቷ የተዘገበው ለወራት በአሜሪካ እና በእስራኤል በተፈጸመባት ጥቃት የተዳከመውን የአየር መከላከያ ሥርዓቷን መልሳ ለመገንባት እና ለማጠናከር ጥረት እደያረገች ባለበት ጊዜ ነው።